FREE ALL POLITICAL PRISONERS

FREE ALL POLITICAL PRISONERS
FREE ALL POLITICAL PRISONERS

Thursday, February 20, 2014

መከላከያ የህዝብ ወይስ የህወሓት?

ከበላይ ገሰሰ

Addera5021@yahoo.com
ህወሓት ደርግን ማሸነፍ ማለት የኢትዮጵያ ህዝብን ማሸነፍ ማለት ነው ብሎ ስለሚያስብ ተግባሩ ሁሉ የንቀት፣ የማንቋሸሽና የማዋራድ ስራ እየፈፀመ ይገኛል። ሌላውን ትተን ጥቂት የሻዕቢያ ተላላኪ የሆኑትን የህወሓት መሪዎች የግንጠላ አጀንዳቸውን ይዘው በረሃ የሸፈቱበት ቀን ልክ የኢትዮጵያ ህዝብ በተለይም የትግራይ ህዝብ “ደደቢት ሂዳችሁ ታገሉሉኝ” ብሎ ወክሎ የላካቸው ይመስል “እኛ ታግለን ነፃ ስላወጣንህ እንደፈለግን እናደርጋሃለን” በማለት ዓይን አዉጣ በሆነ መንገድ ሰሞኑን “የካቲት 11 የትግራይ ህዝብ ዳግም ልደት ነው” እየተባለ በመከላኪያ ሰራዊት ታጅቦ በመከበር ላይ ስለሚገኘው የህወሓት አስቂኝ፣ አስገራሚና አሳዛኝ ድራማ የሚከተሉትን ጥቂት ነጥቦችን በአጭሩ እንመልከት።Ethiopian troops belongs to the ruling party TPLF/EPRDF
የህወሓት ድራማ ቁጥር 1.
የህወሓት መሪዎች እናስተዳድራለን የሚሉት 90 ሚሊዮን የኢ/ያ ህዝብ ነው እየገዙ ያሉት። ከፍተኛ ባለስልጣናቱን ጨምሮ ካድሬዎቻቸው፣ አባላቶቻቸውና ደጋፊዎቻቸው በቀጥታም ሆነ በስውር እየጋጡ ያሉት የኢትዮጵያ ህዝብ ሀብት ነው። የገጠሩን ትተን በሀሪትዋ ዋና ዋና ከተሞች ቁልፍ ቦታዎችን በመያዝ 90 ከመቶ የትግራይ ባለሀብቶች የቢዝነስ እንቅስቃሴያቸውን የሚያካሂዱትና ባለቤት የሆኑት በሌሎች ክልሎች ነው። በአጠቃላይ የሀገሪትዋ ሀብት በተለያየ መልኩ የተቆጣጠሩት የህወሓት መሪዎች፣ ካድሬዎችና አጃቢዎቻቸው ናቸው። በመሆኑም በመሬት ላይ ያለው ህዝቡ የሚያውቀው ሐቅ ይህ ሆኖ ሳለ እነሱ የሚሉን ግን “የትግራይ ህዝብ ነፃ አውጪ ነን” ነው። ልብ በሉ!! ስልጣን ላይ ያሉት እነሱ። ሀገሪቱን የተቆጣጠሩት እነሱ። ሀገሪትዋን እየዘረፉ ያሉት እነሱ። ነገር ግን ነፃ እናወጣለን የሚሉት ህዝብ አንድ ክልል ነው። ታዲያ!! ቆም ብሎ ላሰበውና ላስተዋለው ሰው ይህ መንግስት ከኛ አብራክ የወጣ ኢትዮጵያዊ መንግስት ነው ለማለት ያስችላልን?።
የህወሓት ድራማ ቁጥር 2.
የትግራይ ህዝብ ኢትዮጵያን ከነባንዴራዋ ከፈጠሩት የታሪክ አስኳል አንዱ መሆኑን ዋቢ የሚያስፈልገው አይደለም። ቢያንስ አንድ ሶስተኛው የትግራይ ህዝብ በመላ ሀገሪቱ ከሌላው ወገኑ ጋር ተሳስሮ፣ ሀብት አፍርቶ፣ ተጋብቶና ተሰባጥሮ በነፃነት ይኖራል። በኢትዮጵያ የትግራይ ተወላጅ የሌለበት መንደር የለም ቢባል ማጋነን አይሆንም። ሲኖርም እንደ መጤ ወይም እንደ ስደተኛ አይደለም ራሱም ሆነ ሌላው ሰው የሚያስበው “ሀገሬ!! መብቴ!! ነው” በማለት በልበ ሙሉነትና
በመተማመን ይኖራል። በሌላ አነጋገር ህዝቡ ለዘመናት በጋራ የኖሮው በመልካም ጉርብትና ብቻ ሳይሆን በራሱ ፈቃደኝነት በፍቅር፣ በወንድማማችነት፣ በመከባበርና በመተማመን ላይ የተመሰረተ ባንድ እናት ሀገር ጥላ ስር ተቃቅፎ ባህሪያዊ ዝምድናን በመመስረት ነው። ዛሬ 90 ሚሊዮን የኢትዮጵያ ህዝብ የጋራ እሴት አለን የምንለውም ይኸው ነው። ታዲያ!! ይህ ከሆነ ሐቁ የትግራይ ህዝብ ነፃ የሚወጣው ከማን ነው? ነፃ የሚያወጣውስ ማን ነው? እውነት ለራሱ ነፃ
ያልወጣና የሻዕቢያ ሎሌ የሆነውን ዘራፊና ከሃዲ ድርጅት የትግራይ ነፃ አውጪ ነኝ ማለቱ ለታላቁ ህዝብ ውርደትና ሀፍረት አይሆንም ወይ? ለመሆኑ ባድመን ጨምሮ የትግራይን መሬትና ህዝብ የተደፈረው በሀይለ ስላሴ ግዜ ነውን? በሀይለ ስላሴ ስርዓት በትግራይ ምድር ሰው እንደ አራዊት በአደባባይ ተደብድቦስ ያውቃልን? ሀገርን እያፈረሱ ነፃ አውጪ ነኝ ማለቱስ የትግራይ ህዝብ ፍላጎትና ጥቅም መጠበቅ ማለት ነውን? በኢትዮጵያ ደረጃ ትክክለኛ ዲሞክራሲያዊ ስርዓትና ፍትሕ ሳይረገጋጥ በትግራይ ብቻ ትክክለኛ ለውጥ ሊረጋገጥ ይችላል ወይ? ህወሓት የትግራይ ህዝብ ነፃ አውጪና መድህን ቢሆን ኖሮ ህዝቡን ከሻዕቢያ ወረራ ያዳነው ማን ነው? እናንተ የትግራይ ነፃ አውጪ ነን ትላላችሁ ነገር ግን ሌሎች ከሰማንያ በላይ ብሄር ብሄረሰቦችስ ማን ነፃ ያውጣቸው?
አዎ!! ይህ ዓይነቱ ድራማና ጥያቄ ላለፉት ሶስት ዓሰርተ ዓመታት እንቆቁልሽ ሆኖ የቆየና ገና በሚሊዮን ኢትዮጵያውያን ዘንድ በሆድ ውስጥ ታምቆ አንድ ቀን ሊፈነዳ የተቃረበ እሳተ ጎመራ መሆኑን አልጠራጠረም። ከላይ ለተጠቀሱት ጥያቄዎች ህወሓቶች መልስ ይሰጡኛል ብዬም አልጠብቅም። “ከኛ በላይ ወንድ የለም። ተልባ ቢንጫጫ በአንድ መውቀጫ። እኛ እንብላ እነሱ ይጩኹ። እኛ እንግዛ እነሱ ያልቅሱ። ያበጠው ይፈንዳ!! ብለው በንፁኃን ደም የሰከሩ፣ በፍቅረ ንዋይ ዓይናቸው የታወሩ፣ በቂም በቀል አእምሮዋቸው የደነዘዙና በጠባብነት ሻማ የተሸበቡ ካድሬዎችና መሪዎች ዛሬ ዊስኪ እየተራጩና ጮማ እየቆረጡ የልደት በዓላቸውን ቢያከብሩ ብዙም አዲስ ነገር አይደለም።
የህወሓት ድራማ ቁጥር 3.
የህወሓት መሪዎች ህዝቡን ለማታለል ከሚሰሩት ድራማ አንዱ በሀገሪትዋ ላይ ሕገ መንግስት፣ መድብለ ፓርቲ ስርዓት፣ ነፃ የመከላኪያ ኃይልና ፍትሕ መኖሩን ለማስረዳት ይሞክራሉ። እነዚህ መሰረታዊ መርሆዎች ለኢትዮጵያ ህዝብ ሳይሆን የአንድ ድርጅት ሞኖፓላዊ ስልጣን ለመጠበቅና ለማገልግል ሲባል ሌላ ቀርቶ ሰሞኑን የህወሓት መሪዎች ልደት ለማከበር እንዴት እንደሚጠቀሙበት ከሚከተሉት ጭብጦች መረዳት ይቻላል።
  • ሕገ መንግስት አለ ይሉናል። ነገር ግን በሕገ መንግስቱ የሰፈሩ መብቶች ሌላ ዜጋ እንዳይጠቀምባቸው በተግባር ተገድበዋል። ሕገ መንግስቱ በነፃ መደራጀት ይፈቅዳል በነፃ መንቀሳቀስ ግን በሽብርተኝነት አዋጅ ተገድበዋል። ሕገ መንግስቱ የመናገርና የመፃፍ ነፃነት ይፈቅዳል ነገር ግን በህዝብ ሀብት የሚተዳደሩ የብዙሓን መገናኛ አውታሮች በአንድ ድርጅት በሞኖፓል ተይዟል። የፃፈ ወይም የተናገረ ዜጋ ሁሉ ሰፈሩ ቃሊቲ ወህኒ ቤት ሆኗል። ሕገ መንግስቱ ምርጫ ይፈቅዳል ነገር ግን የምርጫው መወዳደሪያ ሜዳ ተዘግቷል። በአጠቃላይ አንድ ድርጅት ራሱ ሕግ አውጪ፣ ራሱ ሕግ ፈፃሚ፣ ራሱ ገዳይ፣ ራሱ ከሳሽ፣ ራሱ ዳኛ የሆነበት ስርዓት ነው ያለው።
  • በሀሪቱ መድብለ ፓርቲ ስርዓት አለ ይሉናል። ነገር ግን አውራ ፓርቲ ወይም ልማታዊ መንግስት በሚል ፓሊሲ ትርጉም ያለው ተቀናቃኝ የፓለቲካ ድርጅት እንዳይበቅል በሩ ተዘግቷል። በሕገ መንግስቱ ላይ አንድ ፓርቲ ከሌሎቹ ፓርቲዎች የበለጠ መብት እንዲኖረው ወይም በአውራ ፓርቲነት የሚፈርጅ አንቀፅ የለም። ነገር ግን ህወሓት ከሌሎቹ የተለየ መብት ያለው የበኩር ልጅ በመሆን የሀገሪትዋን ገንዘባዊ፣ ተቋማዊ፣ ማተሪያላዊና ሰብኣዊ ሀብት በቀጥታም ሆነ በተለያየ መልክ በመጠቀም በዓሉን ሲያከብር እናያለን። ሌላው ሀገር በቀል ኢትዮጵያዊ ድርጅት ያልተሰጠው መብት ለህወሓት ግን ከደደቢት በረሃ በመምጣቱና የመከላኪያ ሰራዊት ከጎኑ ስላሰለፈ ብቻ ሀገርንና ህዝብን እንደፈለገ እንዲንድ፣ እንዲዘርፍ፣ እንዲገድልና እንዲያፍን መብት ተሰጥቶታል።
  • መከላኪያ ሰራዊት ከፓለቲካ ነፃ ነው፣ የሕገ መንግስት ዘብ ነው፣ የህዝብ ሰራዊት ነው፣ የልማት ሰራዊት ነው፣ ወዘተ ይሉናል። ነገር ግን በተግባር ሲታይ የአንድ ድርጅት ህወሓት ጠበቃና አጃቢ እንጂ የህዝብ ወገንና መድህን ሲሆን አላየንም። ለምሳሌ ሰሞኑን እንዳየነው ሁሉ የመከላኪያ ሰራዊት ሳምንት በሚል ሽፋኝ እየተካሄደ ያለው ሰልፍና ኤግዚቪሽን ሆን ተብሎ ከህወሓት ልደት ጋር የተያያዘ እንዲሆን ተደርጓል።
“አትረፍ ያለው በሬ ቆዳውን ለከበሮ ይውላል እንዲሉ” የትግራይ ህዝብ ላለፉት አርባ ዓመታት ያሳለፈውን መከራና ስቃይ እንዳይበቃው ዛሬም ከጀርባው አልወረዱም። እንደ ህዝብ መከበር ሲገባው በአንፃሩ ህወሓት ከሕግ በላይ በመሆን አማራጭ መንገዶችን በመዝጋት የአንድ ድርጅት አገልጋይ ሆኖ እንዲኖር ጥረት በማድረግ ላይ ይገኛል።
ስለዚህ ኢትዮጵያውያን በተለይም የትግራይ ወንድሞችና እህቶች በሙሉ!! ድርጅትና ግለ መሪዎች አላፊ ናቸው። ህዝብና ሀገር ግን ነባሪ መሆናቸውን አምነን ህዝባችንን ከጅብ ምንጋጋ እንዲላቀቅ እጅ ለእጅ ተያይዘን መነሳት አለብን እላለሁ። ዋስትናችን፣ መድህናችንና ጋሻችን አንድ ድርጅት ሳይሆን ታላቁ የኢትዮጵያ ህዝብ መሆኑን አማራጭ የሌለው የህልውና ጥያቄ ነው። ስለዚህ አንድ ድርጅት ወይም ግለ ሰቦች መምረጥ እንችላለን ነገር ግን አንዲት እናት ሀገር ነው ያለችን ሌላ አማራጭ የለንም።
http://ecadforum.com/Amharic/archives/11063/

No comments:

Post a Comment