FREE ALL POLITICAL PRISONERS

FREE ALL POLITICAL PRISONERS
FREE ALL POLITICAL PRISONERS

Thursday, April 17, 2014

“ዘላለማዊነት ለገንዳዎች!! ዘላለማዊ ክብር ለገንዳዎች”

የድህነት ራዳር እንደ ድህነት "ክፉ" ነው

hailemariam qurt


የገንዳዎች የደራጃ መዳቢ ድርጅት ሊቋቋም ይገባል። ገንዳዎች የኑሮ መሰረት የሆኑላቸው እየበረከቱ ስለሆነ በደረጃ መከፋፈል አለባቸው። የአጠቃቀማቸውም መመሪያም በግልጽ ሊቀመጥ ይገባል። የደረጃዎች መዳቢ ድርጅት ቢያንስ በገንዳዎች ውስጥ ስለሚጣሉ ቆሻሻዎች መመሪያ በማውጣት የሚበሉ ነገሮች ከሌሎች አይነት ቆሻሻዎች ተለይተው እንዲጣሉ ማዘዝ አለበት። ከሸራተንና ከቤተ መንግስት የሚወጡ የምግብ ትራፊዎች ተጠቃሚ ጋር ሳይደርሱ ፓስተር እንዲመረመሩ የሚያዝ መመሪያ ቢወጣም መልካም ነው። ቀጭኑ ዘ-ቄራ ማሳሰቢያ አለው።
ገንዳዎች የኢህአዴግን ስራና ሃላፊነት በመወጣት ለድህነት ሰለባዎች “የላቀ” አስተዋጽኦ እያበረከቱ ስለሆነ የሽልማት ኮሚቴ ይቋቋምላቸው። ገንዳዎች በሚወጣላቸው ደረጃ መሰረት ተለይተው ይሸለሙ። የጥሬ ስጋ ተጠቃሚዎችና አንዳንድ አገልግሎት ሰጪ ተቋማት ሽልማቱን ለግል ውዳሴ እንዳይጠቀሙበት አቶ ደመቀ መኮንን የሚመሩት ተቆጣጣሪ ይመደብ። ይህ የእለቱ ጥቆማዬ ነው። ገንዳዎች ባይኖሩ ኖሮ ምን ይኮን ነበር? “ዘላለማዊነት ለገንዳዎች!! ዘላለማዊ ክብር ለገንዳዎች!!”
gendaድህነት ክፉ ነው። ድህነት ስል የሚያምረውን ድህነት አይደለም። “የሚያምር ድህነት ምንድነው?” ለምትሉ መልስ የለኝም። ስለምንግባባ!! እኔ “ክፉ” የምለው መረን የወጣውን ድህነት ነው። ገደብ የለቀቀውን ማለቴ ነው። እረፍት ነስቶ ሞራል የሚያንኮታኩተውን ነው። ሞራል አድቅቆና ሰውነትን አዝሎ አንገት የሚሰብረውን ነው። መጥፎ ጠረንን በመጠየፍ አፍንጫን ጠቅጥቆ ገንዳ ውስጥ ለጉርስ የሚያስዋኘውን አይነት ድህነት ነው። እናት ልጇን ለወሲብ ገበያ አበረታታ እንደትልክ የሚያስገድዳትን ድህነት ነው። የወለዱ የከበዱ አባትና እናትን በስተርጅና ጎዳና ላይ የሚጥለውን ድሀነት ነው …
ብዙ ጉድ፣ ብዙ ዓይነት ጓዳ አለ። መልከ ብዙ ችግር፣ መልከ ብዙ ችጋር አለ። የመከረኛዋ አገር ኢትዮጵያ ጎጆዎች ይቁጠሩት። የሚቦካ አጥታችሁ ቦሃቃ ለሰቀላችሁ፣ ሌማት ለደረቀባችሁ፣ አቁላልቶ መብላት ቅዠት ለሆነባችሁ፣ የእናት ጓዳ ለተዘጋባችሁ፣ መማሪያ ክፍል ውስጥ ርሃብ ለሚፈነግላችሁ ህጻናት፣ ጧሪ ለሌላችሁ የወግ እናትና አባቶች … ጠኔ በየጓዳው ለከነቸራችሁ … ለናንተ ሁሉ መልካም የፋሲካ በዓል ይሁንላችሁ። ፋሲካ … አሁን ለናንተም ፋሲካ ሊሆን ነው። ያስለቅሳል።
ቀጭኑ ዘ- ቄራ ነኝ። ዛሬ እጅግ ስሜቴ ተነክቷል። አንድ ነርስ ወዳጄ ያጫወተችኝ ትዝ አለኝና አልቅስ አልቅስ አለኝ። እሷ በምትሰራበት የግል የርዳታ ድርጅት ውስጥ የኤችአይቪ/ኤድስ ተጠቂዎች ለሆኑ በወር በወር የሚሰጥ ገንዘብ አለ /በነገራችን ላይ የርዳታ ድርጅት ራሱ ሌላ ቫይረስ አለበት/ ርዳታው የሚሰጠው ምርመራ እየተደረገ ነው። በምርመራው ቫይረሱ የሌለበት ሰው ርዳታ አይሰጠውም። “ቫይረሱ ስለሌለብዎ እንኳን ደስ አለዎ” ተብሎ ሲነገራቸው የሚከፋቸው ብዙ ናቸው። አንዳንዶቹ “በዚህም ትለዩኛላችሁ፤ ርዳታ እንዳላገኝ ነው?” በማለት ይከራከሩ እንደነበር በተረበሸ የሃዘን ስሜት ታወጋኝ ነበር። መጨረሻ ላይ በዚህ ሁኔታ መቀጠል አቅቷት ስራ ቀየረች።
በወር 200 ብር ለመቀበል ድህነት የሚያስመኘውን አስቡት፤ የት እንደደረስን ገምቱ። ድህነት “ዛሬን ብቻ ይለፈኝ” የሚባልበት ደረጃ ደርሰናል። ይህ ደረጃ አደገኛ ነው። ዛሬን ብቻ ስለማለፍ የሚያስቡ በፍጥነት እየበረከቱ ነው። ዛሬን ማለፍ ብቻ አላማቸው ያደረጉ ሲበዙ ሁሉም ነገር “በዛሬ ይባዛል” ሁሉም ለራሱ የ”ጎበዝ አለቃ” ይሆናል። የጎበዝ አለቆች … የዚያኑ ያህል ለልጅ ልጅ የሚያካብቱ ጥቂቶች አሉ። እነዚህ ሃብታቸው ሞልቶ የገነፈለባቸውና ጥጋብ ልብ የነሳቸው የሚያደርጋቸውን አሳጥቷቸዋል። እነሱ ምድሪቱ ላይ፣ ጥጋብ ደግሞ እነሱ ላይ ህንጻ ገንብተዋል። የሰበሰቡት ሃብት፣ የገነቡትና የተገነባባቸው ህንጻ በድህነት ራዳር ውስጥ ናቸው። የድህነት ራዳር እንደ ራሱ እንደ ድህነት “ክፉ” ነው። አይምሬ ነው … ድህነት ሲያመር አመረረ ነው። አገርን ሁሉ “በዛሬን ልደር” ያጣፋል።
የማጣፋት ጨዋታ አደገኛ ነው። የጎበዝ አለቆች ሲያብቡ ጨዋታ ይፈርሳል። አዲስ ጨዋታ ይጀመራል። ህግ አልባ ጨዋታዎች ይጀመራሉ። በነገራችን ላይ አሁንም ህግ አልባ ጨዋታ የሚጫወቱ አሉ። ከቻሉ ኢትዮጵያን ከህዝቧ ነጥለው በፓራሹት ወደ ሌላ ስፍራ እንዲያዘዋውሯት የተፈቀደላቸው አሉ። እነዚህ የጎበዝ አለቆች የተበደሩትን ብር እየረጩ ይዘፈንላቸዋል። ይሞካሻሉ። የፈለጉትን አጥር ዘለው የተከበረ አንሶላና ብርድ ልብስ አስገድደው ይከፍታሉ። የህሊናቸው ጠረን በሰሩት ግፍ መጠን ሸቷል። ስብእናቸው ቀርንቷል። የሰውነት ማዕረግ የላቸውም። በእርም ሃብት ህሊናቸው ተጋርዶ “ሰው እኩል ይሆናል ብር” በሚል የወደቀ የሂሳብ ቀመር ውስጥ ተነክረዋል። የድህነት ራዳር እነዚህንም ይከታተላቸዋል።Circus therapy for young homeless
“የራበው ሰው የአፍ ጠረኑ ይቀይራል” የሚል ጓደኛ ነበረኝ። ሰው የአፉ ጠረን የሚቀየረው ጨጓራው የሚፈጨው አጥቶ ሲጨስ እንደሆነ ሁሌ ይናገራል። ለጋስ ነበር። ሰው መርዳት ያስደስተዋል። ሆን ብሎ የሚጎበኛቸው ድሃ እናትና አባቶች ነበሩት። ይኸው ባልደረባዬ “ከራበው ላይ የሚዘርፉ ደግሞ ህሊናቸው ይገማል” በማለት ይጠየፋቸዋል። ዛሬ እሱም ትዝ አለኝ። ነብሱን ይማረው!!
አዎ!! በቀን ሶስቴ እንደሚበላ የተወተወተ ህዝብ በወጉ አንዴም መጉረስ ተስኖታል። ከ22 ዓመት በኋላም ስለ ጉርስ ሳይሆን ስለ “ውርስ” ነው የምንሰማው። በቂም በቀል ዜጎች ከስራ እንዲባረሩ የወሰነ “ውርስ” ለማስተዋወቅ፣ ለመዘከር፣ መታሰቢያውን ለመትከል በጀት ከድሃ ጉሮሮ እየተነጠቀ ይፈስለታል። በቁም ድህነት ነቃቅሎ ያፈረሳቸው እያሉ ለሞተው ቂመኛ መንፈስ ግብር ይገባል። አዶ ከርቤ ይባላል። የኢትዮጵያን ታሪካዊ ፋይዳና ሚስጥራዊ የባህር በር ላዘጋ መንፈስ ስግደት … ቀጭኑ ጥያቄ አለው። ጥያቄው አንድ ነው። ከሙት መንፈስና ከነዋሪ የቱ ይብሳል። ለየቱ መገበር ይቀላል። የቱ ተግባር ህሊናን ያሸታል ወይም ያለመልማል?
አንድ ሳሪስ አዲስ ጎማ ሀዲዱ አካባቢ ያገኘሁት እብድ ትዝ አለኝ። ስለመቆም ይለፈልፋል። “የቆሙ የሚመስላቸው ብዙ ናቸው፣ ግን አልቆሙም። ያልቆሙት መቆም ስለማይፈልጉ አይደለም …” በፍጥነት ይናገራል። ይደጋግማል። “… መቆም እንዴት እንደሆነ ስላላወቁ ነው። መቆም የራሱ ምስጢር አለው። አንተ ግን ተደገፍ፣ ተደጋገፍ፣ ብቻህን አትቁም፣ እንኳን ሰው እንጨት ይደግፋል። ክራንች ይደግፋል። ብቻህን ከምትቆም …” ይናገራል። የስብከት አይነት ነው። ይሰብካል። “አንተ ግለኛ ሁሉ። ሆዳም ሁሉ። ስማ” እያለ ይጮሃል። ስለመብላት ሲናገር “የሞተ ነገር የምትበሉ ሁሉ” ይላል። ለምን እንደዚህ እንደሚል በወቅቱ አልገባኝም። ግን ታላቅ ነገር እንደተናገረ ሁሌም አስባለሁ። አዎ!! መደገፍ። እንኳን ህዝብ እንጨትም ምርኩዝ ይሆናል። ኢህአዴግ ድጋፉ ጠብ መንጃ ነው። ታንክና አጋዚ ነው። ፌደራል ሰራዊትና ስለላው ነው። ለዚህ ሁሉ ብር ይፈሳል። በህዝብ ተደግፎ ገንዘብ በመቆጠብ ጠኔ ለሚደፋቸው ማዋሉ አይቀልም? የህሊና መሽተትና መዋብ እዚህ ጋር ይነሳሉ። ድህነትም የሚያቅራራው እዚህ ወሳኝ ነጥብ ላይ ነው። ክፉ ነዋ!! ሲነሳበት ራዳሩን ሲያበራው … ዋ! ያኔ!! ሳይቃጠል በቅጠል አሉ!!
ስለ ጡረተኞች አስባችሁ ታውቃላችሁ። እንደው ለብቻቸው ገበያ የሚገበዩበት ስፍራ አላቸው? የነሱና የቤተሰቦቻቸው ፍላጎት በቀዶ ጥገና ተኮላሽቷል? አንዴ አንዲት አሮጊት እናት እንዲህ አጫውተውኝ ነበር። በደርግ ስርዓት አንድ ያከራዩት የጭቃ ቤት “ትርፍ ሃብት” ተብሎ ተወሰደባቸው። አበል 7 ብር ከሃምሳ አላቸው። ኢህአዴግ ገብቶ 18 ዓመት እስኪሞላው ገቢያቸው ያቺው 7 ብር ከሃምሳ ነበረች። በየወሩ ደሞዝ ለመቀበል ቀበሌ ሄደው ይሰለፋሉ። ደሞዝ!! እኚህ እናት ብዙ ብለውኛል። መፈጠርን የሚያስጠላ የድህትን ወለል አሳይተውኛል። ለነብስ ያሉ እየረጠቧቸው እንጂ እሳቸው የአንድ ጎልማሳ ዘመን ሸምተው አያውቁም። መለስ እኚህን አዛውንት ጨምሮ ነበር “በቀን ሶስቴ አስበላችኋላሁ /ይቅርታ አበላችኋለሁ/” ሲል የዋሹት። የቂም ፖለቲካ ምህንድስናው ወጥሮ ይዟቸው እንደሁ አላውቅም። እንደወጋችን እዚህ ላይ ነብስ ይማር ማለት አይቻለኝም። መለስን ነብስ ይማር ካልኩ፣ ኑሮ አድቅቆ ለሞት ያስረከባቸውን እናት ምን ልላቸው ነው? ከፈለጋችሁ ታዘቡኝ!!
ጅቡቲ እጇን አጣጥፋ ትበላለች። ቀን የጅቡቲ ጭሰኛ አደረገን። ቂምና የበታችነት መንፈስ ለጅቡቲ አምበረከከን። ጅቡቲ የለፋንበትን እየሰበሰበች ትገምጣለች። “እያንጓለለ” ይላል ይህ ነው። የተንኮል ፖለቲካ!! ጅቡቲን የሚያስፈስክ ሲስተም … አሁን ፋሲካ ነው። ለክርስትና ሃይማኖት ተከታዮች ሁሉ ፋሲካ ታላቅ በዓል ነው። ከላይ በመግቢያዬ ለጠቀስኳችሁ ሁሉ ምን እንደምመኝ አላውቅም። የፋሲካው ጌታ መላ ይበላችሁ። ከፋሲካው ጌታ በላይ ጌቶች ፈጥራችሁ በውርስ አምልኮ ለታሰራችሁ፣ ህሊናችሁ ለሸተተ፣ ልቡናችሁ በትዕቢትና በጥጋብ ለተወጠረ የፋሲካው አምላክ ይርዳችሁ!! የሞተ/አርዶ ለመብላት ካሁኑ መደራጀት የጀመራችሁ ግራና ቀኙን እዩ። የድሆች ራዳር በስራ ላይ ነውና!! እስከዛው ግን “ዘላለማዊ ክብር ለገንዳዎች”… እስኪ እንረፍ። መልካም እረፍት!! ቀጭኑ ዘ – ቄራ!
http://www.goolgule.com/eternal-adoration-to-dumpsters/

No comments:

Post a Comment