FREE ALL POLITICAL PRISONERS

FREE ALL POLITICAL PRISONERS
FREE ALL POLITICAL PRISONERS

Monday, October 28, 2013

ኢህአዴግ የዘራውን አጨደ፣ ተጠያቂው ማን ነው?

እሳት አስነሳችሁ በሚል እስሩ ቀጥሏል

fire


በሰላማዊና በህጋዊ መንገድ ተቃውሞ ቢያቀርቡም የኢህአዴግን ጆሮ ማግኘት ያልቻሉ ተበዳዮች ርምጃ ወሰዱ። ሕዝብ ወዶና ፈቅዶ ያልተቀበለው ኢንቨስትመንት ከዘረፋ ተለይቶ እንደማይታይ የአካባቢው ነዋሪዎች አስታውቀዋል። ውድመት የደረሰበት የህንድ ኩባንያ በልማት ባንክ ላይ ኪሳራ ሊያስከትል እንደሚችል ስጋት አለ። ለደረሰው ጉዳት “ተጠያቂው ማን ነው?” የሚል ጥያቄ ተነስቷል። በጥርጣሬ የሚታሰሩ መበራከታቸው በክልሉ ባሉ ተመሳሳይ የእርሻ ኢንቨስትመንት ባለቤቶችን ስጋት ላይ ጥሏል።
ሻይ ቅጠል ለማልማት የተፈጥሮ ጥብቅ ደን እንዲያወድም የተፈቀደለት ቬርዳንታ ሀርቨስት የተባለ ኩባንያ በከፍተኛ ወጪ ያለማውና ለመለቀም በደረሰ ምርት ላይ ማንነታቸው በውል ያልታወቀ ሰዎች እሳት ለቀውበታል። ጥቅምት 12 ቀን 2006 ዓም ደረሰ በተባለው ቃጠሎ ኩባንያው የደረሰበት ሊሳራ እስከ 80 ሚሊዮን ዶላር ሊደርስ እንደሚችል ስለ ጉዳዩ የሚያውቁ አስታውቀዋል።
አንጋፋ እድሜ ጠገብና ረዣዥም የተፈጥሮ ደን በመጨፍጨፍ ጣውላ እያመረተ ሲቸበችብ የነበረው ኩባንያ ሙሉ ንብረቱና ከፍተኛ መጠን ያለው የጣውላ ምርት ከተለያዩ ማሽኖች ጋር ወድሞበታል። የአካባቢው የጎልጉል ምንጮች እንዳሉት ኩባንያው ላይ የደረሰው የእሳት ቃጠሎ ለመሰብሰብ የደረሰውን የሻይ ቅጠል ማሳ አጋይቶታል።
በጋምቤላ ክልል በመዠንግር ዞን፣ በጎደሬ ወረዳ በጉማሬና በካቦ ቀበሌዎች የሚገኝ 5000 ሄክታር በደን የተሸፈነ መሬት በኢንቨስትመንት ስም እንዲሸጥ መወሰኑን ተከትሎ የአካባቢው ነዋሪዎች ተቃውሞ አሰምተው ነበር። በወቅቱ ውሳኔውን “በባዕድ ወራሪ ሃይል እንኳን የማይፈጸም” በማለት የተቹና ቅሬታቸውን የገለጹ ነበሩ።
ሙሉ በሙሉ በደን የተሸፈነ 3012 ሄክታር ድንግል ለም መሬት በሄክታር111 ብር ሂሳብ ለ50 ዓመት የሊዝ ኮንትራት የተሸጠለት ይህ ኩባንያ ጥብቅ ደኑን ከማውደሙ በፊት ውሳኔው እንዲጤን የአካባቢው ህዝብ በወኪሎቹ አማካይነት ለፕሬዚዳንት ግርማ ወ/ጊዮርጊስ ጥያቄ አቀርበው ነበር። በወቅቱ ለጉዳዩ ከፍተኛ ትኩረት በመስጠት የአዲሲቷ ኢትዮጵያ የጋራ ንቅናቄ ድርጊቱን በመቃወም የሚከተለውን ጽሁፍ አትሞ ነበር። ሰሚ ባለመገኘቱ የተፈራው ደረሰ።
ጡረተኛው ፕሬዚዳንት ለአካባቢ ጥበቃ ባለስልጣን በሰጡት ትዕዛዝ መሰረት የተፈጥሮ ደኑ ከመጨፍጨፉ በፊት ውሳኔው እንዲመረመርና እንዲጠና ሚያዚያ 28 ቀን 2002 ዓ ም ለክልሉ ደብዳቤ ልኮ ነበር። ሟቹ ጠ/ሚኒስትር በወቅቱ የአፍሪካ የተፈጥሮ ጥበቃና የአየር ንብረት ተሟጋች ነኝ ያሉበት ወቅት መሆኑን በማስታወስ፣ የፕሬዚዳንቱን መመሪያ በመጠቆም ባለስልጣኑ የጻፈውን የማስጠንቀቂያ ደብዳቤ የክልሉ ፕሬዚዳንት ህዳር 10 ቀን በተጻፈ ደብዳቤ ደመሰሱት። ከላይ የተጠቀሰው ኩባንያ የ50 ዓመቱን ውል ቅድሚያ ክፍያ የአንድ ዓመት 19 ሺህ ዶላር ስለከፈለ ቦታውን እንዲረከብ ዞኑንን አዘዙ።
የበላይና የበታቹ በማይታወቅበት የመለስ አወቃቀር ጥብቅ ደኑ ያለበት መሬት ለህንዱ ኩባንያ ተላለፈ። ህዝብ ያነሳውን ጥያቄ እስከ ፕሬዚዳንቱ ያደረሱት ሊቀመንበር እንደ ወንጀለኛ ተቆጥረው ከሃላፊነታቸው ተባረሩ። ህዝብ የኑሮው መሰረትና የህይወቱ ያህል የሚንከባከበው ደን ተጨፈጨፈ። የአካባቢው ነዋሪዎች እንደሚሉት ደኑ ሲጨፈጨፍ የነበረው ሃዘን በቃል የሚገለጽ አልነበረም።timber log
ባገኘው ከፍተኛ የደን ምርት ጣውላ ማምረት የጀመረው ኩባንያ መጋዘን ገንብቶ የጣውላ ንግድ ውስጥ ገባ። አሁን ድረስ ንዴቱና የበደል ስሜቱ ያለቀቀቃቸው የአካባቢው ነዋሪዎች የተካሄደባቸውን ግፍ “ዝርፊያ” እያሉ ነው የሚጠሩት።
ህግን ጠብቀው ኢህአዴግን ያሳሰቡት የአካባቢው ነዋሪዎች አሁንም ቢሆን በእስርና በድብደባ በማሰቃየት ኢንቨስትመንትን /ነዋሪዎቹ ዝርፊያ ነው የሚሉት/ በክልሉ ቀጣይ ማድረግ አይቻልም። አስቀድሞ ባቀረቡት አቤቱታ መሰረት ኢህአዴግና ኩባንያው ጆሮ ሰጥተዋቸው ቢሆን ኖሮ እንዲህ ያለ አደጋ ሊፈጠር እንደማይችል አስተያየት ሰጡ አሉ።
92 ሚሊዮን ብር በላይ የኢትዮጵያ ልማት ባንክ እዳ ያለበት የእርሻ ድርጅት፣ ንብረቱ በእሳት ከወደመ በኋላ የተሸከመው እዳ አጀንዳ ሆኗል። የደረሰበት ውድመት ከፍተኛ በመሆኑ ክልሉንና ኢህአዴግን ካሳ እንደሚጠይቅም ከወዲሁ ተሰምቷል። ዜናውን ያቀበሉ ክፍሎች “ህዝብ ላልተቀበለው ኢንቨስትመንት ካሳና የልማት ባንክ ላይ ለደረሰው ኪሳራ ተጠያቂው ኢህአዴግ ነው” የሚል ጥያቄ መነሳቱን አመልክተዋል።
ለአበባ እርሻ ላስቲክና ኬሚካል በማስያዝ ልማት ባንክን እያለቡ የተሰወሩ በርካታ ድርጅቶችና ለስርዓቱ ቅርበት ያላቸው ሸሪኮቻቸው መኖራቸውን በማስታወስ በጋምቤላ ተመሳሳይ ድርጊት ሊፈጸም እንደሚችል የዜናው ምንጮች ጠቁመዋል። ካራቱሪ በኪሳራ መንገዳገዱን፣ ሼኽ መሐመድ ሁሴን አላሙዲ በ”ውክልና” ለሳዑዲ አረቢያ ቀለብ እንዲያመርት የተከሉት ሳዑዲ ስታርና ሌሎች የህወሃት ሰዎች ከተለያዩ የአገር ውስጥ ባንኮች ከፍተኛ ገንዘብ መበደራቸውን ገልጸዋል።
“ህዝብን ያለፈቃዱ በማፈናቀልና መሬቱን በመቀማት የሚከናወን ኢንቨስትመንት ሁሌም አደጋ ላይ መሆኑ አያጠራጥርም” በማለት የአዲሲቷ ኢትዮጵያ የጋራ ንቅናቄ አኢጋን ዋና ዳይሬክተር አቶ ኦባንግ ለጎልጉል ገልጸዋል። “ኢንቨስትመንት እንኳን ደህና መጣህ በሚል ህዝብ ካልተቀበለው ዘረፋ ነው” ያሉት አቶ ኦባንግ “በሰላማዊና በሰለጠነ መንገድ ድምጹን ሲያሰማ ጆሮ ያጣ ህዝብ ተቃውሞውን ገለጸ” በማለት በደረሰው ውድመት ባይደሰቱም ለውድመቱ ተጠያቂው ኢህአዴግና ከኢህአዴግ ጋር ተሻርኮ ዝርፊያ ያከናወነው ድርጅት እንደሆነ አመልክተዋል።
ካሩቱሪና ሳዑዲ ስታርን ጨምሮ ህዝብ ላይ በተፈጸመ ግፍ ሃብት ለማፍራትና ለመበልጸግ የሚያስቡ ትልቅ ግንዛቤ ሊወስዱ እንደሚገባ ያሳሰቡት አቶ ኦባንግ “ኢህአዴግ ዝርፊያና ኢንቨስትመንትን ለይቶ መሔድ ካልቻለ ስጋቱ እየጨመረ ይሄዳልና ከስህተት በመመለስ ህዝብ በሚፈቅደው መልኩ ማስተናገድ ግድ ነው” ሲሉ አሁንም ጆሮ የለውም ለሚባለው ኢህአዴግ ማሳሰቢያ አዘል ምክር ለግሰዋል። ባለሃብት የሚባሉትም ከዚህ ታላቅና አሳዛኝ ውድመት ሊማሩና ህዝብ “እንኳን ደህና መጣችሁ እንዲላቸው ህዝብ ከሚቃወመው ዝርፊያና አሰራር ራሳቸውን ሊያገሉ ይገባል” ብለዋል።
የክልሉ ፕሬዚዳንት ቃጠሎውን ማመናቸውን ሪፖርተር በእሁድ እትሙ ያስታወቀ ሲሆን አጣሪ ኮሚቴ ተቃቁሞ አደጋውን ያደረሱት እነማን ናቸው የሚለው እየተመረመረ እንደሆነ ጠቁሟል። የክልሉ የጎልጉል ምንጮች በርካታ ሰዎች እሳት አስነስታችኋል በሚል መታሰራቸውና በፌዴራል አንጋቾች እየተመረመሩ መሆኑን አረጋግጠዋል። እሳት ያስነሱትን ለማጋለጥ በሚል በየመንደሩ በሚደረግ ማዋከብ ነዋሪዎቹ መማረራቸውን ተናግረዋል። ለጊዜው የእስረኞች ቁጥር ባይታወቅም ወደ ማዕከል የተላኩ በርካታ እንደሆኑም ገልጸዋል። በማያያዝም ሁኔታው በዚህ ከቀጠለ ኢህአዴግም ሆነ ማንም ተጠቃሚ ስለማይሆን ህዝብን ማዳመጥ ሊቀድም እንደሚገባው ጠቁመዋል። (ፎቶ፡ ለማሳያነት ብቻ)

ከእሁድ እስከ እሁድ

(የሳምንቱ አጫጭር ዜናዎች ከተለያዩ ምንጮች)

mk


“መጽሐፈ ቅዳሴ” ወደ ኦሮምኛ ተተረጎመ
የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተክርስትያን “መጽሐፈ ቅዳሴ” ወደ ኦሮምኛ ቋንቋ ተተረጎመ፡፡ ለብዙ ዘመናት “መጽሐፈ ቅዳሴ”ን በግእዝ እና በአማርኛ ስትጠቀምበት የቆየችው ቤተክርስትያኗ፤ መፅሃፉን በኦሮምኛ ማስተርጎም የጀመረችው በ1999 ዓ.ም እንደሆነ ታውቋል፡፡ የመጽሐፉ መተርጎም በኦሮሚያ ክልል ላሉ አብያተ ክርስትያናት በኦሮምኛ ለመቀደስ ያስችላቸዋል ተብሏል፡፡
የቤተክርስትያኒቱ ቅዱስ ሲኖዶስ እያካሄደ ባለው የጥቅምት ምልዐተ ጉባዔው ትኩረት ከሰጣቸው ዋና አጀንዳዎቹ አንዱ ስብከተ ወንጌልን ማዳረስ እንደሆነ የገለፁት ፓትርያርክ ብፁዕ ወቅዱስ አቡነ ማትያስ፤ የመጽሐፉ ሕትመት እንዲቀላጠፍ ትዕዛዝ እንዳስተላለፉም ለማወቅ ተችሏል፡፡ “መጫፈ ቂዳሴ” በሚል ርዕስ የተተረጎመው የኦሮምኛ መጽሐፉ፤ በቅርቡ ዝግጅቱን የተቀላቀሉትን ብፁዕ አቡነ ዮሴፍን ጨምሮ፣ በርካታ ጳጳሳት ተሳትፈውበታል፡፡ መጽሐፉ በብርሃንና ሰላም ማተሚያ ድርጅት እየታተመ ሲሆን በዚህ ሳምንት ከተጠናቀቀ በቅዱስ ሲኖዶስ ጉባዔ መዝጊያ ላይ ሊመረቅ እንደሚችል ታውቋል፡፡ (አዲስ አድማስ)
በኬንያና በዚምባብዌ የታሠሩ ኢትዮጵያውያን ይከሰሳሉ ተባለ
በህገወጥ መንገድ ወደ ኬንያና ወደ ዚምባብዌ ድንበር ሲያቋርጡ ተይዘው የታሰሩ መቶ ያህል ኢትዮጵያውያን ክስ ይጠብቃቸዋል ተባለ፡፡
ሰሞኑን ወደ ናይሮቢ ሊገቡ ሲሉ በፖሊስ የተያዙት ሀምሳ ሶስት ወጣት ኢትዮጵያውያን ህጋዊ ፓስፖርት እንደሌላቸውና ከአማርኛ ውጪ በእንግሊዝኛ መግባባት እንደማይችሉ የሳምራ ፖሊስ ኮማንደር ኤል ሙታሚያ ተናግረዋል፡፡ ከስደተኞቹ ጋር፣ ህገወጥ የሰዎች ዝውውር የሚያካሂዱ ደላሎች ናቸው የተባሉ ኬንያዊያንም ታስረዋል፡፡Ethiopia, Abudrafi, treating kala azar and HIV, November 2010.
በሌላ በኩል የዚምባቡዌን ድንበር አቋርጠው ወደ ደቡብ አፍሪካ ሊሄዱ የነበሩ ሰላሳ ስምንት ኢትዮጵያውያን በሃገሪቱ ፖሊስ ተይዘዋል፡፡ ወጣት ስደተኞቹ ወደ ዙምባብዌ የገቡት በህገወጥ መንገድ ስለሆነ ክስ ይመሰረትባቸዋል ሲል ፖሊስ ገልጿል፡፡
የኢትዮጵያ የውጪ ጉዳይ ሚኒስቴር ቃል አቀባይ አምባሳደር ዲና ሙፍቲ፣ በኬንያና በዙምባቡዌ ለታሰሩ ስደተኞች ከመንግስት እገዛ ይደረግላቸው እንደሆነ ከአዲስ አድማስ ተጠይቀው፣ “መንግስት ሁልጊዜም ዜጐቹን የመርዳት ፍላጐት አለው፤ በየአገሩ ያሉ ኤምባሲዎቻችንም በዚህ ፖሊሲ መሰረት እየሰሩ ነው” ብለዋል፡፡
በቅርቡ የወጣው የአለም አቀፍ የስደተኞች ድርጅት መረጃ እንደሚለው በየአመቱ ከሀያሺ በላይ የሚሆኑ ኢትዮጵያውያንና ሶማሊያዊያን በኬንያ በኩል ደቡብ አፍሪካ ይገባሉ፡፡ (አዲስ አድማስ)
አውራምባ ታይምስ አገሯ ገባች
ኢህአዴግ ለህይወቴ ያሰጋኛል በሚል አሜሪካን አገር ከላላ አግኝቶ የነበረው የአውራምባ ጋዜጣ ባለቤትና ዋና አዘጋጅ አቶ ዳዊት ከበደdawit k አገሩ መግባቱ ተገለጸ። ዳዊት በ1997 ምርጫ ወቅት ከታሰሩት ጋዜጠኞች ጋር እስር ቤት ነበር። ከሌሎች የሙያ ባልደረቦቹ ጋር ከእስር ሲፈታ ሌሎች በሙያቸው ለመስራት ጠይቀው ፈቃድ ሲከለከሉ ዳዊት ግን ዳግም የጋዜጣ ፈቃድ ማግኘት ችሎ ነበር። ከእስር መልስ ከሁለት ዓመት በፊት ከዳዊት ጋር ኢህአዴግን በመሸሽ የተሰደደችውን አውራአምባ ታይምስን ወረቀት አልባ በሆነ መልኩ አቋቁሞ የነበረው ዳዊት ወደ አገር ቤት ለመመለሱ የሰጠው ምክንያት የዲያስፖራው ጽንፈኛ አስተሳሰብና መወቀስን አለመውደድ አንደሆነ አስታውቋል። ጋዜጠኛነት አሸባሪነት በሆነባት ኢትዮጵያ ዳዊት ሥራው ያለው እዚያ ነው ቢልም “ዳያስፖራውን በጥብጦ ሲያበቃ ተልዕኮውን አሳክቶ ተመለሰ” ብለውታል፡፡ በስፋት የተቃውሞ አስተያየት የሚሰነዝሩበት ክፍሎች ግን “ስለከሸፈበት አገሩ ተመልሶ ኢህአዴግን ተቀላቀለ፤ አድዋ ገባ” ብለውታል።
ኢዴፓ ከተቃዋሚ ፓርቲዎች እውቅና ጠየቀ
በገዥው ፓርቲ ፖለቲካዊ ጉዳዮች ዙሪያ ኢዴፓ ባካሄደው ግምገማ፣ ኢሕአዴግ የአገሪቱን የዴሞክራሲ ሥርዓት ግንባታ ከጊዜ ወደ ጊዜ እያሻሻለና እያጠናከረ ከመሄድ ይልቅ፣ ይበልጥ እየተዳከመ እንዲመጣ ማድረጉን ገልጿል፡፡ ገዢው ፓርቲ ከፕሮፓጋንዳ ባለፈ ለዴሞክራሲ ሥርዓት መጠናከር ምንም ዓይነት ተጨባጭ ዕርምጃ እየወሰደ እንዳልሆነና ይህም በአገሪቱ የጽንፈኝነት ፖለቲካና አክራሪነት የበለጠ እየተጠናከረ እንዲመጣ አድርጓል ይላል የኢዴፓ ግምገማ፡፡
“በአሁኑ ወቅት በአገራችን የፖለቲካና የኢኮኖሚ ሙስና፣ የፖለቲካ ጽንፈኝነትና አክራሪነት ለዘለቄታው ዕድገት ብሎም ለሰላምና ለዴሞክራሲያዊ ሥርዓት ግንባታ እንቅፋት በመሆን፣ አገራዊ አደጋ እየሆነ መጥቷል፤” ይላል ኢዴፓ ገዢው ፓርቲን በገመገመበት ወቅት የደረሰበትን ድምዳሜ ሲገልጽ፡፡edp
ኢዴፓ በጉባዔው ተቃዋሚ ፓርቲዎችንም ተችቷል፡፡ ተቃዋሚዎች የኢዴፓን የተቃዋሚነት ሚናና ህልውና የካዱና፣ በሕዝቡ ዘንድ በበጎ መንፈስ እንዳይታይ ሆን ብለው ሴረኛ አሉባልታዊ ዘመቻ የሚያካሂዱ መሆናቸውን መገንዘቡን ገልጿል፡፡ እነዚህ ፓርቲዎች የወቅቱ ትግል ተጠናክሮ ለድል እንዳይበቃ ዋነኛ እንቅፋት መሆናቸውን ገልጾ ሕዝቡ የእነዚህን ተቃዋሚ ኃይሎች ትክክለኛ ማንነት እንዲገነዘብ ጠይቋል፡፡
በመቀጠልም ተቋዋሚ ፓርቲዎች ራሳቸውን ቆም ብለው መመርመርና ካለፈው ስህተታቸው መማር ካልቻሉ በስተቀር፣ በትብብር ለመሥራት ሙከራ እንደማያደርግና ከዚህ ተግባራቸው ተላቀው ዕውቅና እንዲሰጡት ኢዴፓ ጥያቄ አቅርቧል፡፡
የኢዴፓ ሥራ አስፈጻሚ የጠቅላላ ጉባዔውን አቋም ከገለጸ በኋላ ከጋዜጠኞች ለቀረቡለት ጥያቄዎች ማብራርያ ሰጥቷል፡፡ ከቀረቡለት ጥያቄዎች መካከል ከፀደቀ ጊዜ ጀምሮ መነጋገሪያነቱ ያልቀዘቀዘው የፀረ ሽብርተኝነት ጉዳይ ላይ ኢዴፓ ያለውን አቋም እንዲገልጽ የቀረበው አንዱ ነው፡፡የፓርቲው አዲሱ ፕሬዝዳንት አቶ ጫኔ ከበደ እንደገለጹት፣ ኢዴፓ የፀረ ሽብር ሕጉን ይደግፋል፡፡ ሥልጣን ቢይዝ የፀረ ሽብር ሕጉ እንደሚያስፈልገው አቶ ከበደ ገልጸው፣ ነገር ግን መሻሻል ያለባቸው ነጥቦች መኖራቸውን አስረድተዋል፡፡
መሻሻል ካለባቸው ነጥቦች መካከልም ሰብዓዊ መብቶችን የሚጥስ ይዘት ያላቸው ይገኙበታል፡፡ እነዚህ ነጥቦች ሕጉ አቅጣጫውን እንዲስት ማድረጋቸው አቶ ጫኔ ገልጸዋል፡፡ለዚህም ማሳያው ጋዜጠኞችና መብታቸውን የሚጠይቁ ግለሰቦች በቁጥጥር ሥር እንዲውሉ መደረጉ ነው ብለዋል ፕሬዝዳንቱ፡፡ (ሪፖርተር)
አየር ሃይል አዲስ አዛዥ ተመደበለት
የአቶ መለስ ዜናዊን ህልፈት ተከትሎ ለስልሳ ከፍተኛ መኮንኖች የጀነራልነት ሹመት ያደለው ኢህአዴግ በመከላከያና በደህንነት ተቋማቱ ሃላፊዎች ዙሪያ ሹም ሽር እንደሚያደርግ በተለያዩ መንገዶች ሲገለጽ መሰንበቱ ይታወቃል። በመከላከያ ሰራዊት ውስጥ የአንድ ብሄርና የህወሃት አባላት ብቻ አመራሩን መያዛቸው ቅሬታ መፍጠሩም በስፋት እየተነገረ ይገኛል።
eth afይህንን ተከትሎ ኢህአዴግ የጀነራሎች አዲስ ሹም ሽር ማካሄዱን አዲስ አድማስ ምንጮቹን ገልጾ አስታወቀ። ጋዜጣው እንደጠቆመው የአየር ሃይል አዛዥ በመሆን ሜጀር ጀነራል አደም መሀመድ ተሹመዋል። በቀድሞው የአየር ሃይል አዛዥ ሜጀር ጀነራል ሞላ ሀይለማርያም ምትክ  የተሾሙት ጀነራል አደም የአየር ሀይል ፓይለት የነበሩና በሱዳን አቢዬ ግዛት የሠላም አስከባሪ ሀይል ምክትል አዛዥነት ያገለገሉ፣ እንዲሁም የመከላከያ ዘመቻ መምሪያ ኃላፊ እንደነበሩ ጋዜጣው አመልክቷል።
በሌሎች የመከላከያ የስራ ምድብ ቦታዎች ላይ የአዛዦች የምደባ ለውጥ ተደርጓል።  አዲስ የሀላፊነት ምደባ ከተሠጣቸው ውስጥ ሌተናል ጀነራል ሠአረ መኮንን፣ ሌተናል ጀነራል አበባው፣ ሜጀር ጀነራል ዮሀንስ ወልደጊዮርጊስ፣ ሜጀር ጀነራል ገብራት አየለ እና ሌሎችም እንደሚገኙበት ያስታወቀው አዲስ አድማስ የሃላፊዎቹን የሹመት ምድብ ቦታ አላስታወቅም።
በርሊን፤ የሜርክል የእጅ ስልክና አሜሪካ
የጀርመን መራሂተ-መንግስት አንጌላ ሜርክል የእጅ ስልክ በዩናይትድ ስቴትስ መንግሥት የስለላ ተቋም ተጠልፏል የሚለዉ ዜና እያነጋገረ ነዉ። ዩናይትድ ስቴትስ ድርጊቱን እንዳልፈፀመች በመጥቀስ አስተባብላለች። ጉዳዩ በአውሮጳ መሪዎች ዘንድ ከፍተኛ ትኩረት ተሰጥቶታል።
ጀርመን የመራሂተ መንግስቷ ስልክ ሳይሰለል አይቀርም በሚል በበርሊን የዩናይትድ ስቴትስ አምባሳደርን ዛሬ ለማነጋገር መጥራቷ ተዘገበ። የዉጭ ጉዳይ ሚኒስትር ጊዶ ቬስተርቬለ በጀርመን ለአሜሪካኑ አምባሳደር ጆን ኤመርሰን በዚህ ረገድ የጀርመንን ግልጽ አቋም እንደሚያቀርቡም ተገልጿል። የጀርመን መገናኛ ብዙሃን የአሜሪካን የስለላ ተቋም NSA የመራሂተ መንግስት አንጌላ ሜርክልን የእጅ ስልክ ሳይጠለፍ አልቀረም የሚል መረጃ ይፋ አድርገዋል። ዋሽንግተን ግን አስተባብላለች። ይህ ከተሰማ በኋላም ሜርክል ራሳቸዉ ለፕሬዝደንት ባራክ ኦባማ ስልክ በመደወል የተባለዉ እዉነት ከሆነ ፍፁም ተቀባይነት የለዉም ማለታቸዉን ቃል አቀባያቸዉ ሽቴፈን ዛይበርት ገልጸዋል። የመከላከያ ሚኒስትር ቶማስ ደሚዚየር በበኩላቸዉ፤ “የሰማነዉ እዉነት መሆኑ ከተረጋገጠ በጣም መጥፎ ነዉ። አሜሪካዉያን እዉነተኛ ጓደኞቻችን ነበሩ አሁንም ናቸዉ፤ ሆኖም እንዲህ ሊቀጥል አይችልም።”am
ኋይትሃዉስ ኦባማ ትናንት ከሜርክል ጋር ባደረጉት የስልክ ዉይይት የአሜሪካን የስለላ ተቋም እሳቸዉን እንደማይሰልል ማረጋገጣቸዉን ቢገልጽም ከዚህ ቀደም ስለመደረጉ ያለዉ የለም። የኋይት ሃዉስ ቃል አቀባይ ኤይ ካርኔ፤
“እኔ ልገልጽ የምንችለዉ ፕሬዝደንቱ ዩናይትድ ስቴትስ መራሂተ መንግስቷን በወቅቱ እንደማትሰልል፤ ወደፊትም እንደማትሰልል እንዳረጋገጡላቸዉ ነዉ። ዩናይትድ ስቴትስ ከጀርመን ጋ ሰፊ የጸጥታ ችግሮችን በተመለከተ ላለን የቀረበ ትብብር ትልቅ ዋጋ ትሰጣለች።”
ስለሜርክል ሞባይል መጠለፍ የተሰማዉ የNSA በቀድሞዉ ባልደረባ ኤድዋርድ ስኖዉደን ጉዳዩን አጋልጦ በርካቶች መራሂተ መንግስቷ ነገሩን ያደባብሳሉ የሚል ጥርጣሬ እየተሰነዘረ ባለበት ወቅት ነዉ። የስልካቸዉ መጠለፍ ያስቆጣቸዉ ሜርክል በሳምንቱ መጀመሪያ ከ70 ሚሊዮን በላይ የስልክና ኢሜል ልዉዉጦች መጠለፋቸዉ ካናደዳት ፈረንሳይ መሪ ፍራንስዋ ኦሎንድ ጋ በጉዳዩ ላይ ዛሬ እንደሚነጋገሩ የፈረንሳይ ዜና ወኪል ከብራስልስ ዘግቧል።
am1ይህ በእንዲህ እንዳለም ብራስልስ ላይ የተሰባሰቡት የአዉሮፓ ኅብረት አባል መንግስታት መሪዎች የግለሰብ ዜጎችም ሆነ የመሪዎች የግል ጉዳይ ላይ የሚደረግ ስለላ ተቀባይነት እንደማይኖረዉ አመልክተዋል። የፈረንሳይ የዜና ወኪል የኅብረቱ የፍትህ ኮሚሽነር ቪቫነ ሬዲንግ ቃል አቀባይ ኮሚሽነሯ መረጃን የመከላከል ርምጃ የአንጌላ ሜርክል የእጅ ስልክንም ሆነ የግለሰብ ዜጎችን የኢሜል ልዉዉጥ ላይ በእኩልነት ተግባራዊ ልሆን ማለታቸዉን ዘግቧል። ኮሚሽነሯ የኅብረቱ ጉባኤ ማብራሪያ የሚጠይቅበር ሳይሆን ርምጃ የሚወስድበት ጊዜ አሁን ነዉ ማለታቸዉም ተጠቅሷል። ከወራት በፊት ለአዉሮፓ የመረጃ መከላከል ህግ እንዲጸድቅ ቀርቦ 28 አባል መንግስታት በጉዳዩ ልዩነት ስለነበራቸዉ ታግዷል። የአዉሮጳ ኅብረት ኮሚሽነር ሆሴ ማኑዌል ባሮሶም በበኩላቸዉ አዉሮጳዉያን የግለሰብን የግል ጉዳይ ማክበርን እንደመሠረታዊ መብት ይመለከቱታል ነዉ ያሉት። የኅብረቱ አባል ሃገራት መሪዎች ዛሬ እና ነገ የኤኮኖሚ ጉዳዮች ላይ የሚያተኩር ጉባኤ ለማካሄድ የተሰባሰቡ ሲሆን የጀርመን መራሂተ መንግስት ስልክን የመጠለፍ ወሬ ትኩረታቸዉን ወደሌላ ሳይስብ እንዳልቀረ እየተነገረ ነዉ። (ከጀርመን ሬዲዮ የተወሰደ)
ሶስት የአማራ ክልል አመራሮች ታገቱ
የአማራ ወጣቶች የጋራ ንቅናቄ በአማራ ክልል ላኩማ ወረዳ ሁለት የሚሊሽያ ሀላፊዎችንና አንድ የወረዳ አስተዳዳሪን በቁጥጥር ስራ ማገቱን ኢሳት ጥቅምት 15 ቀን 2006 ዓ ም አስታወቀ።
ንቅናቄው ቀደም ሲል  22 የፖለቲካ አመራሮች በላኩማ ወረዳ በሚገኘው በሰላ አንደኛ ደረጃ ትምህርት ቤት ውስጥ በስብሰባ ላይ እንዳሉ በቁጥጥር ስር ካዋለ በኋላ መልቀቁን ገልጾ፣ ሶስቱን አመራሮች ግን አሁንም ድረስ በቁጥጥር ስር አድርጎ እንደሚገኝ
ኢሳት አመልክቷል። የተያዙት አመራሮች በቁጥጥር ስር ውለው ከነበሩት ፓለቲከኞች ዋነኛ እና የአካባቢውን ህብረተሰብ በመበደል የሚታወቁ እንደሆነ ንቅናቄው አመልክቷል፡፡
አቶ አልዩ ጋሹ የላኩማ ወረዳ አስተዳደር ስብሳቢ፣ አቶ አንበሱ በዙ የሰገላ ወረዳ ሚሊሺያ ዘርፍ ሀላፊ፣ እንዲሁም አቶ ኢያና ካሳ የባምበል ወረዳ ሚሊሽያ ዘርፍ ሀላፊ ሶስቱም በቁጥጥር ስር የሚገኙ ሀላፊዎች እንደሆኑ ንቅናቄው መግለጹኢነ ያመለከተው ኢሳት ዜናውን ከገለልተኛ አካል አለማረጋገጡን ጠቁሟል።
ላኩማ ወረዳ ብዙ የሙስናና የመልካም አስተዳደር እጦት ያለባት ስፍራ እንደሆነች የገለጸው ንቅናቄው ከዚህ በፊት የአካባቢውን ሰዎች ሲያጉላላ የነበረ ሀላፊ እርምጃ ተወስዶበት እንደነበር አስታውሷል፡፡ ንቅናቄው በክልሉ ባሉ ህዝቦች ላይ የሚፈፀመውን የሰብዓዊ መብት ጥሰትና ሰቃይ እንዲቆም መጠየቁንና የጎጃም ዞን ዋና የህወሀት ባለስልጣን በነበሩት አቶ ዳኘ ገብረማርያም ላይ በቅርቡ እርምጃ መወሰዱን መዘገቡን ኢሳት በዜናው አመልክቷል።

Sunday, October 27, 2013

ቤቱን በእሳት ለኩሶ “እንዴት ያለ ብሩህ ቀን እንደሆነ ተመልከቱ” ይላል

አንድ እሥር ቤት ውስጥ የሆነውን ነገር ቆይተው ሲያስቡት ተረት እንጂ በዕውነት በታሪክ የተከሰተ አይመስልም፡፡ 
የእሥር ቤቱ ክፍል አራት በአራት ነው ፡፡ ከሃምሣ እስከ ስልሣ የሚሆኑ እሥረኞች ታጭቀውበታል፡፡ የሚተኙት እንደጨፈቃ ተጨፍቀው ነው፡፡ ጠዋት ሲነጋ ቀኑን ለመግፋት ዳማ፣ ዶሚኖ፣ ቼዝ እና እዚያው በተሠራ ወረቀት ካርታ ይጫወታሉ፡፡ 
የእሥረኛው ዓይነት እንደየጉዳዩ የተለያየ ነው፡፡ በፖለቲካ የታሠረ አለ፡፡ በኢኮኖሚ (ገንዘብ ነክ) ጉዳይ የሚመጣ አለ - ደረቅ ወንጀል ይሉታል፡፡ በእግሩ ድንበር አልፎ ለመሄድ ሲሞክር ተይዞ የሚታሠር አለ “እግር እላፊ” ይሉታል በእሥረኞቹ አጠራር፡፡ የዘማች ሚስት በማማገጥ የሚታሠር አለ “ጭን እላፊ” ይሉታል፡፡ በስርቆሽ የሚታሠር አለ “እጅ - እላፊ” ይሉታል፡፡ በዘለፋ፣ መንግሥት (መሪ) በመሰደብ የሚታሠር አለ - “አፍ -እላፊ” ይሉታል፡፡ 
እሥር ቤቱ ክፍል አሁን ዳማ የማጫወቱት ሁለት ሰዎች፤ አዕምሮአቸውን ነካ የሚያደርጋቸው ናቸው፡፡ በአፍ - እላፊ ነው የታሠሩት፡፡ ዳማ እየተጫወቱ ይወያያሉ፡፡ 
“ይሄ መንግሥት ዕብድ ማሠሩ አይገርምህም?” ይላል አንደኛው፡፡ 
“አሣሪው ይሁን ታሣሪው ዕብዱ? ገና አልለየምኮ” ይላል ሁለተኛው፡፡ 
“እኔ መንግሥት ይመስለኛል ዕብድ”
“እኔ ግን እኛ ዕብድነታችንን ቢያዘልቅልን ከመንግሥት እንሻላለን እላለሁ”
“ይልቅ ዳማችንን እንጫወት፡፡ ለሁላችንም የሚሻለን፤ ህዝብ ቢያብድ ነበር” 
“ለምን?”
“አለዛ ድንዝዝ ፍዝዝ ብሎ ይቀራላ!”
“በል እሺ ዳማችንን እንጫወት?”
ዳማቸውን መጫወታቸውን ይቀጥላሉ፡፡ 
አንደኛው የሌላኛውን ንጉሥ፤ በወታደርም፣ በንጉሥም የሚበላት ሁኔታ ይፈጠራል፡፡ 
ሁለተኛው - “በንጉሥ ትገደዳለህ፡፡ ንጉሤን በንጉሥ ነው እንጂ በወታደር አትበላኝም” ይላል፡፡ 
አንደኛው - “በየትኛውም ብበላህ ጨዋታው ያልቃል፡፡ በፈለኩት እበላለሁ” 
ሁለተኛው - “በጭራሽ! በንጉሥ ትገደዳለህ”
አንደኛው - “እኔ እምልህ፤ አንዴ ሞት ከተፈረደብህ በቺቺ ግደሉኝ በክላሽ ግደሉኝ እያልክ ምን ያጨቃጭቅሃል?” አለው፡፡ 
* * *
በትንሹም በትልቁም ነገር ከማበድ ይሰውረን፡፡ የመሞቻ መሣሪያ ከማማረጥ ያድነን፡፡ የፖለቲካ፣ የኢኮኖሚና የማህበራዊ እንከኖቻችን ጥቅል ውጤት ማስጨነቁና ማሳሰቡ የሀገርና የህዝብ ስሜት ላለው ሁሉ አይቀሬ ነው፡፡ በተለይም ዱሮ የእጅ - እላፊ ይባል የነበረው የምዝበራና አገርን የማራቆት ተግባር፣ (ዛሬ ሙስና የተባለውን)፤ “ባንዱ ያለማ ባንዱ ያደለማ” ሆኗል፡፡ አገር ትልቅ ለውጥ ላይ ናት፤ ከፍተኛ የትራንስፎርሜሽን ሂደት ላይ ነን እየተባለ፤ በጐን የዝርፊያ የኮንትሮባንድ እና “በአንድ ጀንበር ፎቅ ሠርቼ ልደር” ዓይነት ዘመናዊ ምዝበራ ይታያል፡፡ “በአንዴ ዘጋ/ዘጋች” ዛሬ የተለመደ ቋንቋ ነው፡፡ እንደነናይጄሪያና እንደነናይሮቢ (“ናይሮበሪ” እንደተባለው) ዐይን - ያወጣ የቀን ተቀን ዘረፋ የሚመጣው ከላይ እስከታች እየተወሳሰበ ያለው ሙስና ፍፁም ወደፈጠጠ ደረጃ ሲደርስ ነው፡፡ “ልጄን የእንቁላሉ ዕለት ቆንጥጬው ቢሆን በሬ ሲሰርቅ አይያዝም ነበር” አለች እንደሚባለው ነው፡፡ 
አንድም ሙስናው በየአቅጣጫው መሆኑ፤ አንድም ደግሞ ቢሮክራሲያዊ መጠቅለያ መኖሩ እጅግ ውስብስብ ያደርገዋል፡፡ (ዱሮ “ቢሮክራሲያዊ ካፒታሊዝም ይውደም” የሚል መፈክር ነበር፤ ነብሱን ይማረው!) በዚህ ላይ የግለሰቦች አሻጥር ሲጨመርበት፣ ከቁጥጥር ውጪ ወደሆነ ደረጃ ይሸጋገራል፡፡ የመሬት አሰቃቂ አወሳሰድ፣ ከፍተኛ የኮሚሽንና የድለላ ሥራ፣ አደገኛ ወገናዊ አሠራር…በአስደንጋጭ የድህነት መቀመቅ ውስጥ ለገባች አገር ከምትሸከመው በላይ ትከሻ አጉብጥ ሸክም ይሆንባታል፡፡ የባሰ ዘግናኝ የሚሆነው ደግሞ ከዕለት ወደ ዕለት በምዝበራ ምክንያት መታሰር ራሱ እየተለመደና ቀላል እየመሰለ መምጣቱ ነው፡፡ “እገሌ ታሠረኮ” ሲባል፤ 
“ተወው በልቷል - የሚበቃውን ቀለብ አከማችቷል”
ማለት እንደሰላምታ የሚነገር መሆኑ አሳዛኝ ነው፡፡ 
ዱሮ “በሥራው አጋጣሚ በእጁ የገባውን የመንግሥት ገንዘብ ለግል ጥቅሙ በማዋሉ” የሚለው ሐረግ ነበር ሬዲዮንና ቴሌቪዥን ያጣበበው፡፡ ዛሬ ዳር እስከዳር በየሰው አፍ የሚወራ ነገር ሆኗል፡፡ ዝርፊያው ዓይነት በዓይነት ሆኗል፡፡ ተወርቶም በቀላሉ ይረሳል፡፡ በተለይ ለህብረተሰብ ቀጥተኛ መጥፊያ የሚሆኑ እንደመድሃኒት ያሉ የኮንትሮባንድ ዕቃዎች ባመቸው መንገድ ሁሉ ተበርዘው ከተባዙ፣ ምን ያህል አሰቃቂ የሆነ ዕልቂት እንደሚያስከትሉ መገመት አያዳግትም፡፡ የሚያስገኙት ገንዘብ የትየለሌ፣ የሚፈጁት ህዝብ የትየለሌ!!
ማናቸውንም የጥፋት ድርጊት የሚፈጽሙ ወገኖች ለሀገር እንደቆሙ፤ የህዝብ ልጆች እንደሆኑ አድርገው መጮሃቸውና ሀቀኛ መምሰላቸው፤ ሌላው እንዳይናገር በር ይዘጋል፡፡ They shout at most against the vices they themselves are guilty of እንደሚሉት ነው ፈረንጆቹ - ጅራፍ እራሱ ገርፎ እራሱ ይጮህ እንደማለት ነው፡፡ ጩኸቱ በቅጡ ለገባው አገር - ወዳድ ሰው ግን፤ “ቤቱን አቃጥሎ እንዴት ብሩህ ቀን እንደሆነ ተመልከቱ” አለ እንደተባለው ነው፡፡ ልዩነቱ ያኛው ለግሉ እየተጠቀመ፤ ይሄኛው የገዛ ንብረቱን ጭምር እያወደመ የሚጃጃል መሆኑ ነው፡፡ ሁለቱንም መዋጋት ተገቢ ነው!

የጀነራል መኮንኖች የምደባ ለውጥ ተካሄደ

et.

ሜጀር ጀነራል አደም መሀመድ የአየር ሀይል አዛዥ ሆነው መሾማቸውንና የአዛዥ ጄነራሎች ላይም የምደባ ለውጥ መደረጉን ምንጮቻችን አመለከቱ፡፡ በአየር ሀይል አዛዥ በነበሩት ሜጀር ጀነራል ሞላ ሀይለማርያም ምትክ የተሾሙት ሜጀር ጀነራል አደም የአየር ሀይል ፓይለት የነበሩና በሱዳን አቢዬ ግዛት የሠላም አስከባሪ ሀይል ምክትል አዛዥነት ያገለገሉ እንዲሁም የመከላከያ ዘመቻ መምሪያ ኃላፊ ነበሩ፡፡


በሌሎች የመከላከያ የስራ ምድብ ቦታዎች ላይ የአዛዦች የምደባ ለውጥ መደረጉን የተናገሩት ምንጮች፣ አዲስ የሀላፊነት ምደባ ከተሠጣቸው ውስጥ ሌተናል ጀነራል ሠአረ መኮንን፣ ሌተናል ጀነራል አበባው፣ ሜጀር ጀነራል ዮሀንስ ወልደጊዮርጊስ፣ ሜጀር ጀነራል ገብራት አየለ እና ሌሎችም ይገኙበታል፡፡


ባለፈው አመት እና ዘንድሮ ከ60 በላይ ለሚሆኑ መኮንኖች የጀኔራልነት ሹመትና እድገት መሰጠቱ ይታወሳል፡፡

የሂውማን ራይትስ ዋች የሰሞኑ ዘገባ

ለወያኔ ፋሽስታዊ ግፍና የውገን ሰቆቃ ምላሽ መስጠት ይገባል

በኤፍሬም የማነብርሃን
በዓለም ታዋቂው የሰብዓዊ መብቶች ሟጋች ድርጅት ሂውማን ራይትስ ዋች (Human Rights Watch) ሰሞኑን ባወጣው ዘገባ፡ የአፍሪቃ አንድነት ዋና ከተማ በምትባለው በአዲስ አበባ ከተማ ውስጥ የወያኔ መንግስት በኢትዮጵያውያን ላይ እያካሄደ ያለውን የግፍ ግፍ ለዓለም አጋልጧል፡፡ በዚች ደቂቃ ማዕከላዊ ፖሊስ ጣቢያ እየተባለ በሚጠራው የሰቆቃ ቦታ በንጹሃን ኢትዮጵያውያን ላይ ለኢትዮጵያዊነት ፍቅርና ክብር በሌለው የወያኔ ወንጀለኛ መንግስት ይህ ነው የማይባል ወንጀል እየተፈጸመበት ይገኛል። በ”ሕጋዊ” መንገድ እንዲሰሩ “ተፈቅዶላችው” የሕዝቡን ሰቆቃ በመስማትና የሚፈጸመው ግፍና በደል እንዲቀርና በሰላማዊ መንገድ በውድ አገራችን ላይ ደሞክራሲ እንዲለመልም እየታገሉ በሚገኙ ኢትዮጵያውያን ላይ፤ የወያኔ ፋሽስታዊ መንግስት በአንድ ወገን ዓለምን ለማታለልና ዲሞክራሲ እንዳለ ለማስመሰል ፓርቲ ማቋቋም ይቻላል ብሎ ካስወራ በኋላ፤ ከዓለም እይታ በስተጀርባ ግን ይህ ነው የማይባል ፋሽስታዊ ጭካኔ በንጹኅን ኢትዮጵያውያን ላይ እያካሄደ አንደሚገኝ የመብት ሟጋች ድርጅቱ አጋልጧል። እንዲህ ያለ ወንጀል በውዲቷ ዋና ከተማችንና በታላላቆች የሃይማኖት መጻሕፍት በቅድስናዋ ደጋግማ በምትጠቀሰው አገራችን ሲፈጸም እንዴት ዝም ብለን እናያለን? እያንዳንዱ እትዮጵያዊ ባለው ዐቅሙ ሊያደርግ የሚገባውን ለማድረግ ለምን አይረባረብም?
ይህ ግፍ በወገኖቻችን ላይ ሲፈጸምባቸው የቆየ መሆኑን ከሥርዓቱ ተጠቃሚዎች በስተቀር ሁሉም የሚያውቀው ቢሆንም፡ እንደዚህ በዓለም ደረጃ ታውቆ በግላጭና ቁልጭ ብሎ መነገሩ ወያኔ አትዮጵያውያንን ብቻ ሳይሆን፤ ከአሁን በኋላ የዓለምን ሕዝብ ጭምር አያታለለ ሊቆይ እንደማይችል ያስገነዘብው ዪመስለኛል። ለዚህም የሂውማን ራይትስ ዋችን በሚቻል ሁሉ መርዳትና ምስጋናችንንም ማቅረብ ይገባናል።
በተጨማሪም እያንዳንዱ ሰላም ወዳድ ኢትዮጵያዊ “አሁንስ በቃ በጋራ እንኳን ምንም ማድረግ ቢያቅት በግሌ ማድረግ የሚገባኝን ማድረግ አለብኝ” ብሎ መነሳትና ይህንንም የግል ውሳኔ በስራ ለመተርጎም መወሰን አለበት፡፡ የግፉ አይነት፡ ብዛት፡ እና የጭካኔው መጠን ውስጣችንን የሚረብሽና ሰላምን የሚነሳ እንደመሆኑ መጠን፤ ይህን የውስጥ ንዴታችንን ወደ ወደተጨባጭ ትግል ለመቀየር በኢትዮጵያ ላይ ይግፍ መረቡን ዘርግቶ የተቀመጠውን ይሕን እርኩስ መንግስት ባለን ዐቅም ፊት ለፊት ተጋፍጠን “በዚህማ ልትቀጥል አትችልም ፡ይብቃህ እርኩስ ኃይል ይብቃህ“ ማለት መቻል አለብን።
በአገሪቱ ዋና ከተማ መሃል ላይ እንዲሁም ስላልታወቀ ነው እንጂ በጣም በብዙ የአገሪቱ ከተሞችና መንደሮች ውስጥ ይህን የመሰለ የግፍ ግፍ እየተካሄደ እያለና ሕዝቡ የመከራ ገፈፉን እየቀመሰ ያለ መሆኑን ሁላችንም በልባችን እያወቅነው እንዴት ብለን ቁጭ እንላለን፤ እንዴትስ በልተን ጠጥተን እንውላለን አናመሻለን፤ እንዴትስ ተኝተን እናድራለን፤ እንዴትስ ቤተ ክርስቲያን አስቀድሰን፤ መስጊድ ተሳልመን ቤታችን እንገባለን፤ እንዴትስ አገር አለን ብለን ስለ አገር ዕድገትና ልማት እናወራለን፤ እንዴትስ ስለዚህ ወንጀለኛ መንግስት መልካምነት እንናገራለን።
ከሂውማን ራይትስ ዋች ሪፖርት ትንሽ ቀንጨብ አድርገን እንመልከት፡፡
“ በኢትዮጵያ ከ1997ቱ አወዛጋቢ ምርጫ በኋላ በሰላማዊ ተቃዎሞ ላይ የሚደረገው ጫና ተባብሷል። በማዕከላዊ ተይዘው ምርመራ የሚካሄድባቸው የመንግስት ተቃዋሚ ናቸው ተብለው የሚታሰቡ ሰዎች … በተለይ በምርመራ ጊዜ ታሳሪዎቹ በጥፊ፣ በእርግጫ እንዲሁም በብትር እና በሰደፍ በተደጋጋሚ እንደተመቱ … ሰውነታቸውን ለህመም በሚዳርግ ሁኔታ እንዲሆኑና በተለይም እጆቻቸውን ከግድግዳ ጋር ታስረው እንዲንጠለጠሉ ተደርጎ ለረጅም ሰዓታት ያለማቋረጥ እንደሚደበደቡ ተናግረዋል። ከኦሮሚያ ክልል የመጣ አንድ ተማሪ ብቻውን ተነጥሎና በሰንሰለት ታስሮ ለበርካታ ወራት እንዲቆይ እንደተደረገ ተናግሯል፡፡ ‘ለመቆም ስሞክር እቸገራለሁ፡ ለመቆም ጭንቅላቴን፣ እግሮቼን እና ግድግዳውን መጠቀም ነበረብኝ ፡፡ ምግብ ስመገብ እንኳ በሰንሰለት ታስሬ ነበር። ስመገብ እጆቼ በፊት ለፊት በኩል እንዲታሰሩ ይደረጋል ስጨርስ ደግሞ መልሰው ወደ ኋላ ያስሩኛል።’”
እንግዲህ ይህ መረጃ በአጋጣሚ ሕዝብ ዘንድ ወሬው ሊሰማ የቻለው ከእስር ወጥተው ለወሬ ነጋሪነት የበቁ ሰዎች ስለተገኙ ነው። ክዚህ ጀርባ እንዲህ ያልታወቁ፡ በድብቅ በአገሪቱ ዙርያ በወያኔ ነፍሰ ገዳይ ቡድኖች በወገኖቻችን ላይ የሚፈጸሙ ስፍር ቁጥር የማይገኝላቸው ወንጀሎች እንዳሉ መገመት አያዳግትም። ቤት ይቁጠረው። የወንጀለኞቹ መሪ መለስ ዜናዊ በተገኘበት የፌደራል ፖሊስ ኮሚሽነሩ ወርቅነህ ገበየሁ በደህነነት ምክር ቤት ስብሰባ ላይ የተናገረውን ለመጥቅስ ወያኔ እንደ ልዩ የስራ ችሎታው አድርጎ የሚትቀምበት ዘዴ “በተቀናጀ ኦፐሬሽን ለረጅም ጊዜ ለመንግስት ሥጋት ሆነው የቆዩ ሰዎች እንዲወገዱ” ማድረግ መሆኑን ወርቅነህ በኩራት ሲገልጽ ሁሉም በስብሰባው የነበሩ የምክር ቤቱ አባላት ከመለስ ጭምር የዜናው አስፈሪነትና ከባድነት ለመቅጽበት እንኳን በመንፈሳችው ውል ሳይል ስብሰባውን ሲቀጥሉ ታይተዋል።
በቅንጅት መሪዎች በተልይ ደግሞ በእህት መሪያችን በወይዘሪት ብርቱካን ሚደቅሳ ላይ የተፈጸመውን ግፍና መከራ እንዲሁም በአሁኑ ውቅት በእስክንድር ነጋ፤ በአንዷለም አራጌ፤ ወዘተ በዚች ሰዓት የሚፈጸመውን ግፍና መከራ ሁሉም የሚያውቀው ነው ። በሞቱ የተገላገልነው መለስ ዜናዊና የወያኔ መንግስት በሃሰትና ውሽት ላይ የተመሰረተውን የስልጣን ዘመናቸውን ለማራዘም በማሰብ፤ የቅንጅትን መሪዎችን ለዓመታት በእስር ቤት በማንገላታትና በማሰቃየት፤ በጨለማ ቤት ለወራት በማቆየት፤ ከጉልበትና ከማስፈራራት በተገኘ የሃሰት የእምነትቃል ላይ እንዲፈርሙ በማድረግ በኢትዮጵያ ሕዝብና በደጋፊዎቻቸው ዘንድ እነዲጠሉና የመሪነት ድጋፋቸው እንዲቀንስና እንዲናቁ ያደረጉትን ሙከራ ሁሉም ኢትዮጵያዊ የሚያውቀው ነው።
ይህ የወንጀለኞች መንግስት በኢትዮጵያ ላይ በመሳርያ ኃይል ከተፈናጠጠ በኋላ አገሪቱን በዘር መከፋፈሉ፤ አገሪቱን ያለባሕር በር ማስቅረቱ፤ ለምለም የአገሪቱን መሬቶች ለሱዳን አሳልፎ መስጠቱ፤ የአንድን አናሳ ብሔረሰብ አባላትን የኢኮኖሚው፡ የቢሮክራሲው፡ የሚሊታሪው፡ የፍርድ ቤቶች፡ የቤት ንብረትና መሬት ይዞታዎች የበላይ አስተዳዳሪና ባለቤት ወዘተ ማድረጉ፤ የአገሪቱን ብርቅዬ መምህራን ከዩኒቨርሲቲ ማፈናቀሉ፤ ሕዝብን ለምርጫ ካልወጣህ ካለ በኋላ መሸነፉን ሲያውቅ በዲሞክራሲ የተመረጡትን መሪዎች ማስገደሉ ማሰሩና ንጹሃን ወጣትና ህጻናትን መጨፍጨፉ፤ ሰሞኑን ደግሞ የወንጀለኛ ድርጅት አባል ካልሆናችሁ ስራ፡ እድገት አታገኙም ማለቱ ወዘተ አልበቃው ብሎ አስከፊ በሆኑት አሥር ቤቶቹ ውስጥ መሪዎችንና አዛውንቱን ለዚሕ ለሚዘገንን መከራና ሰቆቃ መዳረጉ ምን ያሕል ሕዝቡን የናቀ መሆኑን ያሳያል።
እንዲያውም ከሁሉም በላይ ደግሞ የሚያበሳጨው መንግስቱ ኃይለማርያምን በኢትዮጵያውያን ላይ ትልቅ በደል ሰርቷል እያለ የሚያብጠለጥለው የወያኔ መንግስት፡ ከመንግስቱ ኃይለማርያም በማያንስ ጭካኔ ከፖለቲካ ልዩነት በቀር ምንም ያልሰሩ ንጹሃንን ይህን ለመሰለ ስቃይና መከራ የዳረጋቸው መሆኑ ነው። በተጨማሪም በመንግስቱ ኃይለማርያም የተጀመረው የዚህ ለመከራ የተዳረገ ሕዝብ ፍዳ በዚህ ዘረኝነት ባሰከረው የወንጀለኞች መንግስት በጣም በተራቀቀ ድርጊት መቀጠሉ “ያገር ያለህ” ወደሚያስብል ነጥብ ላይ አድርሶናል።
በተለይ ደግሞ በዚህ ኢንተርኔት፡ ተዟዟሪ ስልክ፡ ሳተላይት ሬዲዮና ቴሌቪዥን እና በአጠቃላይ የሚዲያ ቴክኖሎጂ በዓለም በተንሰራፋበት ዘመን የወያኔ መንግስት ኢትዮጵያውያን የዚህ ዕድገት ሙሉ ተካፋይና ተሳታፊ እንዳይሆኑ አፍኖ፡ የዓለምን ሕዝብ ይሉኝታ ሳይፈራ የጭካኔና የግፍ መረቡን በአገሪቱ ላይ ዘርግቶ በማናለብኝነት አስከፊ ሴራውን ሲያከናውን ለብዙ ኢትዮጵያውያን “አሁንስ አልሞትኩም ብዬ አልዋሽም” የማያስብል ደረጃ የደረስን ይመስላል ። እስከመቼ ችለን ልናየውና የወያኔን የግፍ ቀንበር ተሸክመን ኑሮን መቀጠል እንደምንችል ማሰብና አስቸኳይ ውጤት ለማግኘት መረባረብ ይገባናል።
ይህን የሂዩማን ራይትስ ዋች ዘገባ ያነበብነውንና እንዲሁ እንደማንኛውም ዜና የምናልፈው መሆን የለበትም። ተጨባጭ የሆኑና የወንጀለኛው መንግስት እንዲሰማው የሚያስችሉ፤ ከባድ ያልሆኑ ነገርግን ተፈጻሚነት ሊያገኙ የሚችሉ፤ ሰላማዊ ዘዴና እርምጃዎች ላይ ተወያይተን በዝርዝር በማስቀመጥ በውጭ አገር ተቀማጭ የሆንነው ኢትዮጵያዊ ያን በስራ ልንተረጉማቸው ይገባናል። ለመነሻ፤ መወያያና መንደርደሪያ ያህል የሚከተሉት እነሆ።
1. ቢያንስ ለሶስት አለያም ለስድስት ወራትም ሆነ ለአንድ ዓመት የኢትዮጵያ ኤምባሲና ቆንስላዎች ከኢትዮጵያውያን የሚያገኙትን ገቢ ለመቀነስ፤ እነደ ፓስፖርት የማሳደስ ቪዛ የማስመታት፤ የውክልና ሰነዶችን የማጻፍ፤ ቤትና መሬት ለማሰራትና ለመግዛት የሚከፈሉ ክፍያዎችን ወዘተ የሚጠይቁ ሥራዎችን ወደነዚህ የመንግስት አውታሮች ዘንድ ሄዶ ወይም በፖስት ቤት አማካኝነት ልኮ አለማሰራት።
2. ቢያንስ ለሶስት አለያም ለስድስት ወራትም ሆነ ለአንድ ዓመት በውጭ አገር በሚገኙ በግልጽ በወያኔ ካድሬዎች በሚንቀሳቀሱ ወይም የወያኔን ካፒታልና ቢዝነስ በሚያንቀሳቅሱ ግለሰቦችና ድርጅቶች ላይ የኢኮኖሚ ማዕቀብ በማድረግ ምንም ዓይነት የዕቃ ግዢ ወይንም የገንዘብ ልውውጥ እንዲህ ካሉ ሰዎች ጋር ከማድረግ መቆጠብ። ይህንን ዐቀብ በምናካሂድበት ወቅት እንቅስቃሴው በዘር ላይ ያልተመሰረተና ያለበቂ ማስረጃ በአንድ ብሔር ተወላጆች ላይ ያላነጣጠረ እንዲሆን አስፈላጊውን ጥንቃቄ ማድረግ ይገባል። ወደዚያ ዓይነት የትግል አቅጣጫ ሊመሩ የሚፈልጉትን ግለሰቦች በሙሉ መምከርና ካልሆነም መገሰጽ ይገባል።
3. ቢያንስ ለሶስት አለያም ለስድስት ወራትም ሆነ ለአንድ ዓመት የመንግስት አውታር ለሆነው የኢትዮጵያ ንግድ ባንክም ሆነ ሌሎች ባንኮች ገንዘብ ለሚያደርሱ እንደ ዌስተርን ዩኒየን የመሳሰሉ ወደ ወያኔ ካዝና የውጭ ምንዛሪ (ፎርን ኤክስቼንጅ) በሚያስገቡ ድርጅቶች ወደ ኢትዮጵያ የሚላክ ገንዘብ አለመላክና የሚኖሩበትን አገር ሕግ ሳይጥሱ በሌላ ዘዴ አገር ቤት ለሚገኝ ወዳጅ ዘመድ ብር መላክ።
4. ቢያንስ ለሶስት አለያም ለስድስት ወራትም ሆነ ለአንድ ዓመት የወያኔን ዓላማ በግላጭ ከሚያስፈጽሙ የወያኔ ካድሬዎች ጋር በማንኛውም አጋጣሚ ድጋፋቸውን የሚሰጡት መንግስት በደምና ግፍ የተጨማለቀ መንግስት መሆኑን ባላሰልሰ በማስረዳት ላጭር ጊዜም ቢሆን ከጋራ ተሳትፎ ማግለል። ይህንን ዐቀብ በምናካሂድበት ወቅት እንቅስቃሴው በዘር ላይ ያልተመሰረተና ያለበቂ ማስረጃ በአንድ ብሔር ተወላጆች ላይ ያላነጣጠረ እንዲሆን አስፈላጊውን ጥንቃቄ ማድረግ ይገባል። ወደዚያ ዓይነት የትግል አቅጣጫ ሊመሩ የሚፈልጉትን በሙሉ መምከርና ካልሆነም መገሰጽ ይገባል።
5. ቢያንስ ለሶስት አለያም ለስድስት ወራትም ሆነ ለአንድ ዓመት በኢትዮጵያ አየር መንገድ አለመጠቀም። ወያኔ በአሁኑ ጊዜ የጭካኔና የግፍ ሥራውን ለማካሄድ ብዙ የገንዘብ ዐቅም ስለሚያስፈልገው ይህንን የገቢ ምንጩን መቀነስ ለትግላችን መፋጠን ይጠቅማል።
6. ወያኔ በኢትዮጵያ ውስጥ መልካም ሥራ እያካሄደ እንዳለ ሊናገሩ የሚፈልጉ ሞኝና ተላላዎች አገሪቱ በደም የተነከረችና የንጹሃን ሰቆቃ የሚጮህባት አገር እንደሆነች ባላሰለሰ በመንገር በእጅ አዙር የወያኔ ቱልቱላ ቃል አቀባዮች እንዳይሆኑ መምከርና የኢኮኖሚ ዕድገትም እውነትነቱም ሆነ ተፈጻሚነቱ ሊረጋገጥ የሚችለው የሰው ልጅ በሰውነቱ ሲከበርና ያች ሃገር የጥቂቶችና የዘረኞች ሳትሆን የሁሉ ኢትዮጵያዊያን በመሆኗ ጥቂቶች ዘረኞች የብዙዎችን መብት ረግጠው ላንተ እኛ ብቻ ነን የምናውቅልህ እያሉ የሚያናፍሱት ወሬ በሰለጠነው ዘመን ሊሰራና ሊቀጥል የማይችል ተራ ቱልቱላ መሆኑን እንዲገነዘቡ ማድረግ።
7. ወያኔ ሰሞኑን በዳያስፖራ የሚገኙትን የዋህ ኢትዮጵያውያን ገንዘባችውን ለመቀማት የያዘው ዘዴ “ኢትዮጵያ ውስጥ መሬትና ኮንዶ ለመሥራት ኢንዲያስችላችሁ 60/40 የሚባል ፕሮግራም ተዘጋጅቶላችኋል፤ 60 በመቶ (60%) በውጭ ምንዛሪ ካስቀመጣችሁ ቀሪዊን አርባ በመቶ (40%) በአነስተኛ ወለድ የሚከፈል ብድር አዘጋጅቼላችኋለሁ፤ ነገር ግን የውጭ ምንዛሪውን በቀጥታ ለኢትዮጵያ ንግድ ባንክ ብቻ ገቢ ማድረግ ይጠበቅባችኋል” በማለት ኢትዮጵያውያንን በግፍ ቀንበሩ ለረጅም ጊዜ ሊይዝ የሚያስችለውን ሃብት ለመሰብሰብ ጥረት ኢያደረገ ስለሆነ ቢያንስ ለሶስት አለያም ለስድስት ወራትም ሆነ ለአንድ ዓመት ይህን ከመሰለ ለወያኔ የውጭ ምንዛሪ መሰብሰቢያ ማታለያ ዘዴ ውስጥ ከመውደቅ መቆጠብ።
እነኝህ ከላይ የተዘረዘሩት ምን መደረግ አለበት ለሚለው ጥያቄ መልስ ባጭሩ ለመስጠት የታቀዱ ናቸው እንጂ ሁሉንም ዘዴ አያካትቱም። የተለያዩ ኢትዮጵያውያን በዝርዝሮቹ ላይ ተጨማሪም ሆነ ማሻሻያ ወይም አዳዲስ ገንቢ ሃሳቦች ቢያቀርቡ ጥረታችን ውጤታማ ይሆናል የሚል ግምት አለኝ፡
የወያኔ የክፋት የጭካኔና የበደል ቀንበር አንድ ቀን ከኢትዮጵያውያን ጫንቃ ላይ ወድቆ ይፈጠፈጣል!!
የኢትዮጵያውያን ሰቆቃ የማለቂያው ቀን ሩቅ አይደለም!!
ውድ አገራችን ኢትዮጵያ ለዘለዓለም ትኑር!!

Friday, October 25, 2013

ስብሃት ህወሃት ጠቦ ታሪኩን እንደሚቋጭ አረጋገጡ

ህወሃትን ገልብጦ “ከየትኛው ክልል ድጋፍ ሊገኝ?”

sebhat nega


ስብሃት ነጋ የኢህአዴግ አባትና ፈጣሪ የሆነው ህወሃት የመጨረሻው ታሪኩ ጠቦ እንደሚቋጭ ይፋ አደረጉ። ችግር የህወሃት ልዩ በረከትና ስጦታ እንደሆነ በማመልከት ህወሃት ውስጥ ልዩነትና መፈርከስ አደጋ ተከስቶ እንደማያውቅ ሸመጠጡ።
አቶ ስብሃት ጠቦ የሚጠናቀቀውን የህወሃት ስውር አጀንዳ የገለጹት ከጋዜጠኛ ደረጃ ደስታ ለቀረበላቸው ጥያቄ መልስ በሰጡበት ወቅት ነበር። በኢህአዴግ የመከላከያ መዋቅር ውስጥ ከፍተኛ መከፋፈልና የኩዴታ አደጋ ሊያስከትል የሚችል አደጋ እንደተረጋገጠ ተጠቅሶ ለቀረበላቸው ጥያቄ አቶ ስብሃት “አዲስ አበባ መንግስት ገልብጠው የክልሎችን ድጋፍ ቢጠይቁ ማን እሺ ይላል” በማለት ነበር የመለሱት። አንዴ በመከላከያ ውስጥ የመከፋፈልና የመበታተን አደጋ ሊያጋጥም የሚችልበት አግባብ እንደሌለ፣ ጠያቂው እንዳለው የመፈንቅለ መንግስት አደጋ ቢያጋጥም እንኳ የህወሃት ስጋት እንዳልሆነ አስመስለው አቶ ስብሃት የመለሱት የክልሎችን ስም በመጥራት ተቀባይት እንደማይኖረው ነው። ይህም አባባላቸው እኛን ገልብጦ አገር አንድ አድርጎ መምራት አይቻልም የሚል እንደምታ ያለው ቢመስልም፤ “ሪፑብሊክ” ለመመሥረት የተነሳውና እስካሁን በነጻአውጪ ስም አገር እየገዛ ያለውን ህወሃት የመጨረሻ የመጥበብ ዓላማ በማስረጃ የገለጹበት ነው፡፡
ህወሃት “ኢህአዴግ” የሚባለውን ድርጅት ሲያበጀው የአገልግሎት ዘመን መድቦለት እንደሆነ ስለ ድርጅቱ የወደፊት መድረሻ ድንበሩ ከሚያወሱ የድርጅቱ የተለያዩ መረጃዎችና ነባር አባሎቹ መጠቆሙ ይታወሳል። ህወሃት 40ና 50 ዓመት ኢትዮጵያን በብሔር ፖለቲካና በዘር እያጋጨ ለመግዛት የሳለው ስዕል እንዳሰበው ካላዘለቀው እንዴት ጠቦ እንደሚጠናቀቅ የጠቆሙት ስብሃት፣ አስተያየታቸው አካሄዱ የገባቸውን በሙሉ አበሳጭቷል።
በ1997 የምርጫ ወቅት ተፈጥሮ በነበረውና በራሱ በቅንጅት ሰዎች ሽኩቻ በተኮላሸው ህዝባዊ ድል ግለት ወቅት ኢንዲያን ኦሽን የተሰኘው ጋዜጣ “ህወሃት ወደ ትግራይ የማፈግፈግ እቅድ ይዟል” በማለት የዘገበውን ዘገባ በማስታወስ በአቶ ስብሃት መልስ ላይ አስተያየት የሰጡ፤ በቅድሚያ አቶ ስብሃትን “አቦይ ብላችሁ አትጥሩት። አባታዊ አንደበትና ምግባር የለውም” በሚል ማሳሰቢያ ከሰጡ በኋላ “የስብሃት ንግግር ህወሃት ታሪኩ ሲጠናቀቅ ጠቦ እንደሚቋጭ ነው። ለዚህ ሲል ነው ህዋሃት ከአንቀጽ 39 ጋር ቅበሩኝ የሚለውና የአማራ ክልል መሬትን እየዘረፈ የመውጫ ቀዳዳ ፍለጋ ሌት ከቀን መሬት እየቆረሰ አዲስ ካርታ የሚያመርተው፤ ዓለምአቀፋዊ ድንበርም ለትግራይ እንዲኖራት ያደረገው” ብለዋል።
“ህወሃት ካለውና ከተፈጠረበት  ክፉ ዓላማ አንጻር በቀጣይዋ ኢትዮጵያ ‘ቦታ አይኖረኝም’ የሚል ድምዳሜ ላይ ስለደረሰ ሁልጊዜ ሲጨንቀው ኢትዮጵያን የማፈራረስ ስዕል ያሳያል። የስብሃትም ንግግር ይህንኑ የሚያረጋግጥ ነው” በማለት ምልከታቸውን የተናገሩት የጎልጉል የዘወትር አስተያየት ሰጪ “ውሳኔውና ህልሙ ስኬት የናፈቀው የቅጥረኞቹ የህወሃት ሰዎች ጭንግፍ ምኞት ቢሆንም መላው የትግራይ ህዝብ በዚህ ጉዳይ ላይ ጥርት ያለ አቋም በመያዝ ከኢትዮጵያ ሕዝብ ጋር የሚቆም መሆኑን ማሳየት እንደሚገባው” አመልክተዋል።azeb 3
ከህወሃት ሊቀመንበርነታቸውና ከስራ አስፈጻሚነታቸው አራት ጊዜ ማመልከቻ በመጻፍ በፈቃዳቸው እንደለቀቁ ያመለከቱት ስብሃት ነጋ በኤፈርት ጉዳይ ከወ/ሮ አዜብ ጋር ስምምነት እንዳልነበረቸው ፍንጭ ሰጥተዋል። አያይዘውም ህወሃት የመከፋፈል አደጋ አጋጥሞት እንደማያወቅ፣ እንዲያውም በየጊዜው የሚነሱ የሃሳብ ልዩነቶች የድርጅቱ ልዩ ስጦታውና በረከቱ አንደሆነ ተናግረዋል። ልዩነትና በልዩነት ጥግ ድረስ ደርሶ መፋጨት የህወሃት የጥንካሬው መሰረት እንደሆነ ያመለከቱት አቶ ስብሃት በድህረ ኢትዮ-ኤርትራ ጦርነት ወቅት ህወሃት ለሁለት ተከፍሎ አደጋ ላይ የወደቀበትን ጊዜ አስተባብለዋል። እነ አቶ ስዬንም “የተባረሩ” ሲሉ አቅመ ቢስ አድርገው ስለዋቸዋል።
ኤርትራ ራሷን በወጉ መከላከል እንኳ የማትችል አገር እንደሆነች የጠቆሙት ስብሃት ኤርትራን ተማምኖ የሚከናወን የተቃውሞ ትግል የጤና ነው ብለው እንደማያምኑ “እብደት ነው” በማለት ኢህአዴግም ሆነ እሳቸው በእንቅስቃሴው ላይ ስጋት እንደሌለባቸው ለመግለጽ ሞክረዋል። ስብሃት በአሜሪካ ከተለያዩ ወዳጅ ሚዲያዎች ጋር እየተወደሱ ጥያቄና መልስ ያካሄዱ ሲሆን በተለይም ስለ መለስ ቅንድብ ከዘፈነው ሰለሞን ተካልኝ ሲቀርቡላቸው የነበሩት ጥያቄዎች የሚያዝናኑ ነበሩ። ጥያቄና መልሱን የተከታተሉ “ጠያቂው መልሱን አስቀድሞ ጥያቄ ማስከተሉ ጥሩ ተማሪ መሆኑንን በማረጋገጥ የምስክር ወረቀት የፈለገ አስመስሎታል” ሲሉ የለበጣ አስተያየት በማህበራዊ ገጾች ላይ አስፍረውበታል። አቶ ስብሃት በአሜሪካ ከጠባቂዎቻቸው ጋር በመሆን መደባደባቸውና በፖሊስ ይፈለጉ እንደነበርም መዘገቡ ይታወሳል። አቶ ስብሃት ከፖለቲካው ፈላጭ ቆራጭነት ወጥቻለሁ ቢሉም የሚሰጡዋቸው አስተያየቶችና ትንቢቶች አሁንም “የህወሃት የኋላ ዘዋሪ” እንደሆኑ አመላከች እንደሆነ ተጠቁሟል።

ጫልቱ እንደ ሄለን ከቡርቃ ዝምታ የቀጠለው መርዛማ ብዕር

ዳኛቸው ቢያድግልኝ

ተራሮች አንቀጠቀጥኩ ያለው ትውልድ አካል ነኝ ባዩ ወንድማችን በቡርቃ ዝምታው በማር የተለወሰ መርዝ አሰናድቶ አማራና ኦሮሞ ሲተራረድ ዙርያ ከበው በለው! አትማረው! የሚሉትን የአባቱን ሀገር ፖለቲከኞች አስቦ የጻፈው ክታብ መሆኑ ተነግሮ አብቅቶለታል። ተስፋዬ የጦር ሜዳ ዘጋቢነቱን በኢትዮጵያውያን ተምሮ ኢትዮጵያዊ አይደለንም ብለው ለሚወጉን ማገልገሉና በደል መፈጸሙ እውነት ነው። ለዚህ ውለታውም የዘመናት ታሪክ ያለውን ድርጅት ያለምንም ክህሎት በአዛዥነት ይዞ እንዳሻው እንዲፈነጭበት ተሰጥቶት ነበር። ቁንጮ ሆኖም የሚበቃውን መረጃ ከክምችቱ እንዲያገኝ ሆኖ መሰየሙንና ክምችቱንም ለፕሮፓጋንዳ መሳርያነት እንዲጠቀምበት ሙሉ መብት ተሰጥቶት እንደነበረም እናውቃለን። ተስፋዬ አገር የለቀቀበትን ጊዜ መለስ ብለን ብንመለከት ለሻዕብያ ያለው ቅርበት ከወያኔ ጋር ለመቀያየም ምክንያቱ መሆኑን መገመት ይቻላል። በተስፋዬ ስራዎች ውስጥ የኤርትራ ጉዳይ ልዩ ቦታ እንዳለውና ከጻፈም ጀግና ብልህና አስተዋይ እንደሚያደርጋቸው የታወቀ ነው።Tesfaye Gebreab's New Book: “Yesidetegnaw Mastawesha
ስለዚህ ኤርትራዊነት አያደላበትም ወይም ለኤርትራ መረጃ አያቀብልም ብሎ ያለመገመት ከመነሻው የሚገርም ጉዳይ ነው። በቅርብ ድርሰቶቹ ወያኔዎቹን በተመለከተ የአሉባልታ ዶፍ ማውረዱና ይልቁንም ዱላው የጠነከረው ለሻዕብያ ወገንተኛ አይደሉም ባላቸው ላይ መሆኑም የሚያመለክተው ይህንኑ ነው። በማሩ ቃላት አሉባልታዎች ከመገለጻቸው በቀር የፖለቲካ ፋይዳ ያላቸው የማይታወቁ ድብቅ ምስጢሮች የሚባሉ ነገሮችም የሉበትም። ስለዚህ ተሥፋዬ የት እንደሰፈረ የሚሸሽግ አንዳች ነገር ከሌለ ፈቅደን የታለልንለት ድንገት መባነናችንና ምስጢሩ እንደተገኘ ያለማሳወቃችን ለምን በዚህ ጊዜ ሆነ ብለው ለሚጠይቁ ጠርጣሪዎችም የውይይት ማንደርደርያ ቢሆን አይገርምም። የአብርሃ ደስታን ምልከታ እጋራዋለሁ። የተሰጡ አስተያየቶችን አንብቤያለሁ። ጥሩ የሚባል ነገር ሲጻፍ ማመስገን ስህተት ሲኖርም ስህተት እንደመጠቆም የዘር ሀረግ ላይ ተንጠልጥሎ መራገም ውይይታችንን ጤናማ ያደርገዋል የሚል እምነት የለኝም። የቀረበበት ማስረጃ ግን አንዳንድ የዋሆች ለኦሮሞ ካለው ፍቅርና አክብሮት አንጻር የተንገበገበ ሳይሆን የእልቂት ድግሳችንን እያጧጧፈ እንደሆነ እንዲገነዘቡ ያደርጋል ብዬ አምናለሁ።
ተስፋዬ የቢሾፍቱ ልጅ ነው ሥጋና ደሙን የቢሾፍቱ አፈርና ወሀ ገንብተውለታል፣ አንደበቱን የገራለት ሀሳቡን በዚህ መልክ ይገልጥበት ዘንድም የቋንቋ ቁልፉን ያስጨበጠው የኢትዮጵያ ሕዝብ ነው። ይሁን እንጂ ወንድማችን ተሥፋዬም የማንነት መምታታት የማያውቀውን አገር የመናፈቅ ግራ መጋባት ውስጥ አይደለም ብዬ አልገምትም። ከጠባው ጡት ጋር ሲነገረው የኖረ የጥላቻ መርዝ መኖሩንም በጻፈው ማስታወሻ ላይ  ግልጽ ብሎ ተቀምጧል። አብሮ አደጎቹን ወይም በስደት ዘመን ያገኛቸውን ሁሉ ለዚህ የፖለቲካ ጥቅም በቢሾፍቱ አድባር ስም እየማለ ሊጠቀምባቸው ቢሞክር አይደንቅም። እንዲያውም ለአባት አገሬ አደረኩ የሚለውን እያሰበ በበግነታቸው ድዳቸውን ማስገልፈጡንና የበግ ነጋዴነቱ ውስጡን ያስቁት ያኩራሩትም ይሆናል። “በግ እሰራ” ነበር ማለቱ ድንገት የተጻፈች አረፍተ ነገር ናት ብሎ ማሰብ እንዲከብደን ሆኗልና። እንዲያም ሆኖ ወንድማችን ያለኢትዮጵያዊነት ነብሱ ባዶ መሆንዋን አልጠራጠርም። ከኢትዮጵያ ሌላ ባማረ አማርኛ ለማንስ ሊጽፍ ይቻለዋል?  በሁለት ባላ ላይ ለተንጠለጠለቺው ነብሱ በጣም አዝናለሁ። የአባቱን ሀገር ለማገልገል ቆርጦ የተነሳ ቢሆንም እንደ ተበላ ሰላይ ሜዳ መውደቂያውን ማፍጠኑ ግን ብልህነት እንደሚያንሰው ያሳያል።
ለዚህም ይሆናል የስደተኛው ማስታወሻ በወቅቱ ከሕዝቡ ጆሮ ካልገባ የሚያመጣው የፖለቲካ ትርፍ ስለሚቀንስ በነጻ እንድናነበው የሆነው። እኔም ገረፍ ገረፍ አደረኩት ማለትም ለመተቸት በሚያስችል መጠን አልተመለከትኩትም። ብቻ ዘመን አቆጣጠሩን ‘በግዕዝ’ የሚል ሲቀጥልበት እንደ ኢትዮጵያ ማለት ከብዶት ይሆን? ብዬ ማሰቤ አልቀረም። በጠቅላላው ዘረፍ ዘረፍ የሚያደርጋቸው ቃላትና ጠቅለል አድርጎ የሚገልጽባቸው አረፍተ ነገሮች በውል ሊታዩ የሚገባ ነው። ሳይንሱን ባለመረዳቱ ስለፍጥረት የሚሰጠው ምሳሌም የሚተች ነው። ጦስኝ ሳር አይደለም የበግ ሽንትም ሳር ማስተኛቱን እጠራጠራለሁ። ምናልባት የቢሾፍቱ በጎች ከሆራው እየጠጡ እንደ እሳት አደጋ ጎርፍ ይሸኑ አንደሆን አላውቅም።
ሌላው ምሳሌ አንበጣ ብሎ የጻፈው ስለ ምስጥ ነው። አንበጣማ ከፊቱ ያለውን እየጠረገ ጥቁር ደመና መስሎ  ብዙ ኪሎሜትሮችን ያካልላል። ምስጥ ክንፍ የሚያወጣው ሩቅ ለመብረር አቅዶ አይደለም እንደ ተስፋዬ ግምትም ክንፋቸው ሲረግፍ ባጭር መቅረታቸው አይደለም። የምስጥ ንግስትና ንጉስን ለመፍጠር ከተለያየ መኖርያ ቤታቸው (ኔስት) በተመሳሳይ ጊዜ ወጥተው ወንድና ሴት የሚፈላለጉበት ተፈጥሮ የምትደግሰው ድንቅ ሰርግ ነው። ጋብቻ ካንድ ቤተሰብ እንዳይሆን የዚህኛው ቤት ልጃገረድ ምስጥ ከዚያኛው ቤት ኮበሌ ጋር ዝናብ ሲያባራና አመሻሹ ላይ እየበረሩ ትንሽ ይዳራሉ። ወንድየው ሴቲቱን ተጠግቶ “ሁኚኝ” ይላታል ከፈቀደች ትሆነዋለች። ያኔ ፍቅር መስራት ይጀምራሉ፣ ክንፋቸውን አራግፈውም ጎጆ ለመቀለስ የክረምቱ ዝናብ ያለሰለሰውን አፈር ማስ ማስ አድርገው ሃኒሙን ይጀምራሉ። የነርሱን ጋብቻ ደግሞ የእረኞች የቡሄ ጅራፍ ያደምቀዋል። ተስፋዬ ይህን አውቆ ቢሆን ባማሩ ቃላት ወሲብ ወሲብ እያሰሸተተው ይህንን ጋብቻ ለመፈጸም ከየጉድጓዱ እየወጡ ከወፎች አደን ተርፈው አዲስ ጎጆ የሚቀልሱትን የህይወት ታሪክ በጻፈው ነበር። ንግስቲቱ በቀን ከሺህ በላይ እንቁላል እየጣለች በሰራተኛና በወታደር የታጀበ መንግስት እንደምታቋቁምና ኩይሳ የምንለውን ከኢንጅነሮች ሙያ የላቀውን ቤተመንግስትም እንደምታስገነባና ሌላም ሌላም በነገረን ነበር። ያወቅን የሚመስለን ብዙ የማናውቀው የተፈጥሮ ምስጢር ቢገለጽልን ኖሮ እርስበርስ ለመጠፋፋት ጦር ባላመዘዝን ነበር። ሆኖ ያለፈን ነገር ወይም እየሆነ ያለን ስህተት በቅንነት ተነጋግረን አብሮነታችንን ማስዋብ የሚቸግረን አይደለንምና ወዳጅ መስለው መርዝ የሚረጩትን ማጋለጥ ተገቢ ነው።
ስለ አንድ የሶማሌ ህጻን እሱን አይቶ ማልቀስ ሲጽፍ ይህ የሶማልያ ህፃን እኔን ሲመለከት ለምን እንዳለቀሰ ማሰላሰል ያዝኩ… “አበሻ እባብ” እንደሚለው ነባር የሶማሌ ብሂል እባብ መስዬ ታይቻቸው ይሆን…. የሚል መንደርደርያ ከጻፈ በሁዋላ ወረድ ብሎ ደግሞ በብዙ አለም አቀፍ ሚዲያዎች ኢትዮጵያ የኤርትራና የሶማሌ ጠላት እንደሆኑ ይነገራል ይለናል ይህንን ቅጥፈት ካስነበበ በሁዋላ ደግሞ እባብ ስለመግደሉ ሲነግረን እግዚአብሄር.. የእባብን አናት ቀጥቅጠህ ትገድለዋለህ ሲል ያዘዘውን እኔ በተደጋጋሚ ፈጽሜዋለሁ የፈጣሪን ቃል በማክበር ረገድ በተሟሉ ሁኔታዎች ተሳኩልኝ ብዬ ከምኮራባቸው ትዕዛዛት ዋናው “የእባብን ጭንቅላት ቀጥቅጡ” የተባለው ሳይሆን አይቀርም በሚል ይደመድመዋል። እነዚህ በተን ተደርገው የተረጩት በመጀመርያ አበሻና እባብ ከዚያ አበሻ የሶማሌና የ ኤርትራ ጠላት በመጨረሻም አግዜር እባብን ቀጥቅጡ ባለው መሰረት እባብ መቀጥቀጥ ተሳክቶልኛል የሚሉ እንደ እባብ ቃላት ውስጥ እየተሹለከለኩ የሚሄዱ መርዘኛ መልዕክቶቹን አስፍሮበታል። መጽሃፉን ለመተቸት ሳይሆን አንዲት በየምዕራፎች ተብትና የተቀመጠችውን ስራውን በተመለከተ ብቻ ጥቂት ለማለት ነው። ሌሎቹ ዋናው ተልዕኮአቸው ማዳመቅ ይመስለኛል።
ዛሬ ሰለ ጫልቱ ሄለን መሆን በተጻፈው ላይ ትንሽ እላለሁ። ጫልቱ በለጠች ማለት ነው ጫላም በለጠ። ለኢትዮጵያዊ ጫልቱ ወይም በለጠች ከሄለን የበለጠ ትርጉምና ቅርበት ያለው ስም ነው። በጣም ደስ ያለኝ አቤ ቶኪቻው ተመሳሳይ ነገር ማንሳቱና የአዱገነት ልጆች ይህንን ጉዳይ የሚመለከቱት ለየት ባለ መነጽር መሆኑን ማሳየት መቻሉ ነው።
የቢሾፍቱው ልጅ ተስፋዬ በልጅነቱ አዲስአበባን ሁለቴ ብቻ ስላያት ያልተረዳው ነገር መኖሩን መግለጽና እግረመንገዱንም ያዘኑብን ይቅር እንዲሉን በሸገር ልጆች ስም ያለውክልና ለመጻፍ በመሻቴ ነው።  አዲስ አበባ ውስጥ የትኛውም አካባቢ የኖረ ሰው ሶስት አመት ሙሉ ኦሮምኛ ሲነገር አልሰማሁም ቢል በጣም ያስቃል። አዲስ አበባንም ያለማወቅ ይመስላል። እንኳን ኦሮምኛ ችሎ ለመጣ አዲስ አበባም ኖሮ ኦሮምኛ ማቀላጠፍ ይቻላል። ብዙዎቻችን ለዚህ ምሳሌ ልንሆን እንችላለን የኦሮሞ ልጆች መሆናችን አስፈርቶንም አሳፍሮንም አያውቅም። ተረብና ቀልድ ደግሞ ለሁሉም ዘር የሚሰጥ በመሆኑ በተለየ መልኩ ኦሮሞን ብቻ አንገት የሚያስደፋ አይደለም። ስለ ሌላ አገር የተጻፈ እስኪመስለን ድረስ የተቀባባ ነገር ነው። እንኳን ሀዘን ኖሮ በኦሮምኛ ማልቀስ ይቅርና የመስቀልን በዐል ውብ የሚያደርገውስ የማን ዘፈን ነበርና? ኦሮምኛ ሳይሞከርስ ከገጠር የመጣ ሸቀጥ እንዴት ይገዛ ነበር? በራሱ ዝቅተኛ ስሜት ውስጥ የገባና ራሱን መደበቅ የሚፈልግ ካልሆነ በቀር ኦሮምኛ መናገር የተከለከለባት ከተማ እስክትመስል ድረስ አዲስ አበባን ማጠልሸት በጣም አሳዛኝ ነገር ነው ውሸትም ነው። አማርኛ የስራ ቋንቋ በመሆኑ ብዙዎች ቋንቋውን እስኪማሩ ይቸገራሉ ይህ እውነት ነው። ሁዋላ ቀርነት በመኖሩ ቋንቋ ያለመቻልን መቀለጃ የሚያደርጉ ነበሩ ይህ ደግሞ ሁሉንም ይመለከታል። ኦሮምኛውን ስናወላግደው ዘመዶቻችን ይስቁብን ነበር። አንዳንዴም የአማርኛውን ቃል እንደ ኦሮምኛ ስናደርገው “ይሄ ደግሞ የሚበላ ነው የሚጠጣ” እያሉ የሚስቁብንን ጭምር አስታውሳለሁ።
አቴቴ የተከለከለ ነገር ሆኖ ሳይሆን ክርስትናን ከመቀበል ጋር የቀረ ነገር ነው። የግንቦት ልደታ አድባርም እንደዚሁ። ይህ ‘ዘመናዊነት’ በሚል ፈሊጥ የራስን የማጣጣል አባዜ እንጂ ሲስተሚክ ቫዮለንስም አይደለም። የተደራጁ ሃይማኖቶች የብዙዎችን አምልኮ አረመኔ የሚል ቅጥል እየለጠፉለት መስፋፋትን አድርገዋል። ይህ በመላው ዐለም የሆነ ነው። ይህ ማለት ምንም ጎጂ ነገር ማለትም ማንጓጠጥና መተረብ አልነበረም ለማለት አይደለም። የነበረ ነገር ነው በጣምም ስህተት ነው። ቋንቋችን ሀብታችን ነው ታሪካችን ነው ልንጠቀምበት ይገባል። አንድ ሁላችንንም ሊያገናኘን የሚችል ቋንቋ መኖሩ ደግሞ እንደ ሀገር አብረን እንድንኖርበት ያመቻቻል። አንዱ አንደኛው ላይ ሲሰለጥንበትና ሲጎዳው ይሁን ማለት ተገቢ አይደለም።
በጫልቱ ላይ የደረሰው ነገር ከልብ የሚያሳዝን ነው የዚህ አይነት ስነልቦና እንዲኖራቸው ለተገደዱት ሁሉ ልናዝን ተገቢ ነው። ሆኖ ያለፈን ነገር ፈጽሞ እንዳልነበር መካድም አይቻልም። ቢሆንም ይህ ድርጊት አንድን ዘር ለማዋረድ ሆን ብሎ የተነጣጠረ ክፋት እንዳልሆነ መረዳት ተገቢ ነው። አንዳንድ ጊዜም ለመብት መቆም ያለመቻልና ካለው ሁኔታ ጋር ተስማምቶ ለመኖር የሚደረግ ስህተትም ነው። ልክ እንደ ጫልቱ  ማንጠግቦሽ፣ ኩሪባቸውና አቻምየለሽ ከስማቸው ጋር በተያያዘ ብዙ ይተረቡ ነበር። አዝብጤና እርገጤን ሙደስርና ሙሽሪንም የማራቸው አልነበረም ከተሜ ያልሆነው ሁሉ ቅጽል ስም አያጣም ነበር። ከሸገር ልጆች ተረብ ያመለጡ ነብሶች ካሉ የታደሉ ናቸው። ከጎጃምም ይምጣ ከደሴ አዲስ ላይ ቅጽል ስም አይታጣለትም። ትክክል ነው ማለት አይደለም ግን ፈጽሞ በአንድ ዘር ላይ የተነጣጠረ ልዩ ጥቃት አይደለም። የሰውን ስሜት በዚህ ደረጃ ሊጎዳ የሚችል ቅጽል ስምም ሆነ ተረብ ጎጂ ከሆነ መስቀሉን መሸከም ያለባቸው አማርኛ የሚናገሩ የአዲስ አበባው ድብልቅ ኢትዮጵያውያን እንጂ አንድ ዘር የጥቃት ዒላማ ሊሆን አይገባም። አማርኛ ስለተናገሩ ብቻ አማራውን ሀጢአት ማሸከም ተገቢም ትክክልም አይደለም። ስህተትን በጥፋት ማረምም አይቻልም።
የኦርቶዶክስ ሃይማኖትና አማራን ማጥፋት ኢትዮጵያን የማፍረሻ ቁልፍ ነው ያሉትን የፋሺስት ጣልያኖች መርህ ለሚያስፈጽሙ ደግሞ፣ እንኳን የሰደበ የገደለም ይቅር የሚባባልበትን ባህል ያዳበረ ሕዝብ እንዳለን ልናስታውሳቸው ይገባል። የፋሺስቶቹን መርህ አራማጆቹንም ወገን ብለን አቅፈን ይዘን ብዙ ተጉዘናል። ለኛ ሞት ለመደገስ አይኑን የማያሸውን ተስፋዬንም እንደዚሁ። ያኔ ተቀለደባቸው ተሰደቡ ነው አሁን በኦሮሞ ልጆች ላይ የሚደርሰው ግፍ ምን ስያሜ ይሰጠዋል? ዘረኞች የራሳቸውን ጎሳ ብቻ ሽቅብ ሰቅለው በሌሎች ላይ ሊያደርሱ የሚችሉትን በደል የተመለከትነው አሁን ነው። ምናልባት ተስፋዬ ወደ ወለጋ አላቀና ይሆናል እንጂ እዚያ ደግሞ ጉራጌና አማራው ላይ ብዙ የሚያስቁ ቅጽል ስሞች ይሰጥ እንደነበር አስታውሳለሁ። ከዚያም ያለፉ ነገሮች ሆነዋል ግን ተማርን የሚሉ ጥቂት ሰዎች ያደረጉትን  የኦሮሞ ሕዝብ በሌላው ላይ እንዳለው ጥላቻ አድርጎ መውሰድ አላዋቂነት ነው። የኢትዮጵያ ገበሬ የመሸበትን አሳድሮ የራበውን አብልቶ የሚሸኝ ደግ ሕዝብ ነውና የጥቂቶቹን ክፋት ለሕዝቡ ማሸከም አይቻልም።
አዲስ አበባ ያለው አማርኛ ከዚህም ከዚያም ቃላት ተውሶ ኢተዮጵያንኛ ሆኖአል። እኔ ባደኩበት አካባቢ ስድስትም እንሁን ደርዘን ሁላችንም አንድ ዘር ሆነን አናውቅም። ድብልቅልቅ ነን። እናትና አባትም ከተለያየ ብሄረሰብ የተውጣጡ ሊሆኑ ይችላሉ። ይህ ለኛ ምንም ዋጋ አልነበረውም። ዘር ለመጥላት የሚያነሳሳ ምክንያትም እውቀትም አልነበረንም። ጥርት ያልኩ አማራ የሚለውም የአዲስ አበባ አማርኛ ሲቸግረው እናያለን።  ትልቁ ጥያቄ ይህ ሰዎችን እንደሚያሳዝን በመረዳት አሁን እንዳይደገም ማድረግና ከአንደበታችን የሚወጣውን መመዘን መቻልን ተምረናል ወይስ እዚያው ነን? የሚለው ነው። ባህላችን ሊያድግ ይገባዋል። መፍትሄው ወዲያና ወዲህ መሰነጣጠቃችን አይደለም መጥፎ ወይም ጎጂ የምንለውን ልማድ ማረም ማስተካከልና ከህግም አንፃር ተጎጂዎችን መታደግ የሚቻልበትን መንገድ በጋራ መፈለግ ይመስለኛል። ተስፋዬም ወደ መዝጊያው ላይ ወደዚያው የሚያንደረድር አረፍተነገር ማከሉ ከቡርቃ ዝምታ ጭፍን ጥላቻ ለመውጣት መሞከሩ ይመስለኛል። በዚህኛው ቅጹ ላይ ከአማራ ጥላቻ ወደ ሲስተሚክ ቫዮለንስ ዝቅ ብሎልናል ይህም የኦሮሞ ነጻ አውጪዎች የመገንጠል ጥያቄን ተወት ከማድረጋቸው ጋር ሊቀራረብበት የፈለገበት የብልጥ መንገድ ይመስለኛል። ተስፋዬ ስለ ኢትዮጵያ ግድ የሚለው ቢሆን ኖሮ ሌሎችንም በማማከር የአዲስ አበባው ባህል ምን ይመስል ነበር? ብሎ ትንሽ ምርምር ሊያደርግ በተገባው ነበር። አዲስ አበባ ተወልዶ ላደገ ኦሮምኛ በከተማው ብርቅ ነበር ቢለን ምናልባት መስማት የተሳነው ሰው ወይም በኦሮሞው ስም የፖለቲካ ትርፍ ፈላጊ መሆን አለበት እንላለን።
አዲስ አበባችን ከየትም መጣ ከየት ሰው ጦሙን የማያድርባት ከተማ ነበረች። የኢትዮጵያ ብሄር በሄረሰብ ጭማቂና ራሱን ዘመናዊ አድርጎ የሚጠራ ድብልቅልቁ የወጣ ሕዝብ የሚኖርባት ከተማ ናት። በስልጣኔና ዘመናዊነት ስም ዝርጠጣ፣ ተረብ፣ ስድብና ድብድብም እንደዚያው ጎላ ብሎ የሚታይባት ከተማ ነበረች። ንቅሳታሟን ኒቂሴ ብሎ የሚጠሩት ኦሮሞ ስለሆነች አይደለም መተረብ ስላለባቸው ነው። በዚህ አጠራር የኦሮሞ እናትና አባት ያላቸው ቋንቋውንም አሳምረው የሚናገሩ ልጆች ዘመዶቻቸውን ይተርባሉ። ከወሎም ትምጣ ከጎጃም ‘ኒቂሴ’ የሚለው ስም ሊለጠፍላት ይችላል። ትክክል ነው ማለት አይደለም። ፈጽም ‘ቡሊ’ ማድረግን አጥብቄ የምቃወም ነበርኩ። በልጅነት እድሜዬ በዚህ ምክንያት ቅር የሚሰኙ መኖራቸውን አሳምሬ አውቃለሁ። አንዳንዶችም ከተረብ ለመዳን የመጡበትን ጎሳ ይደብቁ እንደነበር አውቃለሁ። በመጡበት ጎሳ ምክንያት ትምህርት መማር ያልቻሉ ወይም የስራ እድል የተነፈጋቸው ካሉ በኔ እድሜ የማውቀው ባለመኖሩ መመስከር አይቻለኝም። በኦሮምኛ  ቅላጼ ብቻ የሚሳቅ የሚመስላቸው ሰዎች በጣም ተሳስተዋል። ኦሮሞው ግዕዝን ራብዕ ሲያደርጋት ወሎዬውም ‘ደ’ን ሲያጠብቃት ተረብ አለ። በወሎ ቅላጼ የአዲስ አበባ ልጆች በጣም ያፌዙ ነበር፣ በጎጃሙም በጎንደሩም እንደዚሁ። በትግሪኛውም ባልተለየ መልኩ ይቀለድ ነበር። ጉራጌስ ቢሆን ምኑ ተርፎ። ግን ይህ ሁሉየከተሜው ጉራ እንጂ  የዘር ጥላቻ አልነበረም። ይህን ሁሉ ጠልቶስ ማን መሆን ይቻላል? አሁንም ብዙ የአደባባይ ቀልዶች የዚህ አይነት አኪያሄድ አላቸው በሰላም ጊዜ ሊያስቅ ቢችልም በቀውጢ ሰዐት ግን መታረጃም ሊሆን እንደሚችል ሰዎች ልብ ሊሉት ይገባል። ከዚህ አይነት ቀልድ መታቀብም አለባቸው።
አዲስ አበባ ዘር የለም ‘ወልመካ’ ነው ድብልቅልቁ የወጣ። ለዚህም ነው ብዙ የአዲስ ልጆች ዘርህ ምንድን ነው? ለሚለው ጥያቄ መልስ መስጠት የማይችሉት።  አዲሰ አበባ ጥቁር መሆን ያስተርባል፣ ቀይ መሆን ያው ነው። ትልቅ አይን ያለው ጉጉት ትንሽ ዐይን ያለው ጭልፊት ሊባል ይችላል። ቀጭኑ ሲምቢሮ ወይም ወፍ ሲባል ወፍራሙ ወደል ወይም ‘ቦዬ’። ረዥሙም ቀውላላ ነው አጭሩም ኩሩሩ። አፍንጫ ሲተልቅም ስም አለው ልጥፍ ሲሆንም እንደዚያው። እንደጊዜው መለዋወጥ ስም የመለዋወጡ ነገርም ያለ ነው። ይህ የሁላችንንም ስነልቦና የሚነካ ነው። አሁን ኦሮሞም አማራም ወደ መጽሀፍ ቅዱስና ቅዱስ ቁርዐን በመዝለቅ የአይሁድና የአረብ ስም መስጠቱን በሰፊው መያዙም የዚሁ ምሳሌ ነው። ኢዮብ የሚባል ደግና ትዕግስተኛ የመኖሩን ያህል ኢዮብ የሚባል ቀማኛ ሊኖር ይችላል። ስለዚህ አንድ ምሳሌ ሊገልጸው አይችልም። ተስፋዬ ሲባል ግን ወላጆች ራቅ አድርገው የሚመኙትን ይገልጻል። የተስፋዬ ወላጆች የተመኙትን በልጃቸው እያዩ ከሆነ ምንኛ ደስ ይላቸዋል። አርቲስቶቻችን ወደፈረንጅ ጠጋ የሚል በሁለት ፊደል የሚገለጥ ስም ፍለጋ ሲባዝኑ የምናስተውለውም ከዚህ ከጊዜ ጋር የሚመጣ ጉዳይ ነው። ማንጠግቦሽን ማኒ፣ ጎሳዬን ጆሲ ቴወድሮስን ቴዲ አይነት እንደማለት ነው። ይህ ግን ሲስተሚክ ቫዮለንስ ተብሎ ሊፈረጅ የሚችል አይመስለኝም።
ቀደም ባለው ጊዜ አንዳንድ ደካማ መምህራን ተማሪዎቻቸውን የሚያሳቅቁ ነገሮችን አላደረጉም ማለት አይቻልም። በርካታ የኦሮሞ ልጆች በዚህ አይነት ተረብና አስተማሪዎች አማርኛ ለመናገር ሲሞክሩ በሰደቧቸው ምክንያት አቂመው ከፍ ሲሉ ወደ ትግሉ እንደተቀላቀሉ ሲናገሩ ይደመጣል።  ይህ አገር ለመገንጠል ምክንያት ባይሆንም የፖለቲካ ትርፍ ተዝቆበታል። ይህ ባሁኑ ትውልድ እንዳይኖር ማስተማር አስፈላጊ ነው። እንደ ተስፋዬ ግምት ወይም ታሪኩን እነዳጫወቱት ሰዎች ግምት ከተማ ውስጥ የሆነው አማራ ኦሮሞ ላይ ያደረሰው በደል ሳይሆን ከተሜው በጅምላው ገጠሬው ላይ የነበረው ግብዝነት እንደሆነ መረዳቱ አስፈላጊ ነው። በደል አልነበረም፣ አልተደረገም ወይም ሆኖ አያውቅም የሚል የሚኖር አይመስለኝም። ማንም ቢሆን ተፈጥሮ በሰጠው መልኩ፣ ቤተሰብ በሰጠው ስሙና፣ አዲስ ቦታ ላይ አላዋቂ ሆኖ በመታየቱ ሊሰደብ አይገባም ብሎ መነሳቱ የተሻለ ነው። ከዚህ የፖለቲካ ትርፍ መፈለግ ግን ደካማነት ነው።የሆነው ሆኖ አልፏል በዚህ አይነት ሰው የማንኳሰስ ተረብ ምክንያተ ያዘኑ ወገኖች ለደረሰባቸው የስሜት መጎዳት በግሌ በጣም አዝናለሁ። እንደ ከተማው ልጅነቴም ይቅርታ እጠይቃለሁ የሸገር ልጆችም ይህንን ሰሜት እንደሚጋሩኝ አምናለሁ። እንደ አንዳንድ የጭቃ ወስጥ እሾሆች ደባ ግን የዘር ጥላቻ እንዳልሆነ አጥብቄ እሞግታለሁ።
ዘመናዊ ትምህርት ኢትዮጵያና ኢትዮጵያዊነትን መሸርሸሩን ልብ ያለማለት የራሳችንን ጥፋት ለመሸፈንም ምክንያት ሊሆን ይችላል። ምሁራን ባህላችንን ባህላዊ እውቀታችንን እንደ ሁዋላ ቀር በመቁጠር የፈረንጆቹን በመኮረጅ የነበረንን ሁሉ ሲኮንኑ መኖራቸውን ልንክድ አይገባም። በዚህ ምክንያት የኦሮሞውም ሆነ የአማራው ባህላዊ እሴቶች ወደ ጎን ተገፍተው ነበር። በዚህ ውስጥ ከኦሮሞው የወጡ ምሁራንም አስተዋጽኦ ማድረጋቸውን ሊቀበሉ ይገባል። ፈቅደን የተውነውን ተነጥቀን ነበር ብንልም ወደ እውነት የሚያመጣን አይመስለኝም። የሚበጀን ጣት መጠነቋቆልና ወንጀል መፈለጉ ሳይሆን ከዘመናዊ ኑሮ ጋር አጣጥመን ልናሳድጋቸው የሚገቡንን ባህሎቸ መመርመርና ጠቃሚ በሚሆን መልኩ መልሶ ማሳደጉ ተገቢም አስፈላጊም ነው። ተስፋዬም ሲስተሚክ ቫዮለንስን ሲተነትንልን ሀሳቡ ይገባን ይሆናል። እስከዚያው ግን ተስፍሽ ስለ አባት አገሩ እድገትና ብልፅግና ቢጨነቅና የኛን ለኛ ቢተውልን ይሻለዋል እላለሁ።
biyadegelgne@hotmail.com

Tuesday, October 22, 2013

የገቢዎችና ጉምሩክ ተከሳሾች ክስ መሰማት ጀመረ

አለማየሁ አንበሴ
የገቢዎችና ጉምሩክ ተከሳሾች ክስ መሰማት ጀመረ
  • የቀድሞ ኤርፖርት ጉምሩክ ሃላፊ በዋስ ተለቀዋል 
  • በእነ አቶ መላኩ ፈንታ ላይ የቀረበው ክስ ሠኞ እና ማክሰኞ ይሰማል
በከባድ የሙስና ወንጀል በተከሰሱት የቀድሞ የገቢዎችና ጉምሩክ መስሪያ ቤት የተለያዩ ሃላፊዎች እና ሠራተኞች እንዲሁም ታዋቂ ባለሃብቶች ላይ በፌደራል የስነምግባርና ፀረ ሙስና ኮሚሽን አቃቤ ህግ የቀረበው ክስ፣ ልደታ በሚገኘው ከፍተኛ ፍርድ ቤት 15ኛ ወንጀል ችሎት መሠማት የጀመረ ሲሆን በባለሀብቱ አቶ ማሞ ኪሮስ እና በገቢዎች ጉምሩክ ባለስልጣን የቦሌ አየር ማረፊያ ጉምሩክ የፍተሻ የስራ ሂደት መሪ በነበሩት በአቶ ዮሴፍ አዳዩ ላይ የቀረበው ክስ ከትናንት በስቲያ በዋለው ችሎት በንባብ ተሰምቷል፡፡

ተከሳሾችም በክሱ ላይ ያላቸውን የመቃወሚያ ነጥብ ያስመዘገቡ ሲሆን አቶ ዮሴፍ አዳዩ የተከሰሱበት የወንጀል አንቀጽ ከ10 አመት በታች የሚያስቀጣ በመሆኑ የዋስትና መብታቸው ተከብሮላቸዋል፡፡

አቃቤ ህግ በአቶ ማሞ ኪሮስ ላይ ያቀረበው ክስ ተከሳሹ በ1998 ዓ.ም “ከተማ ኮንስትራክሽን ሃላፊነቱ የተወሰነ የግል ኩባንያ”ን በስራ አስኪያጅነት ሲመሩ ከህግ አግባብ ውጪ እቃዎች ከቀረጥ ነፃ እንዲገቡ አድርገዋል ይላል፡፡ ተከሳሹ “የኮንክሪት ሚክሰር” እና “ቫይብሬተር” ከውጭ ከቀረጥ ነፃ ካስገቡ በኋላ፣ ከእሸቱ ኤልያስ ወልደማርያም አስመጪና ላኪ የገዙ ለማስመሰል ሃሰተኛ ሰነድ አዘጋጅተዋል የሚል የወንጀል ክስም ቀርቦባቸዋል፡፡ አቃቤ ህግ በክስ መዘርዝሩ ላይ ስለወንጀሉ አፈፃፀም ያስረዱልኛል ያላቸውን የሰው እና የሰነድ ማስረጃዎች ማቅረቡንም ፍ/ቤቱ የክሱን ጭብጥ በንባብ ባሰማበት ወቅት አመልክቷል፡፡ ክሱ በችሎቱ ከተነበበ በኋላም የቀረበው ክስ የውስብስብነት ባህሪ ስለሌለው በመደበኛ ክርክር ሂደት እንዲቀጥል ብይን ተሰጥቷል፡፡
የተከሳሽ ጠበቃ የመቃወሚያ ሃሳባቸውን ተጠይቀው ሲያቀርቡም፤ የአቃቤ ህግ ክስ፣ ተከሳሽ ራሱን መከላከል በሚያስችለው ደረጃ ተዘርዝሮ በሚገባ የቀረበ አይደለም፣ የተጠቀሰው የወንጀል አንቀጽ (379) በባህሪው የሙስና ወንጀልን አያመለክትም፤ ክሱ የቀረበበት አንቀጽ ተገቢ አይደለም” ብለዋል፡፡ ከእሸቱ ኤልያስ ድርጅት ተጭበረበረ የተባለው ሰነድ የመንግስት ሰነድ አይደለም ያሉት የተከሳሽ ጠበቃ፤ ክሱ በዚህ መልኩ መቅረቡ የተከሳሹን የመከላከል እድል የሚያጠብ ስለሆነ ተሻሽሎ እንዲቀርብ ይደረግልን ሲሉ ጠይቀዋል፡፡ አቃቤ ህግ በበኩሉ፤ ለመቃወሚያው በሰጠው ምላሽ ክሱ ተከሳሹ በሚረዳው መልኩ በዝርዝር የቀረበ ነው፣ የተጠቀሰው አንቀጽ የሙስና ወንጀልን የሚጠቅስ ነው፣ የተጭበረበረው ሰነድ በእርግጥም ከግል ድርጅት የወጣ ነው፤ ነገር ግን የጉምሩክ መስሪያ ቤትን በዚያ ሰነድ አሳስተዋል፤ ስለዚህ ፍ/ቤቱ መቃወሚያውን ውድቅ ያድርግልን ሲል ጠይቋል፡፡

በተመሳሳይ ፍ/ቤቱ በአቶ ዮሴፍ አዳዩ ላይ የቀረቡትን ሁለት ክሶች በንባብ ያሰማ ሲሆን አንደኛው ክስ፣ ተከሳሽ በገቢዎችና ጉምሩክ የአዲስ አበባ ኤርፖርት የመንገደኞች ማስተናገጃ የፍተሻ ክፍል ሃላፊ ሆኖ በሰራባቸው ከ2002 -2003 ባሉ አመታት ከውጭ ወደ ሃገር ውስጥ የሚገቡ የተለያዩ ግለሰቦች ለያዙት እቃ ቀረጥ ሳይከፍሉ እንዲገቡ በማሰብ፣ ሳይፈተሹ እንዲያልፉ አድርጓል የሚል ነው፡፡ ከዚሁ ክስ ጋር ተያይዞም ንብረትነታቸው የገቢዎችና ጉምሩክ የሆኑ ኦርጅናል የስራ ሰነዶችን መኖሪያ ቤቱ አስቀምጦ ተገኝቷል የሚል የወንጀል ክስ ቀርቦበታል፡፡ በተከሳሹ ላይ የቀረበው ሁለተኛ ክስ ደግሞ ህጋዊ ፍቃድ የሌለው ማካሮቭ ሽጉጥ ይዞ ተገኝቷል የሚል ነው፡፡ ለክሶቹ የሰነድና የሰው ማስረጃ እንዲሁም በኤግዚቢት የተያዙ ንብረቶች መቅረባቸውን በክሱ ማመልከቻ ተጠቅሷል፡፡

የተከሳሽ ጠበቃ የመቃወሚያ ሃሳባቸውን ያቀረቡ ሲሆን ወንጀሉ ተፈፀመ የተባለበት ትክክለኛ ቀን በዝርዝር አልተገለፀም፣ የግለሰቦቹ ማንነትና ብዛት በግልጽ መታወቅ ነበረበት፣ የጉምሩክ ሰነዶች በቤቱ ተገኝተዋል የተባለው በየትኛው የወንጀል አንቀጽ እንደሚያስጠይቅ አልተጠቆመም ብለዋል፡፡ ፍቃድ የሌለው መሣሪያ ይዞ መገኘት የሚለውን በተመለከተም ኮሚሽኑ እንዲህ አይነት ክስ ማቅረብ አይችልም፤ ጉዳዩ ከሙስና ጋር የሚገናኝ ስላልሆነ በሌላ አካል ነው መታየት ያለበት ስለዚህ ክሱን ይሰርዝ ሲሉ ጠበቃው መቃወሚያቸውን አቅርበዋል፡፡

አቃቤ ህግ ለመቃወሚያው በሰጠው ምላሽ፤ ድርጊቱ የተፈፀመው በተለያየ ጊዜ ነው፣ ሳይፈተሹ እንዲያልፉ የተደረጉት ግለሰቦች ብዛት እና ማንነት ምስክሮች ሲቀርቡና ማስረጃ በዝርዝር ሲቀርብ በሂደት የሚታይ ይሆናል፣ ሰነዶችን በተመለከተም ኦርጅናል የመስሪያቤቱን ሰነዶች ማስቀመጥ የነበረበት መኖሪያ ቤቱ ሳይሆን መስሪያ ቤት ነው ብሏል፡፡ ህገ ወጥ መሣሪያ ይዞ መገኘት በእርግጥ የሙስና ወንጀል አይደለም፤ ነገር ግን ክሱን አብሮ ለማቅረብ የስነ ስርአት ህጉ እንደሚፈቅድ በሰበር ሰሚ ችሎት ተወስኗል የሚል ምላሽ ሰጥቷል - አቃቤ ህግ፡፡

የተከሳሹ አቶ ዮሴፍ አዳዩ ጠበቃም የተጠቀሰው አንቀጽ ከ10 አመት በታች የሚያስቀጣ ስለሆነ የዋስ መብትን የሚያስከለክል አይደለም፤ የዋስትና መብቱ ይከበር ሲሉ ፍ/ቤቱን የጠየቁ ሲሆን አቃቤ ህግም በዋስ ቢለቀቁ ተቃውሞ እንደሌለው፣ ነገር ግን ከሃገር እንዳይወጡ ለኢምግሬሽንና ዜግነት ጉዳይ ትዕዛዝ ይፃፍልን ሲል አመልክቷል፡፡

የግራ ቀኙን ክርክር ሲያደምጥ የቆየው ፍ/ቤቱ፤ በአቶ ዮሴፍ አዳዩ ላይ በሰጠው ትዕዛዝ፣ ተከሳሹ የ5ሺህ ብር ዋስ አቅርበው እንዲለቀቁ እንዲሁም ከሀገር እንዳይወጡ ለኢምግሬሽንና ዜግነት ጉዳይ ደብዳቤ እንዲፃፍ ብሏል፡፡ መዝገቡንም ለጥቅምት 25 ቀን 2006 ዓ.ም ቀጥሯል፡፡ በአቶ ማሞ ኪሮስ ላይ ፍ/ቤቱ በሰጠው ትዕዛዝ፣ መቃወሚያውን መርምሮ ብይን ለመስጠት ለጥቅምት 14 ቀን 2006 ቀጥሯል፡፡

በሌላ በኩል ክስ ሳይመሰረትባቸው ጉዳያቸው ወደ ምርመራ መዝገብ የተመለሠው አቶ ፍፁም ገ/መድህን፣ በእግዚአብሔር አለበልና ምህረተአብ አብርሃ ጥቅምት 6 ቀን 2006 ፍ/ቤት ቀርበው ዳኞች ተሟልተው ባለመቅረባቸው ለጥቅምት 12 ቀን 2006 ዓ.ም ተለዋጭ ቀጠሮ ተሰጥቷል፡፡

አቶ መላኩ ፋንታ እና አቶ ገ/ዋህድ ወ/ጊዮርጊስን ጨምሮ ክስ ቀርቦባቸው ማረሚያ ቤት የሚገኙ ባለስልጣናትና ባለሀብቶች ጥቅምት 11 እና 12 ቀን 2006 ዓ.ም ክሣቸውን ለማንበብ ቀጠሮ መሰጠቱ ይታወሳል፡፡

http://www.addisadmassnews.com

ዶ/ር መረራ የፍንዳታውን ዜና “እንጠራጠረዋለን” አሉ

"በአዲስ አበባው ፍንዳታ የሞቱት ኢትዮጵያዊያን ናቸው"

bole 1


በአዲስ አበባ ቦሌ ክፍለ ከተማ ሩዋንዳ ሰፈር የደረሰውን ፍንዳታ አስመልክቶ ኢህአዴግ ያሰራጨውን ዜና የሚቃረኑ መረጃዎችና አስተያየቶች ቀረቡ። ለኢህአዴግ ቅርበት ያላቸው የፖለቲካ ፓርቲዎች የድጋፍ አስተያየት ሲሰጡ ዶ/ር መረራ “አትፍቶ ጠፊ አጥፍቶ ይጠፋል እንጂ በሜዳ ዝም ብሎ አያጠፋም” ሲሉ ጥርጣሬ እንዳላቸው ተናግረዋል። የትግራይ ህዝብ ዴሞክራሲያዊ ንቅናቄ /ትህዴን/ በፍንዳታው የሞቱት ኢትዮጵያውያን ናቸው ሲል ስም ገልጾ የኢህአዴግን ዜና አጠጥሎታል።
በፓርላማ አስቸኳይ ስብሰባ እንዲጠራ የጠየቁት ከኢህአዴግ ጋር ግንኙነት እንዳላቸው የሚታሙ ፓርቲዎች “የጸረ ሽብርተኞች አዋጅ ሊጠናከርና ሊጠብቅ ይገባል” ሲሉ ተደምጠዋል። የኢትዮጵያ ቴሌቪዥን ያነጋገራቸው የኢራፓ፣ የኢሴዳፓ፣ ቅንጅትና አዲአን ተወካዮች በየተራ የኢህአዴግን ዜና የሚቃወሙና በጥርጣሬ የሚመለከቱትን አውግዘዋል። በወቅቱ የቴሌቪዥን ጣቢያውም አንድነትና የሰማያዊ ፓርቲ ጠርተውት በነበረው ሰላማዊ የተቃውሞ ሰልፍ ላይ “የጸረ ሽብርተኛነት አዋጅ ለሌላ ተግባር መዋሉን እንቃወማለን” በማለት የተቃውሞ ድምጻቸውን ሲያሰሙ በማሳየት ዜናውን ለማጀቢያነት ተጠቅሞበት ነበር።
በግል አስተያየታቸውን የተጠየቁት ዶ/ር መረራ ጉዲና በቴሌቪዥን መስኮት ቀርበው “ብዙዎች፣ እኔም ጓደኞቼም በጥርጣሬ ነው ያየነው” ሲሉ ከተቆረጠው ንግግራቸው ተደምጧል። ዶ/ር መረራ “አጥፍቶ ጠፊ አጥፍቶ ይጠፋል እንጂ በሜዳ ዝም ብሎ ራሱን አያጠፋም” ካሉ በኋላ “ስለዚህ እውነት ተደርጓል?” የሚለው ትልቁ ችግርና የጥርጣሬው መነሻ እንደሆነ አመልክተዋል።
ስለዚህ በሚል ድምዳሜ “ሰው አንዳንድ ጊዜ የኢትዮጵያ መንግስት ለራሱ ፖለቲካ ብሎ የሚያደርገው ያው የለመደው ስራ ነው” እንደሚል ዶ/ር መረራ በተቀነጨበው አስተያየታቸው ሲናገሩ ተሰምቷል። በተቃራኒ ከላይ በስም የተዘረዘሩት የፖለቲካ ፓርቲ አመራሮች፣ ኢትዮጵያ የሽብር ጥቃት ኢላማና የአልሸባብ ስጋት ላይ ያለች አገር በመሆኗ ኢህአዴግ ህዝብን የመጠበቅና ደህንነትን የማስጠበቅ አደራ ስላለበት እነሱን ጨምሮ እንዲጠብቃቸው ጥሪ አቅርበዋል።
ከቅርብ ጊዜ ወዲህ ስሙ የሚነሳውና በታጣቂ ሃይሉ ፈርጣማነት የሚታወቀው የትግራይ ህዝብ ዴሞክራሲያዊ ንቅናቄ  /ትህዴን/ በቦሌ ክፍለ ከተማ በቤት ውስጥ ፈነዳ በተባለው ፈንጂ ህይወታቸው እንዳለፈ የተገለጸው ሁለት የሶማሌ ዜጎች አይደሉም ሲል ከሁሉም ወገን የተሰራጨውን ዜና በዜሮ አጣፍቶታ። በፈንጂው የሞቱት ሁለት ሰዎች ኢትዮጵያዊያን መሆናቸውን ስማቸውም “ምክትል ኢንስፔክተር ሞላ መላኩ የተባሉ የፖሊስ አባልና አቶ ሞገስ አስቻለው የተባሉ ሲቪል ናቸው” ሲል የገለጸው ትህዴን የሟቾቹ ስም በመታወቂያ መረጋገጡን አመልክቷል።የመታወቂያውን ቅጂ ግን በገጹ አላተመም። ከአደጋው ጋር በተያያዘ በስፍራው ታይታችኋል በሚል በርካታ የተቃዋሚ ፓርቲ አባላት መታሰራቸውን በመግለጽ የሶስት እስረኞችን ስም ይፋ ያደረገው ኦክቶበር 19 ቀን 2013 በራሱ ኦፊሳላዊ ድረገጽ ላይ ነው። ኢህአዴግም ቢሆን ሞቱ የተባሉትን ሰዎች ይህ ዜና እስከተጻፈበት ቀን ድረስ በሰነድ አስደግፎ አላቀረባቸውም።
በሌላ በኩል ኦክቶበር16 ለንባብ የበቃው ሪፖርተር ጋዜጣ ጥቅምት 3ቀን 2006ዓ.ም. በቦሌ ክፍለ ከተማ ሩዋንዳ ማዞሪያና ቦሌ ሚካኤል መግቢያ አካባቢ በቦምብ ፍንዳታ ሕይወታቸው ያለፈው ሁለት ሶማሊያውያን ሽብርተኞች መሆናቸውን ማረጋገጡን፣ የፌዴራል ፖሊስ የፀረ ሽብር ግብረ ኃይል ማስታወቁን ዘግቧል።
Bomb-Blast-Addisየአንድ ግለሰብ ሰርቪስ ቤት ተከራይተው ከነበሩት ሶማሊያውያኑ መካከል፣ አንደኛው ከ20ቀናት በላይ የቆየ ሲሆን፣ ሌላኛው ፍንዳታው ከመድረሱ ከሁለት ሰዓታት በፊት የደረሰ መሆኑን ግብረ ኃይሉ ማረጋገጡን ያመለከተው ሪፖርተር ሽብርተኛ የተባሉት ሶማሊያውያኑ ካፈነዱት ቦምብ በተጨማሪ መጠናቸው ያልተገለጸ ቦምቦችና አንድ ሽጉጥ ከሁለት ካርታ ጥይት ጋር መገኘቱን፣ የፈንጂ ማቀጣጠያና የአደጋ መከላከያ ጃኬቶች፣ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን ማሊያና ቀበቶዎች መገኘታቸውም ጠቁሟል፡፡ ከሶማሊያውያኑ ጋር ቀጥታ ግንኙነት አላቸው የተባሉ ሦስት ተጠርጣሪዎችና የቤቱ አከራይ በቁጥጥር ሥር ውለው ምርመራ እየተካሄባቸው መሆኑንም ግብረ ኃይሉ አክሏል በማለት ሪፖርተር ዘግቧል። አዲስ አድማስ በበኩሉ አልሸባብ ለጥቃቱ ሃላፊነት መውሰዱን አድራሻው አልተመዘገበ የትዊተር ማረጋገጫ በማመላከት ከዚህ በታች ያለውን ዜና አስነብቧል።
ባለፈው እሁድ በቦሌ ሚካኤል አካባቢ ከደረሰው ፍንዳታ ጋር ተያይዞ ሁለት ተጨማሪ የፍንዳታ ጥቃት ለማድረስ አልሸባብ የተሰኘው የሶማሊያ ቡድን እንደዛተ የገለፀው የአሜሪካ ኤምባሲ፤ የዛቻው ተአማኒነት ባይረጋገጥም በኢትዮጵያ የሚገኙ አሜሪካዊያን ጥንቃቄ እንዳይለያቸው ሁኔታው አሳሳቢ እንደሆነ በመግለጽ ዜናውን የከፈተው አዲስ አድማስ፣ “የኢትዮጵያና የናይጄሪያ ቡድኖች ግጥሚያ በሚካሄድበት ሰዓት ጥቃት ለመፈፀም ሲዘጋጁ የነበሩ ሁለት ሰዎች መሞታቸው የሚታወስ ሲሆን በኢትዮጵያ ላይ ጦርነት በማወጅና ሽብር ለመፈፀም በመዛት የሚታወቀው አልሸባብ “ድርጊቱ በኔ አባላት የተፈፀመ ነው” ብሏል በማለት አልሸባብ በቦሌ ሚካኤል ለተከሰተው ፍንዳታ ሃላፊነት እንደሚወስድ በትዊተር እንዳስታወቀ ማሰራጨቱን፤ በፒያሳና በቸርችል ጐዳና አካባቢ የፍንዳታ ጥቃት ለመፈፀም እንደዛተም ገልጿል፡፡
በቦሌ ሚካኤል በአንድ መኖሪያ ቤት ውስጥ በተከሰተው ፍንዳታ ሁለት የሶማሊያ ተወላጆች መሞታቸውን የገለፀው ፖሊስ፤ ከሟቾቹ አንዱ የኢትዮጵያ ማሊያ በመልበስ ከኳስ ተመልካቾች መሃል የፍንዳታ ጥቃት ለመፈፀም እየተዘጋጀ እንደነበር መጠቆሙን አዲስ አድማስ በዜናው አውጇል። አዲስ አድማስም ሆኑ ሪፖርተር ፖሊስ የነገራቸውን ከመዘገብ ውጪ ከሌሎች ሚዲያዎች፣ በተለያዩ ማህበረ ገጾችና በቅርበት ከህብረተሰቡ የሚሰጡትን አስተያየቶች አስመለክቶ ዜናውን ላቀበላቸው ክፍል አላቀረቡም።
የኢህአዴግ አንደበትና የንግድ ድርጅት የሆነው ፋና ብሮድካስቲንግ በአዲስ አበባ ቦሌ ክፍለ ከተማ የደረሰው የፈንጂ ፍንዳታ በሁለት ሶማሊያውያን አሸባሪዎች የተፈፀመ መሆኑን የፌዴራል ፖሊስ ኮሚሽነር ጄኔራል አሰፋ አብዩን ጠቅሶ አስታውቋል።
ፋና ብሮድካስቲንግ ኮርፖሬት እንዳለው ፍንዳታው የደረሰው በክፍለ ከተማው ወረዳ 01 ቀበሌ 01 በተለምዶ ሩዋንዳ ተብሎ በሚጠራው አከባቢ በአንድ የመኖሪያ ቤት ውስጥ ነው። ፖሊስ ፍንዳታው ፈንጂ መሆኑንና በጥቅም ላይ የዋለው ቲ ኤም ቲ የተባለ የፈንጂ ዓይነት መሆኑን እንደደረሰበት አረጋግጧል። ፍንዳታውንም ሁለት ሶማሊያውያን ማቀነባበራቸውን ፖሊስ እንዳረጋገጠና ግለሰቦቹ የአሸባሪ ቡድኑ አልሸባብ አባል መሆናቸውን የሚያሳዩ መረጃዎች መገኘታቸውን ጄኔራል አሰፋ አብዩ መናገራቸውን የጠቆመው ፋና ከሁለቱ አሸባሪዎች መካከል አንደኛው ወገቡ ላይ የታጠቀና ለአጥፍቶ ጠፊ ተግባር የተዘጋጀ መሆኑን ያመላክታል ብሏል።
ሌላኛው አሸባሪ በሻንጣ ፈንጂ የያዘ ሲሆን፥ የፈነዳውም ፈንጂ በሻንጣው ውስጥ የነበረ መሆኑን ነው ጀነራል አሰፋ ያስረዱት። ለአጥፍቶ ጠፊ ተግባር ሲዘጋጅ የነበረው ግለሰብ የታጠቀው ፈንጂ ግን እንዳልፈነዳ አመልክተዋል። አሸባሪዎቹ በአጠቃላይ ሶስት ፈንጂዎችንም ይዘው ነበር። አሸባሪዎቹ ህዝብ ባለበት ስፍራ አደጋ ለማድረስ ተከራይተው በነበሩበት ቤት ውስጥ ሲዘጋጁ ፍንዳታው ደርሷል ብሎ ፖሊስ እንደሚጠረጥር ነው የጠቆሙት። ከአሸባሪዎቹ ጋር ፖሊስ የእጅ ቦምቦችንና ሽጉጥ ከነጥይቱ አግኝቷል።
የፋናን ዜና ተንተርሶ የተሰነዘሩ አስተያየቶች እንደሚያመለክቱት ሪፖርተር በፈነዳው ፈንጂ ህይወቱ ያለፈው አንደኛው ሰው ሰውነቱ መበታተኑና የአይን እማኞችን ገልጾ መዘገቡን ያስታውሳሉሉ። ፈነዳ የተባለው ፈንጂ ከፈነዳ በሁዋላ አጥፍቶ ለመጥፋት የተዘጋጀው ሰው የታጠቀው ፈንጂ አለመፈንዳቱ መገለጹ ከሙያ አንጻር ጥያቄ የሚያስነሳ እንደሆነ፣ ከዚህም በላይ ድርጊቱን ከኢትዮጵያ ብሔራዊ ቡድን ጨዋታ ጋር ለማገናኘት የብሔራዊ ቡድን መለያ ሹራብ ተገኘ መባሉ ድርጊቱን ድራማ ያስመስለዋል ባይ ናቸው። (ፎቶ: ሪፖርተር)

የኢህአዴግ ቀጣይ የፖለቲካ ሴራዎች (ጋዜጠኛ ተመስገን ደሳለኝ)


የሁለት ሺህ ስድስት ዓመተ-ምህረት የመጀመሪያ ወር ተጠናቅቋል፤ አዳዲስ ክስተቶችም ታይተዋል፤ ያለፉት አስራ ሁለት ዓመታትን በጃንሆይ ቤተ-መንግስት ያሳለፉት ፕሬዝዳንት ግርማ ወ/ጊዮርጊስ፣ በኦህዴዱ ሙላቱ ተሾመ መተካታቸው አንዱ ነው፡፡ አባይ ፀሀዬና ዶ/ር ካሱ ኢላላም ከበረከት ስምዖንና ኩማ ደመቅሳ በተጨማሪ በሚኒስትር ማዕረግ የኃ/ማሪያም ደሳለኝ ‹‹የፖሊሲና ጥናት ምርምር›› አማካሪ ሆነው መሾማቸው ሌላው ነው (በነገራችን ላይ ሹመቱን እንደተለመደው አይቶ ችላ ብሎ ለማለፍ የማያስችሉ ሶስት ምክንያቶች አሉ፤ የመጀመሪያው በሀገሪቱ ለአንድ የሥራ መደብ አራት ሚንስትር ተሹሞ አለማወቁ ሲሆን፤ ሌላው ተሿሚዎቹ፣ ኢህአዴግን ከመሰረቱት አራት ፓርቲዎች በኮታ የተወጣጡ መሆናቸው ነው፡፡ ሳልሳዊውና አስገራሚው ደግሞ ሰዎቹ ፖለቲከኞች እንጂ ከጉዳዩ ጋር በተያያዘ ጥናትና ምርምር ያካሄዱ ምሁራን አለመሆናቸው ነው)Journalist Temasegan Dasaleg
እነዚህ ሁሉ በግልፅ የሚታወቁ የዓመቱ መጀመሪያ ክስተቶች ናቸው፡፡ ለስርዓቱ ቅርበት ካላቸው ምንጮቼ ባገኘሁት መረጃ መሠረት፣ በቅርቡ ‹ሚዲያ›ን እና ‹የይቅርታ ስነስርዓት›ን የተመለከቱ አዳዲስ አዋጆች በተወካዮች ም/ቤት ለመፅደቅ ተዘጋጅተዋል፡፡ በተለይም ‹ሚዲያው›ን የሚመለከተው አዲሱ ህግ፣ ከአምስት ዓመት በፊት ተግባር ላይ የዋለውን የ‹‹ፕሬስ አዋጁ››ን የአፋና ጉልበት ይበልጥ የሚያጠናክር በመሆኑ፣ የነበረው አንፃራዊ ጭላንጭል ጭራሽ ሊዳፈን እንደሚችል መረጃዎች ያሳያሉ፡፡ ‹‹የይቅርታ አዋጁ››ም ቢሆን ጥቂት የአገዛዙ ጉምቱ ባለስልጣናት ‹‹የተቃዋሚ ፓርቲ የአመራር አባላትና አንዳንድ የግል ጋዜጠኞች ብንታሰርም በይቅርታ እንፈታለን በሚል ግንባሩን እየተፈታተኑ ነው›› ሲሉ ደጋግመው መደመጣቸውን፣ ከአዲሱ ‹‹የይቅርታ አሰጣጥ እና አፈፃፀም ሥነ-ሥርአት አዋጅ›› ጋር ካያያዝነው፣ አንቀፆቹ ሊኖራቸው የሚችለውን አንድምታ መገመቱ ብዙ ከባድ አይሆንም፡፡
ለማንኛውም ኢህአዴግ ከመቼውም ጊዜ በላይ ጉልበታም በመሆን ቀጣዩን ምርጫ በስኬት ለማለፍ፣ በያዝነው ዓመት የተለያዩ አፋኝ ህጎችን በማውጣት ፓርቲዎቹን የማዳከም ስራ ለመስራት በተለየ መልኩ መዘጋጀቱ ተሰምቷል፡፡ በአናቱም ኃ/ማርያም ደሳለኝ-ከመንግስት፣ ከፓርቲውና ከውስን የግል ጋዜጠኞች፤ ደመቀ መኮንን-ከአዲስ ዘመን ጋዜጣ፤ ሽመልስ ከማል -ከኢዜአ ጋር ያደረጓቸው ቃለ-መጠይቆችም ይህንን መረጃ የሚያጠናክር ሆኖ አግኝቸዋለሁ፡፡ የዚህ ፅሁፍ ተጠየቅም አገዛዙ በቀጣይ ሊኖረው የሚችለውን ባህሪ እና ‹አምስተኛው ዙር ሀገር አቀፍ ምርጫ›ን አስቀድሞ ለማሸነፍ እየቀመረ ያለውን ሴራ መጠቆም ነው፡፡
የባለስልጣናቱ አንደበት
ጠ/ሚኒስትር ኃ/ማርያምና ምክትሉ ደመቀ ሰሞኑን ለጋዜጠኞች በሰጡት ቃለ-መጠይቅ ላይ፣ በስሱም ቢሆን ከጀርባቸው ያደፈጡትን አንጋፋ ታጋዮች ቀጣይ ‹‹የፖለቲካ ሴራ›› (Political Conspiracy) አርድተውናል ብዬ አስባለሁ፡፡
ሁለቱ መሪዎች በዋናነት እንዲያተኩሩ የተደረገው በአራት ጉዳዮች ላይ ነው፡፡ በግንባሩ ውስጥ ክፍፍል መፈጠሩን መካድ፣ አመቱን ሙሉ ‹የመለስ ራዕይ› እየተባለ የተዘመረለትን ‹እሳት ማጥፊያ› ፕሮፓጋንዳ ማስተባበል፣ የሙስና ክሱን ሂደትና ውጤት መሸፋፈን እንዲሁም ተቀናቃኝ ፓርቲዎችን ማስፈራራት የሚሉ ናቸው፡፡ በአዲስ መስመርም እነዚህን አራት አጀንዳዎች ነጣጥለን ለመዳሰስ እንሞክራለን፡፡
ክፍፍሉን በተመለከተ
ከመለስ ህልፈት ማግስት አንስቶ በግንባሩ ግልፅ ክፍፍል መከሰቱ የአደባባይ ሀቅ ቢሆንም፣ ጠ/ሚኒስትር ኃ/ማሪያም ‹‹ፓርቲዎ ውስጥ ክፍፍል አለ ይባላል፤ የኃይል አሰላለፍ እየተጠበቀ ነው የሚኬደው የሚባሉ አሉባልታዎች ይሰማሉ፣ የፓርቲዎ ጤናስ እንዴት ነው?›› የሚል ጥያቄ ሲቀርብለት፡-
‹‹በፓርቲዬ ውስጥ ክፍፍል አለ የሚለው ጥያቄ የምኞት ነው፤ ብዙ ምኞቶች ሲሰሙ ነበር፤ ምኞት አይከለከልም፡፡ ስለዚህም ምኞት ይኖራል የሚል ሃሳብ ከማቅረብ በዘለለ እውነት ስለሌለው ምኞት ነው ብሎ ማለፍ ነው›› በማለት አስተባብሎ ሲያበቃ፤ ከደቂቃዎች በኋላ ደግሞ ተገልብጦ ‹‹አሁን በቅርቡ እንደደረስንበት አንዳንድ ጊዜ በየቦታው ደባ የሚሰሩ ጥቂት የመሥሪያ ቤት ሰራተኞች አሉ›› ብሎ የራሱ ሰዎች በመንግስቱ ላይ እያሴሩበት እንደሆነ በመግለፅ ከላይኛው ንግግሩ ጋር መጣረሱ፣ በርግጥም የተጠቀሰው ችግር መኖሩን ለመረዳት አያዳግትም፡፡
ይህንኑ ጉዳይ በተመለከተም ‹‹አዲስ ዘመን›› ጋዜጣ ምክትል ጠ/ሚኒስትር ደመቀ መኮንንን ከዚህ ቀደም ባልተለመደ መልኩ አጠንክሮ ጠይቆት ያስተባበለበት መንፈስም ለመሸሸግ የፈለገው ጉዳይ እንዳለ የሚያሳብቅ ይመስላል፡፡
‹‹አንድ ግልፅ መሆን ያለበት እንደ አቶ መለስ ያለ ታላቅ መሪ፣ ታግሎ የሚታገል ጠንካራ መሪን ማጣት ትልቅ ጉድለት ነው፡፡ ጉድለቱ እንዲሁ ዝም ተብሎ እዚያና እዚህ በዘመቻ የሚሞላ ጉዳይ አይደለም፡፡ …ስለዚህም ሁለት በምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ደረጃ ኃላፊዎችን በመሰየም ክላስተር እንዲያስተባብሩ ማድረግ ያለመተማመን መገለጫ አይደለም፡፡››
የሁለቱ ሚኒስትሮችን ያልተጠበቀ ቃለ-መጠየቅ መግፍኤ ለመረዳት በተለይ ደመቀ መኮንን ለቀረቡለት ጥያቄዎች የሰጠውን ምላሾች በጥልቅ መፈተሽ አስፈላጊ ነው፡፡ ምክንያቱም ተከስቶ የነበረውን መከፋፈልም ሆነ ‹ፓርቲው በጥቂት የህወሓትና የብአዴን ታጋዮች ነው
ጋዜጠኛ ተመስገን ደሳለኝ
የሚሽከረከረው› መባሉን ለማስተባበል የሄደበት መንገድ፣ ከዚህ ቀደም ኢህአዴግ የሚከራከርባቸውን እምነቶቹን ጭምር እስከመናድ የደረሰ ነውና፡፡ ወይም እንዲንድ ታዝዟል ያስብላል (በነገራችን ላይ ከምንጮቼ ባገኘሁት መረጃ እነአባይ ፀሀዬና በረከት ስምዖንም ከመጋረጃው ጀርባ የሚሰራ ኃይል መኖሩን ማስተባበል ይፈልጋሉ፡፡ በተለይም ‹‹በነፃነት እንዲሰሩ አመቻቹላቸው›› እያሉ የሚወተውቷቸውን ምዕራባውያን ዲፕሎማቶች ማሳመኑ ከባድ ሥራ እንደሆነባቸው ሰምቻለሁ፡፡
የሰሞኑ የቃለ-መጠይቅ ጋጋታም ይህንኑ የሚያጠናክር ይመስላል፡፡ ‹‹አዲስ ዘመን›› ጋዜጣም ለደመቀ መኮንን ያቀረባቸው ጥያቄዎች ከቀደመው ታሪኩ አኳያ ሲመዘን የግል እምነቱ አለመሆኑን መረዳት አያዳግትም፡፡ ‹‹ጋዜጣው እስከአሁን ያልነበረውን ‹የኤዲቶሪያል ነፃነት› ዛሬ አግኝቶ ነው ሰውየውን እንዲህ ያፋጠጠው›› የሚል ተከራካሪ ካልቀረበ ማለቴ ነው፡፡ ምናልባትም ጉዳዩን በሌላ አውድ እንየው ከተባለ ደግሞ የሚያያዘው፣ የድርጅቱ አመራሮች አልፎ አልፎ ህዝብ ዘንድ የደረሱ እውነታዎችን፣ በራሳቸው ጋዜጠኞች እንዲጠየቁ በማድረግ ለማስተባበል ከሚሞክሩበት የቆየ ልማዳቸው ጋር ብቻ ነው፡፡ በመስከረም 22፣ 23 እና 24 ቀን 2006 ዓ.ም በታተመው የ‹‹አዲስ ዘመን›› ጋዜጣ በተስተናገደው የደመቀ መኮንን ቃለ-መጠይቅ ላይ የተነሱትን ጥያቄዎች ብንመለከት ይህንኑ ያረጋግጡልናል፡፡ ‹‹ፓርቲው በጥቂት ሰዎች ስር ስለመውደቁ፣ ከመንግስት ኃላፊነት የተነሱ ባለስልጣናት በፓርቲው ውስጥ ስራ-አስፈፃሚ ሆነው ስለመቀጠላቸው፣ መተካካቱ የቦታ መቀያየር ብቻ ስለመሆኑ፣ ሥራ የማይሰሩ ደካማ መሆናቸውን በተወካዮች ም/ቤት ጭምር የተረጋገጠባቸው ከፍተኛ አመራሮች ዛሬም በኃላፊነት ቦታ ላይ ስለመቀመጣቸው፣ በብልሹ አሰራር /በሙስና/ የተጠየቁ ባለስልጣናት ጥቂት ብቻ መሆናቸው፣ በአቅም ማነስ የሚነሱ ኃላፊዎች ወይ ከነበሩበት የተሻለ አሊያም ተመጣጣኝ በሆነ ደረጃ ስለመመደባቸው፣ አንድ ጊዜ የላይኛውን የስልጣን እርከን የተቆናጠጠ ባለስልጣን ከፓርቲው ቁልፍ አመራሮች ጋር ካልተጋጨ በቀር አቅም ባይኖረውም እንደማይሻር፣ ለፓርቲው መስራቾችና እስከአሁንም ወሳኝ ለሆኑት አመራሮች ታማኝ የሆነ ኃላፊ ምንም አይነት ድክመትና ወንጀል ቢፈፅምም በስልጣን መቆየት መቻሉን፣ የሁለቱ ተጨማሪ ምክትል ጠ/ሚኒስትሮች ሹመት በአራቱ የብሔር ድርጅቶች መካከል ያለውን አለመተማመን ስለማሳየቱ፣ ሁሉም ፓርቲዎች እኩል አለመሆናቸውን፣ መለስ በሃያ ሁለት የሥልጣን ዓመታቱ ተተኪ ማፍራት አለመቻሉን፣ ‹የመለስ ራዕይ› የሚባል ነገር አለመኖሩን…›› እና ተያያዥ ጉዳዮችን በተመለከተ ባልተለመደ ድፍረት የጠየቀው መንግስታዊው ዕድሜ ጠገብ ‹‹አዲስ ዘመን›› ጋዜጣ ነው)
ቃለ-መጠየቁ ከእነዚህ በተጨማሪም ቀጣዩን የኢህአዴግ አቅጣጫ አመላክቷል፡፡ የሆነው ሆኖ ክፍፍሉንና ከጀርባ ሆነው ያሽከረክራሉ የሚባሉትን አንጋፋ የአመራር አባላት አስመልክቶ ለቀረበለት ጥያቄ ከሰጠው ምላሽ ውስጥ እንዲህ የሚል ይገኝበታል፡-
‹‹ፓርቲው አንድ ሰው፣ ሁለት ሰው፣ ሶስት ሰው እጅ ጠምዝዞ ‹ይሄን አድርጉ› በሚል አንዳችም ጉዳይ የሚያስፈፅምበት አይደለም፡፡ …ኢህአዴግ በጥቂቶች የሚመራ ድርጅት አይደለም፡፡ …ጥቂት ግለሰቦችን በተለየ ሁኔታ የሚያይ፣ በእነርሱም ስር የሚሆን አይደለም፡፡ የጥቂቶች ነው የሚለው ከእውነት የራቀ ነው፡፡ …ማንም በራሱ ተቆጥሮ በተሠጠው ሥራ ሊወስን፣ ሊመራና ሊንቀሳቀስ ይችላል፡፡ በድርጅታዊ ዲሲፒሊንና አሰራር፣ የግልና የጋራ አሰራር በሚዛን ተቀምጦ በንቅናቄ የሚመራ እንጂ በግለሰቦች አይደለም የሚለው ቢሰመርበት ጥሩ ነው፡፡››
በርግጥ ይህንን ያነበበ ‹‹ሰውየው ስለየትኛው ኢህአዴግ ነው የሚያወራው?›› ቢል ላይፈረድበት ይችላል፡፡ ምክንያቱም የድርጅቱ የታሪክ ንባብም ሆነ የቀድሞዎቹ ስዬ አብርሃ፣ አለምሰገድ ገ/አምላክ፣ አውዓሎም ወልዱ፣ ገብሩ አስራት፣ አረጋሽ አዳነ፣ ነጋሶ ጊዳዳ፣ ሀሰን አሊ፣ አልማዝ መኩን የመሳሰሉት የአመራር አባላት የነገሩን ‹ድርጅቱ በጣት በሚቆጠሩ ሰዎች ፍቃድ የሚያድር› መሆኑን ነው፡፡ ለነገሩ ራሱ ደመቀም ቢሆን ከኤርትራ ጋር ወደ ጦርነት ለመግባት ህወሓት በር ዘግቶ ብቻውን መምከሩንም ሆነ የግንባሩን አባል ድርጅቶች ነፃነት እንዳሻው መጋፋቱን አምኖ መቀበል ባይፈልግ እንኳን፣ በ1999 ዓ.ም መጨረሻ ከሱዳን ጋር የሚዋሰነው የጎንደር መሬት ላይ የተላለፈው ውሳኔ በምን መልኩ እንደነበረ ሊክደው አይችልም (በነገራችን ላይ በወቅቱ የአማራ ክልል አስተዳዳሪው አያሌው ጎበዜ ምክትል የነበረ በመሆኑ፣ ከዚሁ ጋር ተያይዞ ጎንደርና ትግራይ አካባቢ፣ የሚወራበትን ውንጀል በሌላ ጊዜ እመለስበታለሁ)
የሰውየው መከራከሪያ ግን እውነት አለመሆኑን ‹ፍትህ›ና ‹ልዕልና› ጋዜጦች፤ ‹አዲስ ታይምስ›ና ‹ፋክት› መፅሄትን ጨምሮ የምዕራብ ሀገራት ብዙሃን መገናኛ እና ድርጅቱን በቅርብ የተከታተሉ ምሁራን በተለያየ ጊዜ ማስረጃ በማጣቀስ ደጋግመው ስላቀረቡ ተጨማሪ ማብራሪያ ያስፈልገዋል ብዬ አላስብምና ወደ ቀጣዩ ጉዳያችን አልፋለሁ፡፡
‹‹መተካካት›› ሲባል…
በአንድ ወቅት አቶ መለስ ብዙ ብሎለት የነበረው የመተካካት ዕቅድ ‹‹ቦታ ከመቀያየር ያለፈ አዲስ ፊት አላመጣም›› መባሉን በተመለከተ፣ ደመቀ መኮንን የሰጠውን ምላሽ፣ ከተለያየ አውድ ካየነው ከላይ የተጠቀሰውን ክፍፍል በሌላ በኩል ይነግረናል፡፡ ምክንያቱም መለስ በህይወት በነበረበት ዘመን ጉዳዩን አስመልክቶ የነገረን ‹መተካካቱ ከላይ ያሉትን ነባር የአመራር አባላት፣ በየተራ በጡረታ በማሰናበት አዲሱን ትውልድ (አዲስ ፊት) ወደመሪነት ማምጣት ነው› የሚል እንደነበረ ይታወሳል፡፡ ደመቀ መኮንን ደግሞ በግልባጩ እንዲህ ይላል፡-
‹‹አዲስ ፊት ሲባል የማናውቀው ሰው ከጨረቃ ይምጣ? የሚመራው እኮ አገር ነው፡፡ አንድ ሰው አንድ ቦታ ላይ ሆኖ ሥራውን እየተወጣ፣ ሌላውንም እያበቃ ሥርዓቱ መቀጠል አለበት፡፡ በጣም የሚታወቅ ህዝባዊ አገልግሎት ላይ ያለ ሰው፣ ከያዘው ኃላፊነት ሌላ፣ በሌላ ጊዜ ሌላ ተክቶ ሊቀርብ ይችላል፡፡ አዲስ ፊት የለም፤ የማናውቃቸው ሰዎች ይምጡ ማለት፣ ሀገር የሙከራ ቦታ ይሁን ማለት ነው፡፡››
ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ እንዲህ የሚደክመው በረከት ስምዖን፣ አባይ ፀሀዬ፣ ኩማ ደመቅሳ፣ ሽፈራው ጃርሶ፣ ካሱ ኢላላ፣ ሙላቱ ተሾመን… የመሳሰሉ አንጋፋ መሪዎች ከዚህ ቀደም ለአባላቶቻቸው የገቡትን ቃል ጠብቀው በክብር ከመሰናበት ይልቅ ስልጣን መቀያየራቸውን ለማስተባበል ይመስለኛል፤ በርግጥ ጉዳዩን ከለጠጥነው ቀጣዩ ጠቅላይ ሚኒስትር ከአንጋፋዎቹ መካከልም ሊሆን ይችላል እያለን ይሆናል፡፡ ይሁንና ሰውየው ያስተባበለበት መንገድ ግን በውስጡ ካለው እውነታ ጋር የተቃረነ በሚመስል መልኩ
የመተካካቱ አንድምታ የተቀየረው በመካከል የተፈጠረውን የኃይል ልዩነት አርግቦ፣ ስርዓቱ ከገጠመው መንገራገጭ ወጥቶ በሁለት እግሩ ቀጥ ብሎ ቆሞ እንዲቀጥል ለማስቻል መሆኑን ፍንጭ ይሰጣል፡፡
‹‹መተካካት ግለሰብን አይደለም የሚተካው፤ የስርዓት ቀጣይነትን ማረጋገጥ ነው!››
ይህ ሁናቴ በደንብ የሚፍታታው አቦይ ስብሃት ነጋ በተለይ ህወሓት ውስጥ የተካሄደው መተካካት ከተፈጠረው ልዩነት ጋር ተያይዞ መሆኑን ለ‹‹ውራይና›› መፅሄት የሰጡትን ቃለ-መጠየቅ ስናነብ ነው፡-
‹‹ጉባኤው ከማዕከላዊ ኮሚቴ ለተሰናበቱ ሰዎች ከዚህ ቀደም እንደሚያደርገው፣ አሰራር ለምን እነሱን በሌሎች መተካት እንዳስፈለገ፣ ተራ በተራ እየጠቀሰ አስተያየት (ማብራሪያ) መስጠት ነበረበት፡፡ ይህ ተደርጎ ቢሆን ኖሮ ከተሰናባቾቹ መካከል ማዕከላዊ ኮሚቴ ውስጥ መቆየት (መቀጠል) የሚገባቸው በተገኙ ነበር፡፡ ከተመረጡት ውስጥ ደግሞ መሰናበት (በሌላ መተካት) የሚኖርባቸው ሊገኙ ይችሉ ነበር፡፡ ስለዚህ አካሄዱ ስህተት ስለሆነ ውጤቱም እንደዚያው ሊሆን ችሏል፡፡ እነማን መሰናበት፣ እነማን መቆየት እንደነበረባቸው በዝርዝር ስም ጠርቼ መናገር እችል ነበር፡፡ ግን ምንም ለውጥ ስለማያመጣ ስም መዘርዘሩ አስፈላጊ አይመስለኝም፡፡››
የ‹‹ራዕዩ›› ጉዳይ…
በፋክት መፅሄት ቁጥር 5 ላይ ኢህአዴግ ‹የመለስ ራዕይ› እያለ ይደሰኩርለት የነበረውን አጀንዳ በወራት ጊዜ ውስጥ ገልብጦ በማጠቋቆር ሊቀየረው መዘጋጀቱ ተጠቅሶ እንደነበረ ይታወሳል፡፡ በደመቀ መኮንን ቃለ-መጠይቅ ላይም፣ መለስ ሥልጣን ላይ በነበረበት ዘመን ተገምግሞ መንግስታዊ ተቋማትንና የልማት ዕቅዶችን በአግባቡ መከታተልና መቆጣጠር አለመቻሉ ተገልጿል፡፡
‹‹ያለፉት ዓመታት ሥራዎቻችንን ስንገመግም ጠቅላይ ሚኒስትራችን ብዙ ሥራ ተሸክመው ይሰሩ በነበረበት ዋና ዋና የልማት ሥራዎቻችን ላይ በማተኮር አንዳንድ የሚኒስቴር መስሪያ ቤቶችና የልማት መስኮችን በሚፈለገው ደረጃ ያለመፈተሽ፣ በዝርዝር ዕቅድ ግምገማና ድጋፍ ያለማድረግ ክፍተቶች እንደነበሩ እንደ ችግር በጋራ ያገኘናቸው ነጥቦች አሉ፡፡››
እንዲያ ሀገር-ምድሩ ‹ካልዘመረለት ተደፍረናል!› ሲሉለት የነበረው ‹‹የመለስ ራዕይ››ም ቢሆን የኢህአዴግ እንጂ የመለስ አለመሆኑን እየነገሩን ነው፡፡ አቶ ደመቀም፣ መለስ የነበረው ‹‹ራዕይ›› ሳይሆን ኃላፊነት ነው ወደ ማለቱ አዘንብሏል፡፡
‹‹ይሄን የዕድገት መንገድ ከኢህአዴግ አባላትና ከመሪዎቹ ጋር በመሆን በግንባር ቀደምነት የመሪነት ቁልፍ ሚና የተጫወቱ መሪ ናቸው፡፡››
በጥቅሉ በወቅታዊው የድርጅቱ ፖለቲካዊ አተያይ ‹‹የመለስ ራዕይ›› የሚለው ሀረግ ከየት እንደመጣ የተተነተነበትን አውድ ለመረዳት ከጋዜጣው ላይ አንድ ተጨማሪ ጥያቄና መልስ እንደወረደ ልጥቀስ፡-
‹‹አዲስ ዘመን፡- በየዘርፉ ራዕያቸው ተብለው የሚነገሩት መልእክቶችና መሪ ቃሎች ጋር በተያያዘ የተለጠፈባቸው ራዕይ እንዳለ ነው የሚነገረው፤ አገሪቱን ከመሩበት 22 ዓመታት ጊዜ ውስጥ ምናልባት አንድ ጊዜ በንግግር መሀል የተናገሯት ወይም ለጋዜጠኞች የሰጡት ምላሽ ራዕይ ተደርጎ እየቀረበ ነው ስለሚባለውስ?
‹‹አቶ ደመቀ፡- እነዚያ መልዕክቶች ያንን ራዕይ የሚገልፁ፣ የሚያስታውሱ ምልዕክቶች ናቸው፡፡ ከማንኛውም ጉዳይ ጋር የተያያዙ መልዕክቶች ይኖራሉ፡፡ እነዚያ ያንን ትልቁን ራዕይ የሚመግቡ መልዕክቶች እንደሆኑ አድርጎ መመልከት ይቻላል፡፡››
ይኸው ነው፤ በቃ፡፡ መለስ ራዕዩን በጥሩ ቋንቋ ከመግለፅ ባለፈ የብቻው የሆነ ነገር የለውም፡፡ በክፍፍሉ ወቅት ከ‹አዲስ አበባው-ህወሓት› ጎን የተሰለፉት አቦይ ስብሃት ነጋ በጉባኤ፣ በተለያዩ ጋዜጦችና መፅሄቶች እንዲሁም አርከበ እቁባይ በህወሓት ጉባኤ ላይ የመለስ ‹ራዕይ› የሚባል ነገር አለመኖሩን በመግለፅ፣ በወቅቱ በአሰላለፍ የተመሳሰሉት ‹የመቀሌው-ህወሓት› እና ብአዴን በ‹ራዕይ› ስም ኃይል የማጠናከር እንቅስቃሴ ማድረጋቸውን ለመተቸትና ለማደናቀፍ መሞከራቸው ይታወሳል፡፡ ይህ ሁናቴም ልዩነቱ ከተገለፀባቸው ምልክቶች አንዱ ተደርጎ ተወስዷል፡፡ ሌላው እዚህ ጋ መነሳት ያለበት ጉዳይ በዚህ ዓመት በዚሁ መፅሄት ላይ ‹‹አዲሱ የኢህአዴግ አሰላለፍ›› በሚል ርዕስ የቀረበው ፅሁፍም ‹‹የመለስ ራዕይ››ን የማይቀበለው ቡድን እያሸነፈ በመምጣቱ፣ የእነ አዜብ-አባይ ወልዱ ህወሓትን አዳክሞ፣ የእነ በረከት-ብአዴንን ከጎኑ ማሰለፍ መቻሉን የተተነተነበትን ጉዳይ የሚያጠናክር መሆኑን ነው፡፡
የሆነው ሆኖ አሁን መለስን የሚያመልኩት ሄደዋል፤ በቦታውም እርሱ የሚያርቃቸው፣ እነርሱም ይፈሩት የነበረ ተተክተዋል፡፡ እናም በህልፈቱ ማግስት ድጋፍ ማሰባሰቢያ እና ኃይል ማጠናከሪያ ከመሆን አልፎ ሀገሪቱን ወደ ብልፅግና ሰማይ የሚያከንፍ፣ መና የሚያዘንብ ተደርጎ የነበረውን ‹‹የመለስ ራዕይ›› ታሪክ በማድረጋቸው፣ አርቀው መስቀል ይፈልጋሉ፡፡ በሌላ አነጋገር በፋውንዴሽኑ አጥር ክልል ተወስኖ ይቀመጥ ዘንድ በይነዋል (በነገራችን ላይ ይህን ጉዳይ በዚህ ደረጃ ያነሳሁት የስርዓቱ መሪዎች ‹‹እንመራዋለን›› የሚሉትን ህዝብ በአደባባይ ሲዋሹ ቅንጣት ያህል ሀፍረት እንደማይሰማቸው ለማሳየት እንጂ፣ በግሌ መለስም ሆነ ጓደኞቹ ለስልጣናቸው ካልሆነ በቀር ሀገር የሚጠቅም ራዕይ አላቸው ብዬ አላምንም)
የ‹‹ሙስና››ውን ክስ ሂደት መሸፋፈን:
የእነ መላኩ ፈንቴን እስር ተከትሎ ‹‹ሙስና›› ዋነኛ አነጋጋሪ አጀንዳ ሆኖ ነበር፡፡ በወቅቱ ጠቅላይ ሚኒስትር ኃ/ማሪያምም ‹ጉዳዩን ራሴ እከታተለዋለሁ› የምትል ፉከራ ብጤም ሞካክራው ነበር (ቀደም ሲል በዚሁ መፅሄት የ‹ሙስና›ው ክስ በፖለቲካው የኃይል አሰላለፍ ላይ የበላይነትን ለመጨበጥ በአዲስ አበባው ህወሓት የተመዘዘ ‹‹ካርድ›› እንደሆነ መገለፁ ይታወሳል)
ባለሥልጣናቱ የታሰሩ ሰሞን ‹‹የመለስ ራዕይ›› ገና አልከሸፈም ነበርና ‹‹የፀረ-ሙስና ኮሚሽን›› ኮሚሽነር አሊ ሱለይማንም ጉዳዩን አቶ መለስ ራሱ ጀምሮት ለሁለት ዓመት ያህል ሲከታተለው ከቆየ በኋላ፣ በመጨረሻ ህይወቱ እንዳለፈ እያለቃቀሰ ነግሮን ነበር፡፡
ይሁንና
ከእስራ አምስት ቀን በፊት ኃ/ማሪያም ደሳለኝ ባደረገው ቃለ-መጠይቅ፣ የታሰሩትን ሰዎች አስመልክቶ ከጊዜ ቀጠሮ ያለፈ ቁርጥ ያለ ነገር አለመኖሩ፣ በሌሎች ላይ ስጋት ስለመፍጠሩ ተጠይቆ በሰጠው ምላሽ ‹ገድሉ›ን ከመለስ ወደራሱ (ከኋላው ወደአሉ ሰዎች) መልሶታል፡፡
‹‹በቅርቡ በገቢዎችና ጉምሩክ ባለስልጣን አካባቢ የተፈጠረውን ችግር ለማቃለል በሙስና የተጠረጠሩ የባለሥልጣኑ ኃላፊዎችና በሙስና ተግባሩ ላይ የተሰማሩ ባለሀብቶች ተጠያቂ የሚሆኑበት ስርዓት ተዘርግቶ የመንግስት አካል የሆነው የፌደራል ሥነ-ምግባርና ፀረ-ሙስና ኮሚሽን ክስ መስርቷል፡፡››
ጥያቄውም ይህ ነው፡፡ ‹‹የአሊ ሱሊማንን ‹መለስ የጀመረው…› መግለጫንስ ምን እናድርገው?››
…ደመቀ መኮንንም ‹‹እዚያም እዚያም ከኃላፊነት የማውረድ፣ በሕግ የመጠየቅና ሕጋዊ እርምጃዎች ደረጃቸውን ጠብቀው ይቀጥላሉ›› ቢልም በመሬት ያለው ተጨባጭ እውነታ ግን የሚያሳየው ሙስና የተዘጋ አጀንዳ መሆኑን ነው፡፡ የ‹‹አዲስ ዘመን›› ጋዜጣ የፊት ገፆችም ‹‹ሚኒስትር እገሌ…››፣ ‹‹ዳይሬክተር እገሌ… በሙስና ተጠርጥረው በቁጥጥር ስር ዋሉ›› ከሚል ዜና በብርሃን ፍጥነት ‹‹በቂርቆስ ክ/ከተማ ወረዳ 10 የዲዛይንና ግንባታ ፍቃድ ጽ/ቤት፣ የግንባታና ዕድሳት ባለሙያ የነበረችው ግለሰብ መስከረም 21 ቀን 2006 ዓ.ም አራት ሺ ብር ጉቦ ስትቀበል በፌደራል የሥነ-ምግባር እና የፀረ-ሙስና ኮሚሽን ሠራተኞች እጅ ከፍንጅ ተያዘች›› ወደሚል ቧልት ተቀይረዋል፡፡
አቦይ ስብሃት ነጋ ከላይ በጠቀስኩት መፅሄት የሙስናውን ጨዋታ የገለፁት እንዲህ በማለት ነበር፡-
‹‹አሁንም ድረስ ያልተፈቱ የአካሄድ (የአሰራር) ችግሮች አሉ፡፡ ለምሳሌ ‹ሙስና አለ› ብትል፣ ሙስና በስርዓቱ ላይ በሚያደርሰው አደጋ ላይ ከማተኮር ይልቅ ‹አንተስ ከሙሰኛነት ነፃ ነህ ወይ?› በማለት ዋናው ሀገራዊ ጉዳይ ላይ ቀዝቃዛ ውሃ የሚቸልሱ ሰዎች ጥቂት አይደሉም፡፡ አሁንም ቢሆን ይህንን የከፋ ድርጅታዊ ጉዳይ (ችግር) በመጋረጃ ሸፋፍኖ ለማለፍ ‹ስብሃት ለምን በጊዜው ጉባኤው ላይ አላቀረበውም ነበር› የሚሉ አይጠፉም የሚል ግምት አለኝ፡፡ በበኩሌ ይህ ነገር በሌላ ላይ ጊዜው ሲደርስ የሚነሳ ይሆናል ነው የምለው:፡››
በርግጥ የአቦይ ወቀሳ እውነት ነው፡፡ ይሁንና ጉዳዩን በጉባኤው ላይ ያላነሱበት ምክንያት ‹‹በሌላ ላይ ጊዜው ሲደርስ የሚነሳ ይሆናል›› በሚል እንደሆነ ለመናገር መሞከራቸው ግን የክፍለ ዘመኑ አስቂኝ ቀልድ ከመሆን የዘለለ ፋይዳ የለውም፤ ባይሆን ‹‹አንተስ ከሙሰኛነት ነፃ ነህ ወይ?› ይሉኛል ብዬ ተውኩት›› ቢሉን፣ ቢያንስ ለግልፅነታቸው ባርኔጣ እናነሳ ነበር፡፡ ምክንያቱም በኢትዮጵያ ሰማይ ስር የኢህአዴግ ሰዎችን የሙስና ወንጀል በህግ የሚያስጠይቅ ከሆነ አቦይ ስብሃት ከፊት መስመር መሰለፋቸው አይቀርምና፡፡ ሌላው ቀርቶ አርከበ እቁባይ ለጊዜው ገለል እንዲል (ከሀገር እንዲወጣ) የተደረገው ከዚሁ ጋር በተያያዘ እንደሆነ የመረጃ ምንጮቼ ነግረውኛል፡፡ አርከብ፣ አቦይን ጨምሮ ከታሰሩት ባለሀብቶች ውስጥ ጥቂቶቹ በስጋ ዝምድናና በጋብቻ የተሳሰሩት የመሆኑ ጉዳይ ይመስለኛል ‹ማዕበሉ እስኪረጋ› ከዕይታ እንዲርቅ የተደረገበት ምስጥር፡፡ በተቀረ አርከበ ሀገር ጥሎ ኮበለለ፣ ኢህአዴግን ከዳ… ጂኒ ቁልቋል የሚሉት የፒያሳ ወሬዎች፣ አንድም ወቅታዊውን የኢህአዴግ አሰላለፍ ካለመረዳት ሊሆን ይችላል፤ አሊያም የጉዳዩ ባለቤቶች ስራዬ ብለው የተሳሳተ መረጃ በሚያስተላልፉበት በተለመደው ሰርጥ ያሰራጩት ማስቀየሻ ነው የሚሆነው፤ አርከበ የሄደው አቦይ እንዳሉት ‹‹አንተስ ከሙስና ነፃ ነህን?›› የማለቱ አቅም ያላቸውን አጉረምራሚ ሰዎችን ለማለዘብ ነው፡፡ ምናልባት የመቀሌው ህወሓት አሸንፎ ቢሆን ኖሮ እውነትም አርከበ ከቃሊቲ ይልቅ አሜሪካ ይሻለዋል ማለታችን አይቀርም ነበር፡፡ እነርሱም ቢሆኑ በእጁ ላይ ካቴና ለማጥለቅ አያመነቱም፡፡ ግና! የሆነው በተገላቢጦሹ ነው፡፡ …ማን ነበር ‹‹አባቱ ዳኛ…›› ያለው? (በነገራችን ላይ ኢህአዴግ የሙስና አዋጁንም በዚሁ ዓመት የማሻሻል ዕቅድ አለው፡፡)
የአፈናው ዝግጅት:
ስርዓቱ በሚቀጥለው ዓመት የሚደረገው አምስተኛ ዙር ሀገር አቀፍ ምርጫን ከወዲሁ ‹የቤት ስራን በማጠናቀቅ› ካልተዘጋጀንበት፣ ያልተጠበቀ አደጋ ሊያመጣብን ይችላል ወደሚል ጠርዝ የተገፋው አንድነት እና ሰማያዊ ፓርቲ በተለያየ ጊዜ በጠሩት የተቃውሞ ሰልፍ ላይ የተገኘው ህዝብ ቁጥር አሳስቦት ብቻ አይመስለኝም፡፡ ይልቁንም ኢህአዴግ ወደ ሥልጣን ከመጣ በኋላ ያለ መለስ ዜናዊ የሚጋፈጠው የመጀመሪያው ምርጫ በመሆኑም ጭምር ነው፡፡ እንደሚታወሰው አቶ መለስ ሁሉንም የሥልጣን ምንጮች ጠቅልሎ የያዘ ‹ጠንካራ ሰው› (Strong Man) በመሆኑ፣ በእንዲህ አይነት ወቅት የሚመጡ ድንገቴ አደጋዎችን ለመቋቋም ብዙም ሲቸገር አይስተዋልም ነበር፡፡ ይሁንና በቀጣዩ ምርጫ አንድም በድርጅቱ ውስጥ የእርሱ አይነት ተተኪ ሰው አለመኖሩ፣ ሁለትም ምንም እንኳ ከህልፈቱ በኋላ የተፈጠረው ልዩነት በአንፃራዊነት የተረጋጋ ቢመስልም፣ ለሌላ ዙር የክፍፍል አደጋ አለመጋለጡ አስተማማኝ ባለመሆኑ ስጋት መፍጠሩ የሚጠበቅ ነው፡፡ በአናቱም ከእስልምና እምነት ተከታዮች ጋር የተከሰተው አለመግባት እና በማህበረ ቅዱሳን ላይ ተፅእኖ ለማድረግ የመሞከሩ ጨዋታም ለተቀናቃኞች ያልተጠበቀ ኃይል ሊሆን የሚችልበት ዕድል ቢፈጥርስ የሚል ስጋት አለ፡፡
የባለሥልጣናቱ በአደባባይ የማስፈራራት መግፍኤም ይኸው ነው፡፡ ጠ/ሚኒስትር ኃ/ማሪያም በቃለ-መጠይቁ ላይ ተቃዋሚዎችን (አንድነትና ሰማያዊን) እና የሀይማኖት ማህበራትን ለማስፈራራት ከሰባት ጊዜ በላይ የመለስን ‹‹ቀይ መስመር›› አገላለፅ ተጠቅሞበታል፡፡ በተለይም ሁለቱ ፓርቲዎች የያዙት በሠላማዊ ሠልፍ ተፅዕኖ የመፍጠር መንገድ ተከታዮቻቸውን እያበዛ እና የፈዘዘውን የፖለቲካ ተሳትፎ እያነቃቃው መሆኑን ግንባሩ ጠንቅቆ የተረዳው ይመስለኛል፡፡ በኃ/ማሪያምም በኩል ያስተላለፈው መልዕክትም ቀጣዩን የፖለቲካ ሴራ አመላካች ነው፡-
‹‹መታወቅ ያለበት አንድ ጥያቄ በተደጋጋሚ የሚጠየቅ ከሆነ፣ እኛም አንድ ቦታ ስንደርስ ‹ለዚህ ጥያቄ ብዙ ጊዜ መልስ ሰጥተናል፤ ጥያቄው ይህ ከሆነ የሠልፍ ትርጉም ምንድነው?› ብለን የምናቆምበት ደረጃ እንደርሳለን፡፡ ምክንያቱም ሠልፍ ለዘላለም የሚካሄድበት ሀገር ያለ አይመስለኝም፡፡››
በተመሳሳይ መልኩ የሃይማኖት ማህበራት የሚያነሱትን የመብት ጥያቄም ወዴት ሊገፋው እንደሚችል ጥቁምታ ሰጥቷል፡-
‹‹የሀይማኖት ግብንም አክራሪዎች በምድር ላይ ሊሰሩ የሚፈልጉትን ግብ ሁለቱን የሚያምታቱ ሰዎች አሉ፤ የሌላውን ግብ በምድራዊ ዓለማዊ ማሳካት ስለማይቻል፣ እነዚህ ፖለቲከኞች ይዘዋቸው እንዳይነጉዱ፣ ከህዝብ እንዲነጠሉ ምክር ማስተላለፍ እፈልጋለሁ፡፡ የሚታወቁ ስላሉ፡፡ በተለይ ወጣቶች፣ ከወጣቶችም ወጣት ሴቶች በአሁኑ ወቅት በዚህ ውስጥ ተሳትፈው የሚጓዙ እንዳሉ በግልፅ ይታወቃሉ፡፡ መንግስት በዚህ ደረጃ ለእነዚህ አካላት መልዕክት ማስተላለፉ ጠቃሚ ነው ብዬ አምናለሁ፡፡››
የኮሙኒኬሽን ጉዳዮች ጽ/ቤትን በሚንስትር ዴኤታ ማዕረግ የሚመራው ሽመልስ ከማልም ከ‹‹ኢትዮጵያ ዜና አገልግሎት (ኢዜአ)›› ጋር ያደረገውና ጥቅምት 3 ቀን 2006 ዓ.ም በታተመው ‹‹አዲስ ዘመን›› ጋዜጣ ላይ በወጣው ቃለ-ምልልስ እንደተለመደው ጉዳዩን በተመለከተ ጠንከር ያለ ማስፈራሪያና ማስጠንቀቂያ ለማስተላለፍ የፈለገ (የታዘዘ) መስሎ አግኝቸዋለሁ፡-
‹‹አንዳንድ የተቃዋሚ የፖለቲካ ፓርቲዎች ሕጉን እናሰርዛለን፣ ሕጉ ሰብዓዊ መብት የሚጥስ ነው ብለው በአደባባይ የቅጥፈት ፕሮፓጋንዳ ሲያሰሙ የሚታዩና በተዘዋዋሪ መንገድ ከሽብርተኞች ጋር ለሽብርተኞች የሞራል ድጋፍ ሲሰጡና ሲቸሩ የምናያቸው አንዳንድ ወገኖች ሳያውቁ፣ ግንዛቤ ሳይኖራቸው በቀና መንገድ ተሳስተው ነው የሚል ግምት ሊኖር የሚገባው አይመስለኝም፡፡
እነዚህ ወገኖች አውቀው ነው ይህንን ሥራ የሚሰሩት፤ በስሌት ነው ይህን የሚከናውኑት፡፡››
በእርግጥም የስርዓቱ የሴራ ቀማሪዎች ‹‹አንድነት እና ሰማያዊ ፓርቲ በአዲስ አበባ የፈጠሩት መነቃቃት፣ በጊዜ ካልተቋጨ በሚቀጥለው ዓመት በሚደረገው ምርጫ ‹ባልታወቀ ስፍራ የተኛ ሰይጣን ቀስቅሶ፣ ድንገቴ ማዕበል ሊያስነሳ ይችላል›› የሚለው ትንተናቸው ይመስለኛል ቀድሞም የጠበበውን ምህዳር ይበልጥ ለማጥበብ (ለመድፈን) ከወዲሁ እላይ-ታች እንዲሉ ያስገደዳቸው፡፡
እንደ መውጫ:
ስርዓቱ በብዙ መልኩ ያለ ስኬት ከሃያ ሁለት ዓመታት በላይ መጓዙ እርግጥ ነው፡፡ በተቃውሞ ሰፈርም ይህንን ሁናቴ ለመለወጥ አብዛኛውን ዓመታት የበረዶ ያህል ቢቀዘቅዝም፣ አልፎ አልፎ እየጋመ ለውጥ ለማምጣት ያደረገው ሙከራ፣ አገዛዙ ካከማቸው ኃይል ጋር ባለመስተካከሉ ደጋግሞ መምከን አሳዛኝ ዕድል ፈንታ ሆኖ ቆይቷል፡፡ በዚህ ዓመት የተያዘው ዕቅድም ከቀድሞ በባሰ መልኩ፣ ለመደራጀት የሚውተረተረውን ኃይልም ሆነ ተበታትኖና ተከፋፍሎም ቢሆን ለውጥ የሚጠይቀውን ህዝብ በተለያየ መንገድ ማቀዝቀዝ ላይ የሚያተኩር ነው፡፡ ለዚህም ይመስለኛል ጉዳዩን በደንታቢስነት ማየቱ ይህ እውን ሆኖ የ2002ቱ የምርጫ ድል፣ በ2007 ዓ.ምም ይደግም ዘንድ ፍቃድ የመስጠት ያህል ነው የምለው፡፡
አሁንም አረፈደም፡፡ ነገር ግን ፈረንጅኛው እንደሚለው ‹‹እውነቱ ግድግዳው ላይ ተፅፏል›› የፖለቲካ ፓርቲዎች፣ የሲቪክ ማህበራት፣ ለውጥ ፈላጊ ዜጎች… ስርዓቱ ለህዝብ ፍላጎት ይገዛ ዘንድ ከዚህ ቀደም ያልተሞከሩ (በሰላማዊ ትግል ማዕቀፍ ውስጥ ያሉ) አማራጮችን ከመተግበር ውጪ ጠረጴዛው ላይ የተቀመጠ ተጨማሪ ‹የዕድል ቁጥር› አለመኖሩን መቀበል ይኖርባቸዋል፡፡