FREE ALL POLITICAL PRISONERS

FREE ALL POLITICAL PRISONERS
FREE ALL POLITICAL PRISONERS

Friday, September 27, 2013

የደብሪቱ ወተት

(ወለላዬ)

cow milk


ሰፈራችንን መሀል ለመሀል ሰንጥቆ ከሚያልፈው መንገድ በስተቀኝ ሃያ አንድ መኖሪያ ቤቶች ይገኛሉ። ከነዚህ ቤቶች ነዋሪዎች ውስጥ ከአብዛኛዎቹ ጋር የስጋ ዝምድና አለን። በተለይ በአንድ ግቢ ውስጥ የምንኖረው ስምንት ቤተሰቦች ደግሞ የቅርብ – በጣም የቅርብ ዘመዳሞች ነን።
በነዚህ ቤቶች ውስጥ አያቶች፣ እናቶች፣ አባቶች፣ አክስቶች፣ አጎቶች፣ አማትና አማቾች ሲኖሩ ከሁሉም የተውጣጣን የልጅ ልጆችም እንገኛለን። ከአጎቶቻችንና ከአክስቶታችን መካከል ሁለቱ ከኛ ዕድሜ ብዙ ስለማይርቁ ቀረቤታችን የጎላ ነው።
አሰግድ ገ/እግዚአብሔርና …
አሰግድ ቀልደኛ ነው። በማንኛውም ጊዜ በትንሹም በትልቁም ነገር እራሱን አዝናንቶ ሌላንም ለማስደሰት ይጥራል። የወጣለት ፀሐፊም ነው። እንደዛሬው የትያትር ጥበብ ሳይስፋፋ በቴሌቪዥን መስኮት ብቅ ከሚሉ ጥቂት ተዋናዮች መካከልም አንዱ ነበር። አሰግድ አጎቴ ብቻ ሳይሆን ከጉርምስናዬ ማግስት ጀምሮ ምርጥ ጓደኛዬም ሆኖ ቆይቷል። ስለ አሰግድ ይቺን ካልኩ ይበቃኛል ወደቤታችን ድራማ ላምራ።
በቤታችን ውስጥ ቀንና ሰዓታቸው ያልተወሰነ፤ አጫጭር ድራማዎች በየጊዜው ይቀርባሉ። እነዚህ ድራማዎች አይጠኑም፤ ተዋናይ ተመርጦ አይመደብባቸውም፤ ፀሐፊና አዘጋጅ የላቸውም። አንዱ ባሻው መንገድ ይጀምረዋል፤ ሌላው አውቆም ሆነ ሳያውቅም ያግዘዋል፤ በቅብብሎሽ ወይም በግል ድራማው ተሠርቶ ይፈጸማል። ድራማው አስቂኝ ቢሆንም የማያቄሙ ተበዳዮችም ይኖሩታል። ብዙ ግዜ ድራማው በልጅ ልጆች የሚቀርብ ሲሆን፤ አሰግድ ድምቀት ሰጭ ሆኖ ያገለግላል።
አንድ ቀን እንዲህ ተሠራ። አንዷ አክስታችን ከመንደሩ ጠዋት ጠዋት የሚመጣላት ወተት በኪራይ ይዛለች። አከራይዋ ወ/ሮ ደብሪቱ ይባላሉ። ደብሪቱ ዝቅአድርጌ። ኃይለኛነታቸው በሰፊው ስለሚወራ ሰው ሁሉ በጥንቃቄ ነው የሚይዛቸው። የወተት ሂሳብ በወቅቱ ያልከፈለ የጭቃ ጅራፋቸውን ስለሚያወርዱበት ከቀኗ ውልፍች አይልም።
አክስቴ ዘንግታው ይሁን በሌላ አጋጣሚ የዛን ወር የወተት ሂሳብ ሳትከፍል ሦስት ቀን አልፏታል። በአራተኛው ቀን ጠዋት ወፍ ሳይንጫጫ የወ/ሮ ደብሪቱ ድምፅ በግቢያችን ውስጥ ተሰማ።
“ወ/ሮ አሰገደች እንደምን አደሩ? ምነው ምነው ትልቅ ሰው አይደሉም እንዴ!? ከልጆቼ ጉሮሮ ነጥቄ ያከራየኽዎትን የወተት ሂሳብ ሊበሉኝ ነው? ወይስ ምን ሆነው ነው ሦስት ቀን ሙሉ ያላኩልኝ? ከኔ ከደሃይቱ ይሄን በልተው ምን ሊጠቀሙ ነው? ምነው ጡር አይሆንብዎትም ወይ? ነግሬዎታለሁ! ማንንም የምፈራ እንዳይመስልዎት፤ እንቢ ካሉ ሕግ ፊት ነው የምገትርዎት እከነሽና ደብሪቱ! ‘ግዛኝ ግዣኝ ብለው፣ ሊሸጠኝ አሰበኝ’ አለ ያገሬ ሰው! ዛሬ ባይልኩልኝ ውርድ ከራሴ …” የደብሪቱ ንግግር ማለቂያም የለው …
አክስቴ መግቢያ ቀዳዳ ጠፍቷታል፤ በሹክሹክታ ታወራ ጀመር “ይቺ ሴትዮ ጤናም የላት እንዴ?”
“ምን ጤናም የላት ትያለሽ? ለምንድነው! በወቅቱ ያልከፈልሽው?” ባለቤቷ ደነፋ።
“አንተ ደግሞ ዝም በል። ቢረሳ እንኳን ላኩልኝ ይባላል እንጂ፤ በጠዋት መጥቶ ምን ያስለፈልፋል።” አክስቴ ይበልጥ ጮኸች። የግቢው ቤተሰብ በሙሉ የሴትየዋን እሮሮ እየሰማ ነው። ማንም መልስ ሊመልስ አልፈለገም። ሁሉም አድፍጦ ዝም!
ደብሪቱ ብለው ብለው ድምጻቸው ሲጠፋ መሄዳቸው ስለታወቀ ከየቤቱ ብቅ ብቅ ማለት ተጀመረ። አክስቴ ከሁሉም ቀድማ ነበር ውጪውን የረገጠችው። የወንድሟ ልጅ በራፏ ላይ ቆሟል። “ውይ ሽመልስዬ እዚህ ምን ትሠራለህ? ይቺ እብድ በጠዋት ቀሰቀሰችህ አይደል?” አክስቴ ጥፋተኛነት ተሰምቷታል።
“ምን እኔን ብቻ የሰፈሩ ህዝብ በሙሉ እኮ ነው የተረበሸው! አዋጅ የሚናገሩ ነበር የሚመስሉት። ማን ያልሰማ አለ ብለሽ ነው” ሽመልስ ነገሩን ይበልጥ አደመቀው።
“ጉድ! ጉድ! ጉድ! አዋረደችን እኮ! እስቲ በለሊት መጥቶ አፍ መክፈት ምን አመጣው የሷን ብር ይዤ እንዳልጠፋ ነው? ወይስ ገንዘብ ሆነና እንዳልክድ …?”
“ኧረ! ሕግ ፊት እገትርሻለሁም ብለዋል!”
“ሂድ! አንተ ደግሞ ነገር አታንፏቅ፤ ለሃያ ብር ነው ሕግ ፊት የምትገትረኝ!?”
“እኔ ምን አውቃለሁ፤ ሲሉ የሰማሁትን ነው”
“እሷማ ምን ያላለችው አለ! ቆይ! ግድ የለም! እማደርገውን፤ እኔ ነኝ የማውቅ።” አክስቴ ወደ በሩ አመራች።
“እንዴ አሁን ልትሄጂ ነው እንዴ?” ሸመልስ ነገሩ አላማረውም።
“አሁንማ ምን ይሁን ብዬ እሄዳለሁ። እንደሷ አላበድኩ። እንደው እንዴት እንደገባች በሩን ለማየት እንጂ ቡናዬን ጠጥቼ ቀስ ብዬ እደርሳለሁ። የማደርገውን እኔ ነኝ የማውቅ። ሁለተኛ ግን የሷን ወተት … መርዝ ያስጠጣኝ።”
* * * * * * * * * * *
የአክስቴ ቡና ደርሶ ዘመድ ተሰብስቧል፤ ሁለት ሌሎች አክስቶቼና አንድ አጎቴ እስከሚስቱ ቦታቸውን ይዘዋል። አሰግድ አለ፤ ዙሪያውን በልጅ ልጆች ተከቧል። አያታችን በምርኩዛቸው መሬቱን እያንኳኩ ቀኝ እግራቸውን እየጎተቱ ገቡ። ሁሉም ብድግ ብሎ ተቀበላቸው። ማዕከላዊውን ቦታ ይዘው ከተቀመጡ በኋላ፤ “ጠዋት እንደዛ ትለፈልፍ የነበረችው ማናት?” ጥያቄ አቀረቡ።
“ወ/ሮ ደብሪቱ ናታ” አክስቴ ወ/ሮን ጠበቅ አደረገቻት።
“ምን ይሁን ብላ?” አባባ ነገሩ ገርሟቸዋል።
“አልሰሙም እንዴ ወተት አከራይዋ …
“እኮ ምን ይሁን ብላ መጣች?” አላስጨረሷትም።
“የወተት ኪራይ ሳትከፍይ ዘገየሽ ብላ፤ ልትሳደብ ነዋ! ጨፈረችብኝ እኮ! …”
“ለመሆኑ! በሩን ማን ከፈተላት?”
“እንጃላት! እጇን አስገብታ ከፍታ ወይም አንዱ ወጥቶ ይሆናላ”
“ገብቶ ማለትሽ ነው?” አባባ ወደ አሰግድ ተመለከቱ።
አሰግድ ሽሙጡ ቢገባውም መልስ ሊሰጥ አልፈለገም። “ደግሞ እኮ ስትናገር አንገቷን የታነቀች ነው የምትመስል” አለ አሰግድ፤ የሴትዬዋ ነገር እንዲሰፋ ፈልጓል፤ ሁሉም በጅምላ ሳቀ።
“ኧረ! የሚያንቅ ይነቃትና፤ ስትታይም የታነቀች ነው የምትመስል” የእህቷ መሰደብ ያንገበገባት ትንሿ አክስታችን ነበረች። የአሰግድ ሳቅ ጎልቶ ወጣ።
“አዎን ሳቅ አንተ! ጅብም ሲጎትተኝ ብታይ ሳትስቅ አትቀር። አይ! የኛ ወንድም!” አክስቴ ተናደደችበት።
“አንችስ ለምን ሳትከፍይ ቆየሽ?” አያታችን ሌላ ጥያቄ ወረወሩ።
“እርስት አደረኩት አባብዬ”
“እርስት አደረኩት! አንቺ የረሳሽ እንደሆን እሷም መርሳት አለባት?” ሁሉም ሳቁን ለቀቀው። አባባም በራሳቸው ንግግር ይስቁ ጀመር። ወርቅ ጥርሳቸው ከግራና ከቀኝ እንደ አንፖል ያበራል።
“እናስ! የሆነ እንደሆን ሀገር ጥዬ አልኮበልል፤ በጠዋት መጥቶ መለፍለፍን ምን አመጣው? ቆይ! ግድየለም! የማደርገውን እኔ ነኝ የማውቅ …”
“አክስቴ ገንዘባቸውን ወደዚያ ወርውሪላቸው እንጂ ምንም እንዳትናገሪ” ሽመልስ ጣልቃ ገባ።
“ለምንድነው የማልናገር? አንተን ደግሞ የሷ ጠበቃ ያደረገህ ማነው? ፎቃቃ”
“አይ! ወንድማቸው የአብዮት ጥበቃ ሊቀመንበር ናቸው ሲባል ስለሰማሁ …”
“ታድያ! የሆነስ እንደሆን በጠዋት እየተነሳሽ ሰው ስደቢ ብሎ ፈቅዶላታል ማለት ነው? ማነው ከዘሯ የነገሠ?” ትንሿ አክስት ተንጣጣች። አክስቴ እየተናገረች ሥራዋን አላቋረጠችም። ቁርስ አቅርባ ተበላ። አቦል ቡና ተዳረሰ፤ አሁን ሁሉም ጎኑ ካለው ሰው ጋር ጨዋታ ጀምሯል። አሰግድ ከኛ ጋር እየቀለደ ነው፤ አባባ ጣቶቻቸውን አቆላልፈው ሁለት አውራ ጣቶቻቸውን ማገለባበጥ ይዘዋል።
ሽመልስ ገባ ወጣ ይላል። አክስቴ አልወደደችለትም። “መቀመጫህ ላይ መርፌ የተሰካ ይመስል፤ ምን ያንቆራጥጥሃል? ቡና እያፈላሁ የሚክለፈለፍብኝ አልወድም … ትቀመጥ እንደሆን ተቀመጥ!” ሸመልስ ውጭውን መርጦ ወጣ።
ሁለተኛውና ሦስተኛው ቡና ተፈልቶ ተጠጣ። አክስቴ ስኒውን አነሳስታ፣ እቃውን አጣጥባ ልብሷን ለባብሳ ተነሳች። መሃረቧ ላይ ብር ቋጥራ ያዘች። ወ/ሮ ደብሬ ዛሬ ጉዷ ፈልቷል። ሁለቱ ሌሎቹ አክስቶቼ በዛው የምንደርስበት አለ ብለው ከአክስቴ ጋር ለመሄድ እየጠበቋት ነው። አሰግድ ሥራው ሊሄድ ተዘጋጅቷል። እግረ መንገዱን ግን የደብሬን ጉዳይ ለማየት ፈልጓል። አብዛኛው የልጅ ልጅ በር ላይ እንደዘብ ቆሞ ይሳሳቃል።
በዚህ መሀል ያልታሰበ ነገር ተፈጠረ። የደብሬ ልጅ እንደወትሮዋ ወተቱን በነጭ ጨርቅ ሸፍና በራፋችን ላይ ቆማ ታየች። አክስቴ እንደዛ ተናግረው ካሁን ወዲያ ወ/ሮ ደብሬ ወተት ይልካሉ የሚል ግምት አልነበራትም፤ አብዛኛውም የሚያስበው ይሄንኑ ነው።
አክስቴ ልጅቷን እንደጉድ እያየቻት “አንቺ! …” ብላ ልትናገር ስትጀምር ሸመልስ አንዳች የሚያህል ድንጋይ ይዞ እግሯ ላይ ተከመረ።
“ምንድንነው ነገሩ?” አክስቴ አንባረቀች። ሁሉም ገርሞት ሽመልስ ላይ ዓይኑን ተክሏል።
“አክስቴ ይቅር በይኝ፤ ይቅር በይኝ” ድንጋዩን አስቀምጦ እግሯን አንቆ ያዘ።
“ምንድነው ነገሩ? ጤናም አልያዘኽ? ምኑን ነው ይቅር የምልህ? ኧረ! ይሄ ልጅ አንድ በሉልኝ …” አክስቴ ቆጣ ማለት ጀመረች።
ሁሉም በጥያቄ ያጣድፈው ጀመር፤ ምንድነው? ምን አድርገሃል? አባባ ተነስተው ጎኑን በምርኩዛቸው ጎንተል አደረጉት። ተናደዋል። “ምንድንነው ያደረግኸው? አትናገርም?”
ሽመልስ ይሄን ጊዜ ተነስቶ ቆመ። ፊቱ ፀሐይ ወጥቶ የሚዘንብ ቀን መስሏል። ሳቅም ድንጋጤም ይዞታል።
“ምንድነው ምን አድርገኻል?” የአክስቴ የግንባር ቆዳ ተሰበሰበ።
“ጠዋት …”
“እ … ጠዋት”
“እማማ ደብሬ”
“እ … እማማ ደብሬ ትናገር እንደሆን ተናገር” አክስቴ ይበልጥ ተናደደች።
“እማማ ደብሬ አልመጡም።”
“ታድያ! ማነው እንደዛ ይለፈልፍ የነበረው? እኔ ነኝ እንዳትለኝ ብቻ” አክስቴ አፏን ይዛ ዓይኗን አፈጠጠች።
“አዎን! እኔ ነኝ አክስትዬ ይቅርታ አድርጊልኝ” እንደገና እግሯን አንቆ ያዘ። ሁሉም ሳቁን ለቀቀው አክስቴ እንደመሳቅ እያለች ከእግሯ ላይ ካነሳችው በኋላ እጁን ቀጨም አድርጋ ይዛ “እስቲ እንደጠዋቱ ተናገር” አለችው።
ሽመልስ በአንድ እጁ ጉሮሮውን ይዞ ድምፁን አስተካክሎ መናገር ጀመረ፤ “ወ/ሮ እጅጋየሁ እንደምን አደሩ? ወር ሙሉ ወተቴን ጠጥተው ገንዘቤን ያላኩልኝ ምን ሆነው ነው? ምነው ነውር እማይደል …?”
ጠዋት የተሰማው የደብሪቱ ድምፅ በድጋሚ ግቢውን ሞላው።
(Photo: ILRI – ወ/ሮ ደብሪቱ አይደሉም)

No comments:

Post a Comment