FREE ALL POLITICAL PRISONERS

FREE ALL POLITICAL PRISONERS
FREE ALL POLITICAL PRISONERS

Tuesday, December 17, 2013

በደቡብ ሱዳን የመፈንቅለ መንግሥት ሙከራ ከሸፈ

የጎሣው ፍጥጫ እስካሁን አልለየለትም

kiir s


በደቡብ ሱዳን የፕሬዚዳንት ሳልቫ ኪርን መንግሥት ለመገልበጥ እሁድ ማታ ለሰኞ አጥቢያ ሙከራ ተደርጎ መክሸፉ ተሰማ፡፡ ፕሬዚዳንቱ ሙከራው መክሸፉንና መንግሥት ሁሉንም ነገር በቁጥጥር ሥር ማዋሉን በመግለጽ ለደቡብ ሱዳን ሕዝብ መግለጫ ሰጡ፡፡ በዋንኛው ጎሣ ዲንቃ እና ኑዌር ጎሣ መካከል የተከሰተው ፍጥጫ እስካሁን የለየለት መስመር አልያዘም፡፡
Pagan Amum
ፓጋን አሙን
ከወራቶች በፊት የደቡብ ሱዳን ነጻ አውጪ ንቅናቄ (ኤስ.ፒ.ኤል.ኤም.) ዋና ጸሐፊ የሆኑት ፓጋን አሙን የአመራር ብክነትና ሌሎች ችግሮች አሉባቸው በሚል እንዲገመገሙ ፕሬዚዳንቱ የመርማሪ ኮሚሽን አቋቁመው ነበር፡፡ ኮሚሽኑ ዋና ጸሐፊው የአመራር ጉድለት የታየባቸው በመሆኑ ከሥልጣን እንዲነሱ የውሳኔ ሐሳብ ሰጥቷል በሚል ፕሬዚዳንት ሳልቫ ኪር ዋና ጸሐፊውን ጨምሮ የአገሪቱን ምክትል ፕሬዚዳንት ዶ/ር ሬይክ ማቻር ከሥልጣናቸው ባለፈው ሐምሌ ወር አስወግደው ነበር፡፡ ከዚሁ ጋር ተያይዞም ኪር ካቢኔያቸውን በሙሉ ከሥልጣን በማባረር አዲስ የካቢኔ ሲያዋቅሩ ቆይተዋል፡፡
ሁኔታው በተከሰተበት ወቅት ብዙሃን በሆኑት የሳልቫ ኪር ዲንቃ ጎሣ እና ቀጣዩ አብላጫ ቁጥር ባላቸው የኑዌር ጎሣዎች መካከል ያለውን የኃይል ፍጥጫ በግልጽ የሚያሳይ መሆኑ ተነግሮ ነበር፡፡ ከዚሁ ጋር በተያያዘም ፕሬዚዳንቱ አምባገነናዊ አካሄድ እየተከተሉ መሆናቸው እና ሁኔታው ወደ ከፍተኛ ደረጃ መድረሱ የማይቀር መሆኑ ሲተነበይ ቆይቷል፡፡
ለንዶን ለሚታተመው አሻራቅ አል-አውሳት ቃለምልልስ የሰጡት ዋና ጸሐፊ አሙም የኤስ.ፒ.ኤል.ኤም. ካውንስል ስብሰባ ላይ እንዳይገኙ ፕሬዚዳንቱ እንዳስከለከሏቸው ይናገራሉ፡፡ አሙም ሲቀጥሉም “የፖሊት ቢሮ አባል እንደመሆኔ ልከለከል አይገባኝም” በማለት በአሁኑ ጊዜ አገራቸው ወደ ሥርዓት አልበኝነት እየተጓዘች መሆኗን ተናግረዋል፡፡ ሳልቫ ኪርንም ኤስ.ፒ.ኤል.ኤም. ከተቋቋመበት ዓላማ ውጪ ድርጅቱንና አገሪቷን እየመሯት እንደሆነ በመናገር አማሯቸዋል፡፡ በአገራቸው ላይ ሥርዓት አልበኝነት እየሰፈነ መሆኑን በመግለጽ የንቅናቄው ዋና መሥራች የነበሩት ጆንግ ጋራንግ ከሞቱ ወዲህ አመራሩን የተቆጣጠሩት ሳልቫ ኪር ወደ አምባገነናዊ አገዛዝ እያመሩ መሆናቸውን ተናግረዋል፡፡
ዶ/ር ሬይክ ማቻር
ዶ/ር ሬይክ ማቻር
በ2015 ለሚካሄደው ምርጫ ራሳቸውን እጩ ተወዳዳሪ አድርገው ለማቅረብ እያዘጋጁ የነበሩት ምክትል ፕሬዚዳንት ዶ/ር ሬይክ ማቻር በሳልቫ ኪር ከሥልጣን መባረራቸው በቀላሉ የሚያቆም ሳይሆን ወደከፋ የፖለቲካ ፍጥጫ ብሎም የጎሣ ግጭት እንደሚቀየር በአጽዕኖት ይታመናል፡፡ በጦሩ ውስጥ ይኸው የዘር ልዩነት መኖሩና በዲንቃ እና ኑዌር መካከል ያለው ጥላቻ አላስፈላጊ መጋጨት ፈጥሮ ችግሩ እንዳይሰፋ ቢታሰብም ይኸው ልዩነት አገርሽቶ ለመፈንቅለ መንግሥት ሙከራ እንደበቃ ይታመናል፡፡ ከኑዌር ጎሣ የሆኑት ማቻር ከሥልጣን በተወገዱበት ወቅት አገራቸው ወደ “አንድ ሰው የበላይነት” እያመራች መሆኗን ተናግረው ነበር፡፡
በሳልቫ ኪር አመራር የተማረሩት ሌላዋ የጆን ጋራንግ ባለቤት ርብቃ ጋራንግ ናቸው፡፡ ባለፈው ሳምንት ለራዲዮ በሰጡት ቃለምልልስ ሲናገሩ “ይህችን አገር በተገቢው ሁኔታ እየመራናት አይደለም፤ ከዚህ ይልቅ ቀውሶችን ለማስተካከል ስንሞክር ነው የቆየነው፡፡ ባለቤቴ ከሞተ ወዲህ ምንም ደስተኛ አይደለሁም፤ ሳልቫ ኪር ለምን ደስተኛ እንዳልሆንኩ ጠይቆኝ አያውቅም፡፡ ኑሮን ለማሸነፍና ልጆቼን ለማሳደግ ጁባ ላይ የዶ/ር ጆን ጋራንግ ት/ቤት ከፍቻለሁ፡፡ በመንግሥት አመራር ላይ የሚገኙ ሚኒስትሮች ሥራቸውን ለማከናወን ምንም ዓይነት ግብዓት የላቸውም፤ የኤስ.ፒ.ኤል.ኤም. አመራር በደቡብ ሱዳን ውስጥ እያደረገ ያለው በነጻነት ትግሉ ወቅት (ለሞትንበት) ዓላማ አይደለም” ብለዋል፡፡
ሰኞ ዕለት ባልተለመደ መልኩ ሙሉ የወታደራዊ አለባበስ ተከትለው ንግግር ያደረጉት ሳልቫ ኪር መፈንቅለ መንግሥት መሞከሩን ካመኑ በኋላ “መንግሥት በጁባ ያለውን የደኅንነት ሁኔታ በቁጥጥሩ ሥር አድርጓል” ብለዋል፡፡ የከተማዋ አየርመንገድ እንዲሁም የቴሌቪዥን አገልግሎት ለበርካታ ሰዓታት ተቋርጦ እንደነበር ቢቢሲ ዘግቧል፡፡
ሁኔታው ጋብ እንዳለ በባለሥልጣኖቻቸው ታጅበው ወደ ቴሌቪዥን መስኮት ብቅ ያሉት የጦሩ ዋና አዛዥና የፓርቲው ዋና ሊቀመንበር ሳልቫ ኪር “መፈንቅለ መንግሥት ሙከራ” መደረጉንና የቀድሞ ምክትል ፕሬዚዳንት ዶ/ር ማቻር ደጋፊ የሆኑ ወታደሮች ድርጊቱን መፈጸማቸውን በመግለጽ መንግሥታቸውና ጦሩ ሁኔታውን በቁጥጥር ሥር ማድረጉን ተናግረዋል፡፡ በመቀጠልም “ይህ ዓይነቱ ድርጊት አዲስ በተወለደችው አገራችን እንዲቀጥል ፈጽሞ አልፈቅድም፤ አልታገስም፡፡ ይህንን የወንጀል ተግባር በጥብቅ አወግዘዋለሁ” በማለት ድርጊቱን የፈጸሙትን ሁሉ ለፍርድ እንደሚቀርቧቸው ቃል ገብተዋል፡፡ ከሰኞ ጀምሮም ከጸሐይ ግባት እስከ ማለዳ ድረስ የሰዓት እላፊ አውጀዋል፡፡
ዶ/ር ባርናባ ማሪያል ቤንጃሚን
ዶ/ር ባርናባ ማሪያል ቤንጃሚን
በቅርቡ ወደ ሥልጣን የመጡትና ሰሞኑን በአሜሪካ ጉብኝት ላይ የነበሩት የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር የተወሰኑ ወታደሮች በዋና ከተማዋ የሚገኝ የጦር መሣሪያ ማከማቻ ላይ ጥቃት መሰንዘራቸውንና በአሁኑ ወቅት የተወሰኑ ፖለቲከኞች በቁጥር ሥር መዋላቸውን ለአሶሺየትድ ፕሬስ ተናግረዋል፡፡
በአሁኑ ወቅት ዶ/ር ማቻር በቁጥጥር ሥር ውለዋል እየተባለ የሚነገር ቢሆንም እስካሁን ያሉበት ቦታ አልታወቀም፡፡ ቃል አቀባያቸው ግን በቁጥጥር ሥር እንዳልዋሉና በሰላም እንደሚገኙ መናገራቸውን ቢቢሲ ዘግቧል፡፡
ጎልጉል የድረገጽ ጋዜጣ ወደ ደቡብ ሱዳን ጁባ በመደወል የተለያዩ ምንጮችን ለማነጋገር የሞከረ ሲሆን የኃይል ሚዛኑ ወዴት እንዳጋደለ በተጣራ ሁኔታ ለማወቅ እንደማይቻል ተረድቷል፡፡ ፍጥጫውና በጎሣ መካከል ያለው ውጥረት እንደቀጠለ ለመረዳትም ችሏል፡፡
ደቡብ ሱዳንን ነጻ ለማውጣት ሲታገልና በመሥራቹ ኮ/ል ዶ/ር ጆን ጋራንግ ይመራ የነበረውን የነጻ አውጪ ግንባር የቀድሞው ኢትዮጵያ ፕሬዚዳንት መንግሥቱ ኃይለማርያምና አገዛዛቸው ይደግፍ እንደነበር ይታወሳል፡፡ በአንጻሩም እስላማዊው የሰሜን ሱዳን አገዛዝ ለሻዕቢና ለወያኔ የማያቋርጥ ዕገዛ በማድረግ ወደሥልጣን እንዲመጡ ትልቅ ሚና መጫወቱ ይታወቃል፡፡ ደቡብ ሱዳን ነጻ ከወጣች በኋላ ህወሃት/ኢህአዴግ “አዲስ አገር ለመገንባት” በሚል የደቡብ ሱዳንን ቴሌኮሙኒኬሽን፣ ደኅንነት፣ ፖሊስ፣ ኢኮኖሚ፣ ወዘተ በለመደው የተለያየ መረብ መቆጣጠሩን መረጃዎች ይጠቁማሉ፡፡
ይህ ዜና እሰከተጠናቀረበት ጊዜ ድረስ ሰኞ የተካሄደውን መፈንቅለ መንግሥት ሙከራ አስመልክቶ በደቡብ ሱዳን ውስጥ ካለው “ረዘም ያለ እጅ” አኳያ ህወሃት/ኢህአዴግ ምንም አልተነፈሰም፡፡ በሌላ በኩል ይህ የመፈንቀለ መንግሥት ሙከራ ከመደረጉ አንድ ቀን በፊት በአሜሪካ በጉብኝት ላይ ይገኙ የነበሩት የደቡብ ሱዳንን ውጭ ሚ/ር ዶ/ር ባርናባ ማሪያል ቤንጃሚን ዋሺንግተን ዲሲ  በማግኘት በአስቸኳይ የውስጥ ችግራቸውን በሰላማዊ መንገድ ካልፈቱ አደጋ እንደሚያጋጥማቸው፣ ችግሩ ከ21 በላይ ጎሣ ያለባት አገር ሊያምሳት እንደሚችል፣ የነጻነት ትግሉ ሲጀመርና ሲጠናቀቅ ዓላማው አምባገነናዊ ሥርዓት ለመፍጠር ባለመሆኑ ስህተታቸውን እንዲያርሙ አቶ ኦባንግ ሜቶ መክረው ነበር፡፡ ለአዲሲቷ ኢትዮጵያ የጋራ ንቅናቄ ዋና ዳይሬክተር አቶ ኦባንግ ሜቶ ከውጭ ጉዳይ ሚ/ሩ ጋር ስላደረጉት ውይይት የሰጡትን ዝርዝር ማብራሪያ እናቀርባለን፡፡

No comments:

Post a Comment