FREE ALL POLITICAL PRISONERS

FREE ALL POLITICAL PRISONERS
FREE ALL POLITICAL PRISONERS

Wednesday, April 8, 2015

በስዊድን የሰማያዊ ፓርቲ ድጋፍ ማኅበር ራሱን አስተዋወቀ

semayawi sweden
የሰማያዊ ፓርቲ ድጋፍ ማኅበር በስዊድን ተመስርቶ እየተንቀሳቀሰ መሆኑን በመግለጽ፤ የድጋፍ ማኅበሩ ቅዳሜ አፕሪል 4 ቀን 2015 ዓ.ም. (ግንቦት 26 ቀን 2007 ዓ.ም.) ራሱን አስተዋውቋል። በዕለቱ የሰማያዊ ፓርቲ ዓላማና ተግባርን ጥሪ ለተደረገላቸው ተሰብሳቢዎች ያስረዱት አቶ ሰለሞን ጌታነህ የድጋፍ ማኅበሩ ሰብሳቢ ናቸው።
አቶ ሰለሞን በስዊድን ዋና ከተማ ስቶክሆልም በተደረገው የማስተዋወቁ ሥነሥርዓት ላይ ስለሰማያዊ ፓርቲ ሲያስረዱ፤ ሰማያዊ ፓርቲ በወጣት አባላት የተመሰረተና የሚመራ መሆኑን ገልጸው፤ ወጣቱ ደግሞ ከኢትዮጵያ ህዝብ ብዛት ብልጫ ያለው እንደሆነና የወጣቱም ድጋፍ ሰማያዊ ፓርቲን እንዳልተለየው አሳውቀዋል። አያይዘውም ሰማያዊ ፓርቲ የዓላማ ጽናቱ የበረታ በመሆኑና በሀገር ውስጥ የሚያደርገውም እንቅስቃሴ እጅግ የጎላ ስለሆነ ፓርቲውን ሁላችንም መደገፍ ይገባናል ብለዋል።
የፓርቲው አመራሮች
የፓርቲው አመራሮች
በስብሰባው ላይ የተገኙት ኢትዮጵያውያን መግለጫውን ከሰሙ በኋላ ልዩ ልዩ ገንቢ ሃሳቦችን ሰጥተዋል። ተሰብሳቢዎቹ ለፓርቲው ከሰጡት ሃሳቦች ውስጥ፣ “ሰማያዊ ፓርቲ በሀገር ቤት እንደሚያደርገው ሁሉ በዚህም የድጋፍ ማኅበሩ ከሌሎች የሰላማዊ ትግል ከሚያራምዱ ፓርቲዎች ጋር በመገናኘት ራሱን ማዳበር ይገባዋል” የሚለው ይገኝበታል።
ተሰብሳቢዎቹ የመጀመሪያ ጥሪ መሆኑን አስታውሰው በዕለቱ የተገኘው የህዝበ ቁጥር አነስተኛ ነው ተብሎ እንደማይገመት በመግለጽ፣ “ፓርቲው የበለጠ በሰራ ቁጥር ብዙ አባላትና ደጋፊ ማፍራት እንደምትችሉ ካለው ሁኔታ መረዳት ይችላል” በማለት አስተያየት ሰጥተዋል። ስብሰባውን ለመዘገብ በስፍራው የነበረው የኢትዮጵያ ዛሬ ዘጋቢ አብዛኞቹ ተሰብሳቢዎች የነቃ ተሳትፎ ሲያደርጉ እንደነበር ገልጽዋል።
ቀጥሎም ስለ ሰማያዊ ፓርቲ ዓላማና ሥራ የሚያሳይ የቪዲዮ ምስል ለተሰብሳቢው ቀርቧል። በመጨረሻም የሰማያዊ ፓርቲ ሊቀመንበር ኢንጂነር ይልቃል ጌትነት በስልክ ቀርበው ሰብሳቢዎቹንና ተሰብሳቢውን በማመስገን በሀገር ቤት ያለውን ችግር አሳሳቢ ደረጃ ላይ መድረሱን አመላክተው፤ በአሁኑ ጊዜ በፓርቲያቸው አባላትና በሳቸውም ላይ እየተፈጸመ ያለው በደል የበረታ መሆኑን ገልጸዋል። ነገር ግን ከዚህ የከፋ ችግር ሊገጥመን ቢችልም ፓርቲዬም ሆነ እኔ በጽናት ቆመን ትግሉን እንገፋለን በማለት ያላቸውን ቁርጠኝነት አስረድተዋል። ከኢንጂነር ይልቃል አጭር የስልክ መልክት በኋላ ስብሰባው ተጠናቋል። 

(ዘጋቢ: ወለላዬ ከስዊድን)

http://www.goolgule.com/semayawi-party-support-group-introduced-in-sweden/

No comments:

Post a Comment