FREE ALL POLITICAL PRISONERS

FREE ALL POLITICAL PRISONERS
FREE ALL POLITICAL PRISONERS

Wednesday, March 12, 2014

ፖለቲካዊ ቁርጠኝነት ለችግሮቻችን የመፍትሄው ቁልፍ

(ገለታው ዘለቀ)

commitment


የሃገራቸው ነገር ሲነሳ የሚከነክናቸው ወገኖቻችን ኢትዮጵያ ላለባት ችግር መፍት ሄው ምንድነው? እያሉ ኣጥብቀው ሲጠይቁ ይደመጣል። መፍትሄውም ብቻ ሳይሆን ችግሩ ማለትም እውነተኛው ችግር የት ላይ ነው ያለው? ብለውም ኣጥብቀው ሲደመሙ ይታያል። በዛሬዋ ኣጭር ጽህፌ በነዚህ መራራ ጥያቄዎች ዙሪያ ቁንጥል ኣሳብ ለማቀበል ኣስቢያለሁ።
በርግጥም ሁላችን  ኢትዮጵያዊያን የሆንን ችግሩ ምንድነው? ብለን ከጠየቅን ኣንዳንዶች ሊገረሙብን ይችላሉ። የችግሩ ተካፋይ ሆነን ሳለ፣ እየተጉላላን ያለነው እኛው ሆነን ሳለ፣  እንደገና መልሰን  የሃገራችን ችግር የት ጋር ነው? ብለን ስንጠይቅ የምናወጋቸው ሰዎች ምናልባትም ግራ ሊጋቡ ቢችሉ ኣይደንቅም። ነገር ግን መጠየቃችን ትክክል ነው።
በመጽሃፍ ቅዱስ ውስጥ ትንቢተ ዳንዔል ላይ ኣንድ ናቡከደነጾር የተባለ ንጉስ ኣንድ ጊዜ ጠቢባንን ጠርቶ የህልም ፍቺ ይጠይቃል። ጥበበኞቹም ህልሙን ንገረንና ፍቺውን እንነግርሃለን ሲሉት ህልሙ ጠፍቶብኛል ስለዚህ ህልሙንም ፍቺውንም dreamውለዱ ብሎ ጉድ እንዳፈላ እናነባለን።
እኛ ኢትዮጵያዊያን የዋናው ችግር ተጽእኖዎች የየእለት ኑሮኣችንን ሲያምሱት ብናይም ዋናውን የችግሩን ምንጭ መፈለጋችን ግን ኣሁንም ትክክል ነው።
የሃገራችንን ዋና ችግር የት ጋር ነው ብለን ኣጥብቀን ከጠየቅን በርግጥ የስርዓት ችግር ነው ወይ? ስርዓት በማጣታችን ነው ወይ የከፋ ችግር ላይ የወደቅነው? ብለን እንጠይቃለን።  በዚህ ኣገባብ ስርዓት ስንል የኣይዲዮሎጂውን ጉዳይ ሳይሆን ፍትህና ተጠያቂነት፣ ግልጽነትና የህዝብ የበላይነት የሚንሸራሸርበት ሲስተም ተዘርግቷል ወይ ብሎ የመጠየቅ ያህል ነው።  ስለ ስርዓት ስናነሳ ደግሞ በዋናነት የሚታየው ህገ- መንግስታዊ ስርዓቱ ነው። ህገ-መንግስታዊ ስርዓቱ ምን ያህል ለዜጎች ይጨነቃል፣ ምን ያህል ለፍትህና ለነጻነት ለህዝቦች ጥቅም መንሸራሸሪያ ይህናል? ብለን እንድንጠይቅ ያደርገናል። በዚህ ረገድ በርግጥ መሻሻል ያለባቸው ጉዳዮች ቢኖሩም በዋናነት ግን ችግራችን የስርዓት ችግር ሆኖ ኣናይም። ለኣብነት የ1955ቱን ህገ መንግስት ስናይ የፕሬስ ነጻነትን ይሰጣል፣ እኩል የህግ ከለላ ይሰጣል፣ የመሰብሰብ፣ ሰልፍ የማድረግ መብትን ሁሉ ይሰጣል። የደርጉም ቢሆን ለዜጎች የሚጨነቅ ኣይነት ነው። “ኢትዮጵያዊያን በህግ ፊት እኩል ናቸው” ይላል። ከሁሉ በላይ ደግሞ የ1995ቱን ስናይ “ሰብዓዊ መብቶችና ነጻነቶች ከሰው ልጅ ተፈጥሮ የሚመነጩ የማይጣሱና የማይገፈፉ ናቸው” ብሎ እጅግ ኣጠንክሮ ለዜጎች መብት መቆሙን ይደነግጋል።
በውነቱ ይህ ኣንቀጽ ብቻውን ለኛ ለኢትዮጵያዊያን ዋስትና ይሆን ነበር። ይሁን እንጂ ተግባራዊው እውነት ደግሞ ለብቻው በተቃራኒው ተንሰራፍቶ ይታያል። ይህ ለምን ሆነ? እንዴት እንዲህ ሊሖን ይችላል? ብለን ነው መጠየቅ ያለብን። እንዲህ ስንጠይቅ የችግሩ ዋና ጉዳይም የስርዓት እጦት ሳይሆን ሌላ ጉዳይ መሆኑን እንረዳለን። በርግጥ ለወደፊቱዋ ኢትዮጵያ የተሻለ ስርዓት ማምጣት ያስፈልጋል። በተለይም ብዙህነቱዋን ተንከባክቦ የሚይዝ ማህበራዊ የፖለቲካ ስርዓት ያሻናል። ያ ማለት ግን ከችግራችን እንድንወጣ ብቻውን ዋስትና ነው ማለት ኣይደለም። የቱንም ያህል ጥሩ ስርዓት ዘርግተን ከችግራችን ሳንወጣ ልንቆይ እንችላለን። ርግጥ ነው የማንነት ፖለቲካ ማህበራዊ ቀውስን ያመጣ ችግሮች የበለጠ እንዲነዱ የሚያደርግ ጉዳይ በመሆኑ ከዚህ መንግስት ውድቀት በሁዋላ ከዚህ የፖለቲካ መዋቅር መውጣታችን ለመፍትሄ ትልቅ በር ኣለው። ይሁን እንጂ ኣሁንም ቢሆን የቱንም ያህል ቆንጆ ስርዓት እናምጣ ኢትዮጵያን ከመከራና ከርሃብ የሚያወጣት እሱ  ብቻውን ኣይደለም። ታዲያ ምንድነው? የሚል ጥያቄ መምጣት ኣለበት። ኣዎ፣ ዋናው የሃገራችን ችግር ያለው የፖለቲከኖች ስብእና ተክለሰውነት ወይም ፐርሰናሊቲ ጋር የተገናኘ ነው።
ሃገራችን ከችግር እንድትወጣ ከተፈለገ የፖለቲካ ቁርጠኝነትን ይጠይቃል። የችግሮቻችን ቁንጮም የፖለቲካ ቁርጠኝነት እጦት ነው ብሎ መደምደም ይቻላል።የፖለቲካ ቁርጠኝነት ስንል ኣንድ ፓርቲ ስልጣን ከያዘ በሁዋላ የፍርድ ቤቱን ልጓም ለቀን መልሶ ከበላንም ይብላን፣  በራሳችን ላይ ይፍረድብን፣  ብሎ በራስ ላይ የመወሰን ኣቋም ነው። ወታደሩን ኣገርህን ጠብቅ የፓርቲ ጠባቂ ኣይደለህም ኣንተ ኣገር ጠባቂ ነህ ለማለት የፖለቲካ ሰዎችን ቁርጠኝነት ይጠይቃል። ፖሊሱን፣ ባንኩን፣ ሚዲያውን ሁሉ ልጓሙን ለቆ በሙያህ ኣገልግል ብሎ መወሰን ሲቻል ነው ከገባንበት ኣረንቋ የምንወጣው። የናፈቀንን ዴሞክራሲ በህይወት የምናየው። ጥያቄው ይህ የፖለቲካ ቁርጠኝነት እንዴት ሊመጣ ይችላል ነው። የፖለቲካ ቁርጠኝነት ከጥቂት የፖለቲካ መሪዎች ከራስ ጥቅምና ዝና በላይ የህብረተሰብን ዝናና ጥቅም በተጠሙ ሰዎች ሊነቃነቅ ይችላል። ኣንድ ቁርጠኛ መሪ ኣገር ሊለውጥ ይችላል። በታሪክ የታዩ ኣንዳንድ ቁርጠኛ መሪዎች በየሃገሩ ተነስተው ጥሩ መሰረት እየጣሉ ኣልፈዋል። በሃገራችንም የተጠማነው ይህንን ነው።
በኣሁኑ ጊዜ ተቃዋሚው ክፍል መንግስትን ኣጥብቆ ማውገዙ ትክክል ነው። የህዝቡም ልብ ነጸብራቅ ነው። ይሁን እንጂ ይህ መንግስት በማንኛውም መንገድ ሲወድቅ ስልጣን ይዞ ጥሩ ስርዓት መዘርጋቱ ብቻ ሳይሆን የፖለቲካ ቁርጠኝነት (political commitment) ያላቸውን ሰዎች ይዘዋል ወይ? ብለን እንድናስብ ያደርገናል። በዚህ ረገድ ተቃዋሚው ጥቃቅን በሆኑ ፖሊሲዎች ከመከፋፈል ይልቅ ወደ ጋራ እያመሩ ከሁሉ በላይ የፖለቲከኞችን ስብእና የመገንባቱ ላይ ማተኮር ለነገይቱ ኢትዮጵያ ዋስትና ይሆናል። ይህን ስብእና ወይም ተክለሰውነት የመገንባት ስራ ፓርቲዎችን ቢዚ የሚያደርግ ወቅታዊ ስራ መሆን ኣለበት። ኢትዮጵያ በኣሁኑ ደረጃዋ ጥቃቅን ፖሊሲዎችን በማነጻጸር የምታማርጥበት ጊዜ ላይ ኣይደለችም። መሰረታዊ የሆኑ ጉዳዮችን ያጣች በመሆኑዋ የስካንዲኒቪያው ኣይነት ዴሞክራሲ ይሻልሻል የኣሜሪካው ኣይነት? ማለቱ ያልበላትን የማከክ ያህል ነው። ሁሉቱም ሆኖላትስ ነው?
ዋናው በኣሁኑ የኢትዮጵያ ነባራዊ ሁኔታ ጉዳይ ፓርቲዎች እኔ እሻላለሁ ለማለት ዋናው መመዘኛቸው የተሰባሰቡት በተለይም ኣመራር ላይ ያሉት ግለሰቦች የፖለቲካ ቁጠኝነት ኣላቸው ወይ? ቁርጠኝነት በሞላቸው ሰዎች ቁጥር የትኛው ፓርቲ ያይላል? የሚል ልብ ያለው ድጋፍ ነው በተግባር የሚታየው ወይም መታየት ያለብት።
በቲየሪ ደረጃ በኣሁኑዋ ኢትዮጵያ በፍርድ ቤት ጉዳይ መንግስት ጣልቃ ኣይገባም። ይሁን እንጂ በተግባር ይገባል። ይገባል ብቻም ሳይሆን ፍርድ ቤት የፖለቲካ መሳሪያ ነው። ኣሁን እዚህ ጋር የጎዳን የስርዓቱ ወይም የኣሰራሩ ጉዳይ ሳይሆን መከራ ውስጥ የከተተን ጉዳይ የግለሰቦች ስብእና ጉዳይ ሆኖ ነው የምናየው። ለምን እነዚህ ግለሰቦች ስርዓቱን ይጥሳሉ፣ ህጉ ለምን ኣቅም ያጣል? ካልን የፖለቲከኞቹ ላእላይ ስብስብ በተለያየ የግል ጥቅማጥቅም የተተበተበ በመሆኑ ነው። ድህነታችንም ኣንዱ ኣስተዋጾ ያደረገ ይመስላል። የተሻለ ስራ ለማግኝነት፣ ከድህነት ለመላቀቅ፣ ፖለቲካን መሳሪያ ማድረጉ የተለመደ መሆኑና ወደዚያ ጠጋ ያሉ ሃላፊዎች በዚህ ሞቲቭ የተሞሉ  ስለበዙበት ስርዓቱ በቁሙ እንዲሞት ኣድርጎታል።
ባለፈው ጊዜ ኢትዮጵያ ብሄራዊ እርቅ ኮሚሽን ማቋቋም ያስፈልጋታል የሚል ኣንድ ኣርቲክል ጽፌ ነበር። በርግጥም በኣሁኑ የነጻነት ትግል ኣሰላለፍ በኩል ጎድሎ የታየው ይሄ ነውና ይህንን ማቋቋም ተገቢ ነው። ይህ ኮሚሽን ፓርቲዎችን እያበራታታ ይህን ተፈላጊ ስብእና በመገንባቱ ረገድ ከፍተኛ ኣስተዋጾ ያደርጋል። ፓርቲዎችን በማቀራረብ ረገድ፣ የመፍትሄ ኣሳቦችን በማጠናቀር ረገድ፣ ለኣዲሲቱዋ ኢትዮጵያ የሚሆነውን ኣዲስ ሰውነት በመጠቆሙ ረገድ ከባድ ሚና ሊጫወት ይችላል። ከዚያ በተረፈ ደግሞ እኛ ተራ ዜጎች መሪዎቻችንን የማጎልበትና ወደ ህብረት የመግፋት እንዲሁም ስብእናቸውን የመገንባት ሃላፊነት ኣለብን።
የብዙ ኣፍሪካ ሃገሮች ችግር ይሄ ይመስለኛል። ታግለን በብዙ መስዋእትነት ኣንድ ኣምባገነን  ከጣልን በኋላ መልሰን በሌላ ኣምባ ገነን እንተካለን። ሌላው ኣለም እየተሻሻለ ሲሄድ ይሄኛው ክፍለ ኣለም ወደ ኋላ የቀረበት ትልቁ ምክንያት የነጻነት ታጋዮች ራሳቸው በሚገባ ለኣመራር የሚበቃ ስብእና ሳያዳብሩ ወደ ስልጣን ስለሚመጡ ነው።ደቡብ ሱዳን ለዚህ ጥሩ ምሳሌ ናት። ለብዙ ኣመታት የነጻነት ትግል ታግለው፣ ብዙ ደም በመፍሰሱ ዓለም ሁሉ  እነዚህ ሰዎች ቢገነጠሉ ይሻላል ብሎ ፈርዶላቸው ተገነጠሉ። የዳርፉሩን እልቂት የማያውቅ፣ ያልሰማ ያለም ክፍል የለም። ያ ሁሉ ሆኖ ኣዲስ ኣገር ከመሰረቱ በኋላ ገና ኣንድ ጊዜ እንኳን ምርጫ ሳያካሂዱ፣ በህዝብ የተመረጠ መንግስት ሳይመሰርቱ፣ ከሁለት ዓመት ያልዘለለ እድሜ ያላትን ኣገር በጎሳ ከፋፍለው ማመስ ጀመሩ።
 ያለ መታደል ሆኖብን በኣንዳንድ ኣፍሪካ ሃገራት የሚነሱ መሪዎች ስልጣን ላይ ከመጡ በሁዋላ ሁለት ነገር በጣም ይወዳሉ። ኣንደኛው ዝና ሲሆን ሁለተኛው ገንዘብ ነው። ሁለቱም እጆቻቸው ይዘዋል። ባንዱ ስልጣን በሌላው ገንዘብ። ዝናውን ወደው ገንዘቡን ችላ የሚሉ ቢሆኑ ትንሽ ይሻል ነበር። ነገር ግን ሁለቱንም በሃይል ስለሚወዱና ለዚህ የተሰጠ ስብእናቸው በውስጣቸው ስላልሞተ ክብ በሆነ ችግር ውስጥ እንድንወድቅ ኣድርጎናል።ኢትዮጵያዊያን በዚህ ላይ ልንነቃ ይገባናል። በተለይ የፖለቲካ ሰው መሆን የፈለጉ ወገኖቻችን፣ መሪ መሆን የሚሹ ወገኖቻችን በየጊዜው የባህርይ ለውጥ እያሳዩ በኣመለካከትና በሃላፊነት ስሜት እያደጉልን እንዲሄዱ እንሻለን። ከፍ ሲል እንዳልኩት እኛ ተራ ዜጎች ከውጭ ሆነን መፍረድ ብቻ ሳይሆን መሪዎቻችንን መንከባከብና ፍቅርን ክብርን ማሳየት ለፖለቲካ ቁርጠኝነታቸው ሃይል ይሰጣል።
እግዚአብሄር ኢትዮጵያን ይባርክ!
geletawzeleke@gmail.com
http://www.goolgule.com/the-solution-is-political-commitment/

No comments:

Post a Comment