FREE ALL POLITICAL PRISONERS

FREE ALL POLITICAL PRISONERS
FREE ALL POLITICAL PRISONERS

Wednesday, January 8, 2014

በጅዳ እና አካባቢው የኢትዮጵያውያን ክራሞት


saudi ethio j


ካሳለፍነው ወር ጀምሮ ወደ ሃገራቸው እንዲገቡ በተደረገው ጥሪ እጃቸውን የሰጡ መኖሪያና የስራ ፈቃድ የነበራቸው ዜጎች ባቀረቡት ቅሬታ “ወደ ሃገር እንዳንገባ ተደርገን እየተጉላላን ነው!” ብለውኛል። በቀን በሚሰጠው ደረቅ ብስኩትና ጥራቱ ባልተጠበቀ ሩዝ መጎዳታቸውን የገለጹልኝ ሲሆን መፍትሔ የሚሰጠን የኢትዮጵያ መንግስትም ሆነ የሳውዲ መንግስት ተወካዮች አጥተው ቀን በጸሃይ ፣ ማታ በብርድና በቁር እንግልት እንደደረሰባቸው ተናግረዋል። ወደ ሃገር እንግባ ብለው በተደረገው ጥሪ እጃቸውን የሰጡት መኖሪያና የስራ ፈቃድ የነበራቸው ዜጎች እዚህ በጅዳ ሽሜሲ ብቻ ሳይሆን በሪያድ እስር ቤቶች እንዳሉ እንግልት እየደረሰብን ያሉ ነዋሪዎች ምሬታቸውን ገልጸውልኛል።
ሁከት በጅዳ የንጉስ አብድልአዚአዚዝ አውሮፕላን ማረፊያ-
ከጅዳ መካው የሽሜሲ መጠለያ ተነስተው ወደ ሃገር ለመሳፈር  በጅዳ የንጉስ አብድልአዚዝ አየር መንገድ ማረፊያ አውሮፕላን ማረፊያ የደረሱ ቁጥራቸው 1500 በላይ የሆኑ ኢትዮጵያውያን “የያዛችሁት እቃ ከሚፈቀደው ኪሎ በላይ ነው!” በሚል የተፈጠረው አለመግባባት  ማክሰኞ ከቀትር በኋላ መጠነኛ ሁከት ተቀስቅሶ እንደነበር እና ከሰአታት በኋላ መረጋጋቱን ተደጋጋሚ መረጃ ደርሶኛል።  የማክሰኞው ሁከት መነሻ የተመላሾችን የተከማቸ እቃ ለማየት ወደ ቦታው የደረሱትን የኢትዮጵያ አየር መንገድ ሃላፊ በቦታው መድረሳቸውን ተከትሎ ሲሆን በእንግልቱ የተበሳጩት ዜጎች ሁከት መቀስቀሳቸው በአይን እማኞች ተደጋጋሚ የስልክ ጥሪ  ለመረዳት ችያለሁ። የአይን እማኞች አክለውም ዜጎች ከሃላፊው ጋር ሊጋጩ ሲሉ በጸጥታ አስከባሪዎች ብርታት መትረፋቸውን ከቦታው  በሰአቱ የደረሰኝ መረጃ ያስረዳል። ግርግሩ ለሰአት ያህል የቀጠለ ቢሆንም በሰውና በንብረት ላይ ጉዳት አልደረሰም። ሁኔታውን ለማረጋጋት በቦታው የተገኙ ፈጥኖ ደራሽ ፖሊሶች ማረጋጋት ከፈጠሩ እና ሁኔታው ከተረጋጋ በኋላ የአየር መንገዱን ሃላፊ ለጥያቄ ወስደዋቸው እንደነበርና ሃላፊውን ለማስለቀቅ የጅዳ ቆንስል ሃላፊዎች እና ጅዳ የመጡት የሪያዱ አንባሳደር ወደ ቦታው በመንቀሳቀስ ከሰአታት በኋላ ሃላፊውን ይዘው ምሽት ላይ መመለሳቸውን ተጨባጭ መረጃ ደርሶኛል።saudi ethio j1
የሃላፊውን ለጥያቄ መቅረብ ተከትሎ በጉዳዩ ዙሪያ ያነጋገርኳቸው አንድ ውስጥ አዋቂ ሲናገሩ “  በአውሮፕላን አቅርቦት እጥረት እና እቃችን ሳንይዝ ወይም በአደራ ተቀብሎ ወደ ሃገር የሚያስተላልፍልን እስካላገኘን ወደ ሃገር አንገባም ያሉትን ዜጎች ጉዳይ እንዲመለከቱ በቆንስላው ጥያቄ ወደ አየር ማረፊያው ያቀኑት የአየር መንገዱ ሃላፊ ስለ ዜጎች መጉላላት መረጃ እንዳልነበራቸውና በቦታው ሲደርሱ ከሁከቱ ጋር ተያይዞ ግራ ተጋብተው ታይተዋል።” በማለት ሲያስረዱ በቆንሰሉና በአየር መንገዱ ሃላፊዎች መካከል የመረጃ ክፍተት መኖሩን ገላልጠው አጫውተውኛል።
ይህ በእንዲህ እንዳለ ከዚህ በፊት ከ40 ኪሎ በላይ እቃ መውሰድ አትችሉም የተባሉ ዜጎች እቃ ሃጅ ተርሚናል በሚባለው የአየር መንገዱ ማረፊያ ቦታ በብዛት ተዝረክርኮ እነወደሚገኝና የብዙዎች እቃ አድራሻ እንደሌለው የአይን እማኞች ገልጸውልኛል።  “አድራሻ ያለውን እቃም በሚመለከት የጅዳ ቆንስል ሰብስበን እንልከዋለን የሚል ቃል ከመስጠት ባለፈ ምንም አይነት ተጨባጭ እርምጃ እንዳልወሰዱም” በማለት እማኞች ገልጸውልኛል።
ከአስር ቀናት ያላነሰ እንግልታቸውን  በማስረዳት የተገፊ ድምጻቸውን እንዳሰማላቸው እንባቸውን እያዘሩና በብስጭት ያስረዱኝ ወገኖች በበኩላቸው “የአውሮፕላኑን ወጭ የሳውዲ መንግስት ከቻለ የኢትዮጵያ መንግስት እቃችን ይዘን እንድንገባ ለምን አላመቻቸልንም?  ሌላው ቢቀር መንግስት በሻንጣው መጫንና ለሳምንታት ብስኩት እየተሰጠንና በውሃና ምግብ ግዠ የያዝነውን ገንዘብ ስናጠፋና ስንሰቃይ በዚህ ካልረዳን ወገኖቼ ማለቱ አልገባንም! ዜጎች አይደልንም?” ሲሉ በመጠየቅ በተጎዳ ሰሜት ገልጸውልኛል። ከዚህ ጋር በተያያዘ አንድ ለጉዳዩ ቅርበት ያላቸው ወንድም እንደገለጹልኝ  ዜጎችን ማጓጓዙ እንደ በፊቱ በፍጥነት ባይከወንም አልፎ አልፎ መቶና ከመቶ በላይ ዜጎች በተገኘ የበረራ ክፍት ቦታ እየተላኩ መሆኑን በማስረዳት  ከቀን ወደ ቀን እየተባባሰ የመጣውን ይህንን ችግር የቆንስሉ ሰራተኞች በተደጋጋሚ ለቆንስል ሃላፊዎች ማሰማታቸውን በመግለጽ መፍትሔ ግን እስካሁን አለመሰጠቱን አክለው ገልጸውልኛል።
የካርጎ መዘጋት መዘዝና የነዋሪዎች ሮሮ-saudi ethio j2
የአየር መንገድ የካርጎ አገልግሎት ለወራት መሰናከል ተከትሎ በኢትዮጵያ አየር መንገድና በእቃ አቅራቢ የካርጎ ኤጀንቶች በደል ደረሰብን የሚሉ ዜጎች  ቅሬታ እያሰሙ ነው። ይህ ችግርም በነዋሪዎችና በካርጎ ኤጀንሲ ሰራተኞች መካከል ውዝግብ ማስከተሉ አልቀረም። የአየር መንገድ ወደ ኢትዮጵያ የሚደረገው ጉዞ ከስድስት ወራት በላይ ምክንያቱ ግልጽ ባልሆነ ምክንያት ከተዘጋ በኋላ ሰሞኑን ስራ መጀመሩ እየተሰማ ነው። ያም ሆኖ በጅዳ ዙሪያ ያሉ የካርጎ ኤጀንሲዎች “ወደ ኢትዮጵያ የካርጎ ግልጋሎት በተለያዩ አቅጣጫዎች እንሰጣለን!” በሚል ከፍተኛ ገንዘብ ለእቃው ማስጫኛ እየተቀበሉ እቃውን ቢረከቡም ከስድስት እሰከ አስር ወራት ለሚቆይ ጊዜ እቃውን በመጋዘ ቃላቸውን ጠብቀው እንዳላደረሱላቸው የመጫኛ ማስረጃቸውን እያሳዩ ቅሬታቸውን የገለጹልኝ በርካታ ዎች ናቸው። የሳውዲ ውጡ ህግ ከተነገረ ጀምሮና ከዚያም ወዲህ በተሰጠው የሰባት ወር የምህረት ጊዜ ጠቃሚ የሚሏቸውን ጥሪት እቃቸውን ለካርጎ ቢያስረክቡም አንድም በካርጎው መዘጋት በተጓዳኝ በካርጎ ኤጀንሲዎች ለአንድ ኪሎ እስከ 10 ሪያል በመክፈል እቃቸውን ቢያስገቡም እቃቸውን ደህንነት በማያውቁበት ደረጃ በንብረታቸው ላይ ብክነት እንዳስከተለባቸው እያዘኑ ሮሯቸውን አጫውተውኛል።
በጀዛን የዜጎች እንቢታ እና የህግ ታሳሪዎች ሮሮ -
በጀዛን “ወደ ሃገር እንግባ!” የሚሉ ነዋሪዎችን ጥሪ ተከትሎ የመጓጓዣ ሰነድ ለመስራት የጅዳ ቆንስል መስሪያ ቤት ተወካይ ዲፕሎማት ወደ ቦታው ያቀኑ ቢሆንም “ድረሱልን!” ሲሉ የነበሩ ዜጎች የውሃ ሽታ መሆናቸውን የኮሚቴውን በፊስ ቡክ መኖሩን የሚያሳውቀን የወገን ለወገንsaudi ethio j3የህዝብ ግንኙነት ፊስ ቡክ ጠቁሞናል።  በጀዛን የሚገኙ የህግ እስረኞችም በህግ ተይዘው ፍርድ ከተሰጣቸው በኋላ ለአመታት የሚጉላሉ እና በጥርጣሬ ተይዘው ፍርድ ቤት ያልቀረቡ ዜጎች የድረሱልን ጥሪ ዛሬም አላቆመም። “ትኩረቱ ሁሉ ወደ ሃገር ተመላሾች መሆኑ ብቻ ሳይሆን ድሮም ተረስተናል አሁንም ተረስተናል!” እያሉ ነው!  በጀዛን ዙሪያ ባሳለፍነው ሳምንት መረጃ ያቀበለን የወገን ለወገን ደራሽ የህዝብ ግንኙነቱ ገጽ ባስተላለፈው መረጃ ወደ ሃገር ቤት ለመሄድ ሰላላሳዩት ዜጎች ትኩረት በመስጠት የዜጎችን ወደ ሃላፊዎች ለመቅረብ እና ለመሸኘት ፍላጎት አለማሳየታቸውን ሲገልጽም “እነሆ ግዜው ደረሰና የሁለቱም ሃገር መንግስታት ሁኔታዎችን አስተካክለው በሰማት (አሻራ) የሚሰጡበት ቦታ ተበጅቶላቸው ከቆንስላ ፅ/ቤት ተወካይ በቆንስል አህመድ የሚመራ ቡድን ለዜጎቻችን እዚያው እንዲሰራላቸው በማሰብ ወደ ጂዛን ተጓዙ። አሁንም እዚያው ናቸው። ነገር ግን ነገሮች እንደታሰቡ እየሄዱ አይደለም። ታስቦላቸው የተሄደላቸው ወገኖች እየወጡ አይደለም የሚል አሳሳቢ ዜና ሰማን። አሁን ባለው ሁኔታ ወደ ማቆያ የሚገቡት ሰዎች በቀን መቶም እንደማይደርሱ ተገለፀልን። ከጂዳ ለዚህ ጉዳይ የተንቀሳቀሰው ልኡካን አሁንም ለማገልገል ይጠብቃል፡ ምንም የሚታይ ነገር ግን የለም። በጂዛን አጎራባች ወደ ሆኑ ከተሞችም ከአካባቢው ማህበረሰብ አምስት አምስት ሰዎች ለቅስቀሳ ተልከዋል። ቢሆንም ወገናችን ዜጎቻችን የሚወጡ አይነት አይደለም። በጣም ሚገርም ነው።” ይላል።  የህግ ታሳሪዎች በበኩላቸው የቆንስል ሃላፊዎችን አነጋግረዋቸው “ለእናንተ ጉዳይ አልመጣንም!” እንዳሏቸው ገልጸውልኛል። የህዝብ ግንኙነቱ ዜጎች ወደ ኋላ ስላፈገፈጉበት ጉዳይም ሆነ በደል ደረሰብን ስለሚሉ ህጋዊ ታራሚዎች የሰጠው መረጃ የለም ። በወገን ለወገን ደራሽ ኮሚቴ ለአንድ ወር በስራ አስፈጻሚነት የሰራሁ መሆኑ የሚታወስ ሲሆን ለቆንስል ሃላፊዎች ያቀረብኩት የዜጎች አቤቱታ እንዲታረም በተደጋጋሚ አሳስቤ የነዋሪውን አቤቱታ በጀርመን ራዲዮ በማቅረቤ በተወሰደ የ “በዲሲፕሊን!” እርምጃ ከኮሚቴው አባልነት በተጽዕኖ መነሳቴ ይታወሳል!
የውጭ ጉዳይ ልዑካን በጅዳ:-
በሳውዲ አረቢያ የሪያድ ኢንባሲ አምባሳደርን ጨምሮ ሶስት አባላትን የያዘው የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ቡድን ከሶስት ቀናት በፊት ጅዳ ገብተዋል። ልዑካኑ በእስካሁኑ ቆይታቸው የኢህአዴግ የድርጅት አባላትንና የጅዳ ቆንስል ሃላፊዎችን በዝግ ያነጋገሩ ሲሆን የውይይታቸው ትኩረት በመጡበት የዜጎችን ወደ ሃገር መግባት ጉዳይ የማፋጠን ስራ ይሁን በሌላ ተዛማጅ ጉዳይ የሚታወቅ ነገር የለም። የልዑካን ቡድኑsaudi ethio j4 አባላት በእስካሁን ቆይታቸው አደጋውን ለመከላከል በጅዳ ቆንስል ሃላፊዎች የተቋቋመውን የወገን ለወገን ደራሽ ጊዜያዊ ኮሚቴ እስካሁን ያላነጋገሩ መሆኑ ታውቋል። የልዑካኑ ቡድንን ኮሚቴውን አለማነጋገሩ ቅያሞት የገባቸው አንዳንድ አባላት በበኩላቸው የዜጎች እንግልት በቅንጅት ጉድለት እየተበራከተ በሄደበት በዚህ አጋጣሚ ኮሚቴው ንቁ ተሳትፎ ማድረግ ላልቻለበት ሁኔታ የቆንስሉ እና የአመራሩ ድክመት እንደሆነ በማስረዳት እያደር ለይስሙላ የተቋቋመ እንጅ ወገንን ለመርዳት ከመካዝን ያለውን ውሃ ለማደል እንኳ አቅም አጥቷል በሚል ከማህበረሰቡ ወቀሳ እየቀረበበት መሆኑን በግልጽ አጫውተውኛል።
በሳውዲ አረቢያ የሪያድ ኢንባሲ አምባሳደርን ጨምሮ ሶስት አባላትን የያዘው የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር ልዑክ በጅዳ ቆንስል የመንግስታችን ተወካዮች ለተጠቀሱትና በከባቢው ላሉ ችግሮች አፋጣኝ እርምጃ ካልወሰዱ አደጋውን መታደግ ከማንችልበት ደረጃ እንዳይደረስ የብዙ ነዋሪዎች ስጋት ሆኗል። የሳውዲ መንግስትን እና የኢትዮጵያ ኢንባሲና ቆንስል በማስታወቂያ ብቻ የተደገፈ ተደጋጋሚ ማስጠንቀቂያ ተከትሎ “ሰነድ የሌላችሁ ዜጎቸወ ከሳውዲ ውጡ!” በሚል ማስተላለፋቸው አይዘነጋም። ያም ሆኖ ነዋሪው በርካታ ያልተሟሉ ቅድመ ሁኔታዎችን በማቅረብ ለመውጣቱ ጥሪ “አሻፈረኝ!”  ያሉትን በሽዎች የሚቆጠሩ ነዋሪዎች ሮሮ እና ጥያቄ ለመስማትና አፋጣኝ የመፍየትሔ እርምጃ ለመውሰድም የመንግስት ሃላፊዎች ህዝባዊ አስቸኳይ ጥሪ በመጥራት መፍትሔ ያመላክቱ ዘንድ ደግሜ ደጋግሜ እመክራለሁ!
ዛሬም የመረጃ ክፍተቱ ይዘጋ፣ የምንናገረው ተጨባጭ መረጃ መሆኑን አጣርታችሁ መፍትሔ አፈላልጉ ስል ደጋግሜ “ጀሮ ያለው ይስማ!” እላለሁ !
ቸር ያሰማን!
ነቢዩ ሲራክ

No comments:

Post a Comment