FREE ALL POLITICAL PRISONERS

FREE ALL POLITICAL PRISONERS
FREE ALL POLITICAL PRISONERS

Sunday, September 15, 2013

ስምና ገመድ!!

(ደመቀ ከበደ - ከጣና ዳር)

rope-and-doro


በተለያዩ ምክንያቶች ለረጅም ጊዜ አቋርጠነው የነበረውን የግጥም ጨዋታ እንደገና ጀምረናል፡፡ ከዚህ በፊት እናደርገው እንደነበረው አንባቢያን ይህንን ግጥም አንብባችሁ አስተያየታችሁን በግጥም እንድትሰጡና ጨዋታውን እንድታደምቁት እንጋብዛለን፡፡ ለዛሬ የመረጥነውን ግጥም ከነፎቶግራፉ ያገኘነው ከደመቀ ከበደ የፌስቡክ ገጽ ላይ ነው፡፡ገጣሚ ደመቀ ከበደን ለግጥሙና ለፎቶው ምስጋናችንን እናቀርባለን፡፡

ስምና ገመድ!!

አዝማሪ እንዲህ አለ፤
“ሰው ሰበበኛ ነው – ምክንያት አያጣም
እንኳን ዝናብ ዘንቦ – ሲዳምን አይወጣም፤”
እኔ ግን እላለሁ፤
አተተ በተተ
ወዘተ ወዘተ
በሚል አርቲ ቡርቲ – ዕድሜ ከምንጨርስ
ህይወት ከምናጣ
ፋይዳ ላለው ነገር – ቁልቁለት እንውረድ
አቀበት እንውጣ፤
ያኔ
አላስወርድ ካለህ – ወይም አላስወጣ
ማሰሪያ ከሆነህ – አሊያም ጋሬጣ
ያኔ አይንህን አውጣ
ወይ ሆ! ብለህ ውጣ፤
ያለዚያ
ቀብድ በበላች ሀገር – በድህነት ቁና
ሀብታምነት ከንቱ – ዝነኝነት መና፤
ነው እንጂ ነውና
በስም የሚከብሩ
በስም የሚከስሩ
በስም የሚወጡ
በስም የሚወርዱ
በስም የሚያለቅሱ
በስም የሚያብሱ
በስም የሚጥሉ
በስም የሚያነሱ
በሞላባት አገር – በስም ለታጠረች
ስምህ ገመድህ ነች
ድንገት ታስርሀለች – ወይም ታንቅሃለች፤
‹‹ከስብስም ይሸታል!›› – ብላ እየተረተች
ስምህ ሁሉን ሆና
ወይ ትጥልሃለች – ወይ ታነሳሃለች፤
ስለዚህ
በስም ከፍታ ላይ – እላይ እንድትወጣ
ጫፉን እንድትረግጥ
ዘዴ ዘይድና – ወይ ገመዱን ፍታ
ወይ ገመዱን ቁረጥ!!
(ደመቀ ከበደ – ጣና ዳር)
ከዚህ በፊት ያቀረብናቸው የግጥም ጨዋታዎች ላይ ትሳተፉ የነበራችሁ ሁሉ በድጋሚ እንድትሳተፉ፤ አዲሶችም እንዲሁ በጨዋታው እንድትገቡ ታድማችኋል፡፡ ምናልባት የበፊቶቹ ጨዋታዎች ምን ይመስሉ ነበር የሚለውን ለመመልከት ከዚህ በፊት ያቀረብናቸውን እንደሚከተለው አቅርበናል፡፡ ርዕሶቹ ላይ በመጫን ማንበብ ይቻላል፡፡

No comments:

Post a Comment