FREE ALL POLITICAL PRISONERS

FREE ALL POLITICAL PRISONERS
FREE ALL POLITICAL PRISONERS

Thursday, September 26, 2013

“ወሲባዊ ጂሃድ (ጂሃድ አል-ኒቃ)” በሶሪያ!

ሳዑዲ ሞት የፈረደችባቸውን ወደ ሶሪያ አዝምታለች

tunisian girls


የቱኒዚያ ሴቶችና ልጃገረዶች በሶሪያ የአሳድን መንግሥት እየተፋለሙ ከሚገኙት እስላማዊ አማጺያን ጋር “ወሲባዊ ጂሃድ” በመፈጸም በጦርነቱ ላይ ተሳትፏቸውን እየገለጹ መሆናቸው ተነገረ፡፡ በሌላ በኩል በዚሁ ጦርነት ላይ በሳውዲ አረቢያ የሞት ፍርድ የተበየነባቸው ወንጀለኞች እንዲሳተፉ እየተላኩ መሆናቸው ተረጋገጠ፡፡
በያዝነው የመስከረም ወር መጀመሪያ አካባቢ የቱኒዚያው የአገር ውስጥ ሚኒስትር ሎትፊ ቢን ጄዱ በአገሪቱ ፓርላማ ፊት ቀርበው እንደተናገሩት በጦርነቱ ከፍተኛ መስዋዕትነት እየከፈሉ ለሚገኙት ተዋጊዎች ማደፋፈሪያ እንዲሆንና በትግሉ የነርሱንም ድርሻ ለመወጣት የቱኒዚያ ሴቶችና ልጃገረዶች ራሳቸውን በ“ወሲባዊ ጂሃድ” በመስጠት ላይ እንደሚገኙ ተናግረዋል፡፡
ሚኒስትር ሎትፊ ቢን ጄዱ (ፎቶ: አልጃዚራ)
ሚኒስትር ሎትፊ ቢን ጄዱ (ፎቶ: አልጃዚራ)
በአረቡ ዓለም በሚገኙ የዜና ማሰራጫዎች በሰፊው የተዘገበው ይህ ዜና እንደሚያስረዳው ሚኒስትሩ ጉዳዩ አሳሳቢ ደረጃ ላይ መድረሱን ጠቁመዋል፡፡ “እነዚህ ሴቶች” አሉ ሚኒስትር ቢን ጄዱ “እነዚህ ሴቶች (ሶሪያ በሚቆዩበት ጊዜ) ከ20፣ 30፣ 100” አማጺያን ጋር በመተኛት የወሲብ “አገልግሎት” ይፈጽማሉ፡፡  “ወሲባዊ ግንኙነቱንም የሚያደርጉት በ“ጂሃድ አል-ኒቃ” (ማለትም ወሲባዊ ቅዱስ ጦርነት) ስም ሲሆን ወደ ቱኒዚያ የሚመለሱትም እርጉዝ ሆነው ነው” በማለት ሚኒስትሩ ለተከበሩት የፓርላማው አባላት በግልጽ አብራርተዋል፡፡
ከጂሃዲስቶቹ ልጅ አርግዘው የሚመጡት ሴቶች ቁጥር ምን ያህል እንደሆነ ሚኒስትሩ አልጠቆሙም፡፡ ሆኖም በመቶዎች የሚቆጠሩ ሴቶች በጉዳዩ ላይ እንደሚሳተፉ ከዚህም በተጨማሪ ከ3ሺህ በላይ ቱኒዚያውያን የአማጺያኑን ኃይል ለመደገፍ እንደዘመቱ ይነገራል፡፡ ይህ የቱኒዚያውያኑ ቁጥር በአሳድ ላይ ጂሃድ በማወጅ የሶሪያን አማጺዎች ከተቀላቀሉት የሌላ አገር ዜጎች ከፍተኛውን ቁጥር የያዘ ነው፡፡
ሚኒስትሩ እንደሚሉት ከሆነ እርሳቸው ሥልጣን ከያዙ ካለፈው ዓመት መጋቢት ወር ጀምሮ “ስድስት ሺህ ያህል ወጣቶች በሶሪያ የእርስበርስ ጦርነት እንዳይሳተፉ ለመከልከል” መቻሉን ለፓርላማው አስረድተዋል፡፡ አል አረቢያ ሚኒስትሩን ጠቅሶ እንደዘገበው የቱኒዚያን ድንበር በማቋረጥ ወደ ሶሪያ ለመዝመት የሚፈልጉ ወጣቶችን ለመከላከል በቱኒዚያ የድንበር ቁጥጥር መጠናከሩን ገልጾዋል፡፡ በተጨማሪም በዚህ ድንበር በማሻገር ተግባር ላይ የተሰማሩ 86 ግለሰቦች በቁጥጥር ሥር መዋላቸውን አል አረቢያ ጨምሮ ዘግቧል፡፡
አቡ ኢያድ አል-ቱኒዚ (ፎቶ: አል-ማስዳር)
አቡ ኢያድ አል-ቱኒዚ (ፎቶ: አል-ማስዳር)
ጂሃድ አል-ኒቃ ስም ከጋብቻ ውጪ ከበርካታ ሰዎች ጋር ለወሲብ መተኛት በአንዳንድ አክራሪ የሱኒ ሙስሊም ሳላፊስቶች ዘንድ ተቀባይነት ያለው ቅዱስ ጦርነት (ጂሃድ) ነው፡፡ ይህ በሶሪያ ተከስቷል ተብሎ መነገሩ የሙጃሂዲኑን ቅስም ለመስበር የተደረገ የአሳድ ሴራ ነው በማለት የሚኮንኑት አሉ፡፡ በሌላ በኩል ደግሞ “ወሲባዊ ጂሃድ” በሶሪያ እንዲካሄድ የሚመሩት አንሳር አል-ሻሪያ የተባለው በቱኒዚያ የዋንኛው ሳላፊስት እንቅስቃሴ መሪ የሆኑት አቡ ኢያድ አል-ቱኒዚ ናቸው በማለት የሚወነጅሏቸውም በርካታዎች ናቸው፡፡
በአረቡ ዓለም ጉዳይ ላይ የሚዘግቡ የዜና ምንጮች እንደሚሉት ግን “ወሲባዊ ጂሃድ” እንዲካሄድ የተደረገው “በፋትዋ” (እስላማዊ ትዕዛዝ) ነው ይላሉ፡፡ ባለፈው ዓመት ታህሳስ ወር ፋትዋውን ያወጡት በሳውዲ አረቢያ ወግአጥባቂ የሳላፊ (ዋሃቢ) መሪ ሼክ ሞሃመድ አል-አሪፊ እንደሆኑ በተለይ ፕሬስ ቲቪ ምንጮቹ ጠቅሶ መዘገቡ ይታወሳል፡፡ “የአጭር ጊዜ ጋብቻ ወይም ጊዜያዊ ጋብቻ” በሶሪያ ለሚፋለሙት አማጺያን እንደሚያስፈልግና ይህ እንደ ሼክ ሞሃመድ አባባል “የወሲብ ጋብቻ” የአማጺያኑን ቁርጠኝነት የሚያደፋፍር በመሆኑ እስከ 14ዓመት ዕድሜ ያላቸው ወጣት ልጃገረዶችና ሴቶች ሊሳተፉ እንደሚገባና በዚህ ተግባር የሚሳተፉ ሴቶች ሁሉ “ጀነት (ገነት)” የእነርሱ እንደምትሆን ሼኩ ቃል መግባታቸው ፕሬስ ቲቪ አክሎ ገልጾዋል፡፡
ሼክ ሞሃመድ አል-አሪፊ (ፎቶ: Press TV)
ሼክ ሞሃመድ አል-አሪፊ (ፎቶ: Press TV)
ይህ ከተሰማ በኋላ እንዲህ ዓይነቱ ተግባር ፍጹም የተከለከለ (ሃራም) መሆኑን የቀድሞው የቱኒዚያው ታላቁ ሙፍቲ ሼክ ዖትማን ባታኪ በይፋ መቃወማቸውን አል-አላም የዜና አገልግሎት ዘግቦ ነበር፡፡ ወደ ሶሪያ “ለወሲባዊ ጂሃድ” የሚሄዱት ሴቶች “የተታለሉና አእምሯቸው የደነዘዘ” ናቸው በማለት ሼክ ባታኪ ይገልጹዋቸዋል፡፡ ሲቀጥሉም “እንዲያውም በሶሪያ ሊታወጅ የሚገባው ጂሃድ-አክባር (በራስ ላይ የሚታወጅ) ጦርነት” መሆን እንዳለበትና ይህም ራስን ለመቆጣጠር የሚደረግ ጂሃድ በጦርነት ለመፋለም ከመሰለፍ የሚበልጥ “ታላቁ ጂሃድ” እንደሆነ ተናግረዋል፡፡ ከዚህ ውጪ የሚደረገው “ጂሃድ አል-ኒቃ (ወሲባዊ ጂሃድ)” ሴተኛአዳሪነት ወይም ዝሙት እንደሆነ መግለጻቸውን አል-አላም ጨምሮ ዘግቧል፡፡
ታላቁ ሙፍቲ ሼክ ዖትማን ባታኪ (ፎቶ: አለአላም)
ታላቁ ሙፍቲ ሼክ ዖትማን ባታኪ (ፎቶ: አለአላም)
ይህንን ገለጻ ከሰጡ በኋላ ታላቁ ሙፍቲ ሼክ ዖትማን ባታኪ በሥልጣናቸው አልዘለቁም፡፡ ከሥልጣን የመነሳታቸውን ጉዳይ ከተናገሩት የተቃውሞ ንግግር ጋር የተያያዘ እንደሆነ ግን ብዙዎች ይስማሙበታል፡፡
በተያያዘ ዜና በዚሁ እጅግ ደም አፋሳሽ በሆነው የሶሪያ ጦርነት ሳዉዲ አረቢያ ከ1,200 በላይ የሞት ፍርድ የተፈረደባቸውን እስረኞች አማጺያኑን በመደገፍ የአሳድን አገዛዝ እንዲዋጉ በምስጢር መላኳ ተረጋገጠ፡፡ የሳውዲ የአገር ውስጥ ጉዳይ ሚ/ር ይህንን ስጦታ ማቅረቡን አሜሪካ አገር የሚታተመው USA Today የአሶሪያን ዜና አገልግሎት ጠቅሶ ባለፈው ዓመት ሚያዚያ ወር መዘገቡ ይታወሳል፡፡
በወቅቱ “እጅግ ከፍተኛ ምስጢር” በሚል ከአገር ውስጥ ጉዳይ ሚ/ር የተጻፈው ማስታወሻ 1,239 የሞት ቅጣት የተበየነባቸው እስረኞች ወደ ሶሪያ ሄደው በምስጢር አማጺያኑን በመደገፍ እንዲዋጉ፤ ለዚህም ይቅርታ እንዲደረግላቸውና በልዋጭ ለቤተሰቦቻቸው ወርሃዊ የገንዘብ ክፍያ እንዲደረግላቸው በዚሁ ማስታወሻ ላይ ተጠቅሷል፡፡
በሰይፍ እንዲገደሉ” የተወሰነባቸው እነዚህ እስረኞች ነፍስ በማጥፋት፣ አስገድዶ በመድፈር እና አደንዛዥ ዕጽ በማዘዋወር የተወነጀሉ ናቸው፡፡ የሳውዲ ተወላጆች ከሆኑት ወንጀለኞች በተጨማሪ የአፍጋኒስታን፣ የግብጽ፣ የኢራቅ፣ የዮርዳኖስ፣ የኩዌት፣ የፓኪስታን፣ የፍልስጤም፣ የሶማሊያ፣ የሱዳን፣ የሶሪያ እና የየመን ተወላጆች እንደሚገኙበት ተገልጾዋል፡፡
ምስጢራዊውን መረጃው ሳውዲ አረቢያ አስቀድማ የካደች ቢሆንም የዜና ምንጩ የአረቢኛውን ቅጂ ይፋ በማድረጉና የተላኩት እስረኞች በይፋ ከሰጡት ምስክርነት ጋር ተዳምሮ የሳውዲ መንግሥት ጉዳዩን እንዲያምን አድርጎታል፡፡ በወቅቱ ሳውዲ አረቢያ በተመሳሳይ ተግባር ወደፊት እንደማትቀጥል ለሶሪያም ችግር የፖለቲካ መፍትሔ እንደምትፈልግ የሰጠች ቢሆንም ሰሞኑን የወጡ አንዳንድ መረጃዎች የምስጢራዊውን ሰነድ ትክክለኛነት አረጋግጠዋል፡፡ ከተላኩት እስረኞች መካከል 23 የኢራቅ ተወላጆች እና ቁጥራቸው ያልታወቀ የየመን ተወላጆች ግዳጃቸውን ጨርሰውና ከሞት አምልጠው ወደየአገሮቻቸው ተመልሰዋል፡፡ የተቀሩት ያሉበት ሁኔታ እስካሁን አልተገለጸም፡፡
የሜሶፖታሚያ ሥልጣኔ መስራች የሆኑት አሶሪያውያን የሴም ዝርያ ያላቸውና ከአረቦችና አይሁዶች በዘር ፍጹም የተለዩ ናቸው፡፡ አሶሪያውያን ከክርስቶስ ልደት በፊት በመጀመሪው ሺህ ዓመታት የመካከለኛውን ምስራቅ በበላይነት ይቆጣጠሩ ነበር፡፡ (ሽፋን ፎቶ: አለ-አላም)

No comments:

Post a Comment