FREE ALL POLITICAL PRISONERS

FREE ALL POLITICAL PRISONERS
FREE ALL POLITICAL PRISONERS

Wednesday, May 15, 2013

የታሰሩት ባለስልጣናትና ነጋዴዎች ሰብአዊ መብታቸው እንዳልተከበረ ፣ ከጠበቆቻቸው ጋር ለመመካከር እንዳልቻሉ ለፍርድ ቤቱ ቅሬታ አቀረቡ


ሰሞኑን ፍርድ ቤት የቀረቡት የመንግስት ሌቦችና እና ተረኛ የፖለቲካ “ተጠልፎ ወዳቂዎች ” ፍርድ ቤት ሲቀርቡ ሰብአዊ መብታቸው እንዳልተከበረ ፣ ከጠበቆቻቸው ጋር ለመመካከር እንዳልቻሉ ፣በፍተሻ ወቅት (አንዳንዶቹ ያለ ፍርድ ቤት ትእዛዝ ነው ቤታቸው የተፈተሸው ) የራሳቸውን እና የቤተሰቦቻቸውን ክብር በሚነካ መልኩ ፍተሻው እንደተካሄደባቸው ለፍርድ ቤቱ ቅሬታ አቅርበዋል ፡፡ የመንግስት ሚዲያዎችም ባቀረቡት ሚዛናዊ ያልሆነ ዘገባም ልጆቻቸውን ጨምሮ ወዳጅ ዘመድ ሳይቀር ስነልቦናዊ ጉዳት እንዳደረሰባቸውም ጨምረው ገልፀዋል፡፡ እኛም እንላለን ፡ “ የተከበራችሁ ባለስልጣኖቻችን ሆይ ቅሬታችሁ በእርግጥም ትክክል እንደሆነ ቅንጣት ታህል ጥርጣሬ የለንም፡፡ ግና እናንተው ጠፍጥፋችሁ የጋገራችሁት የፍትህ ስርዐት ነው ፣ ከህዝብ አልፎ እናንተንም ጭምር እየበላ ያለውና አብራችሁን ቻል አድርጉት ” እንበላቸው ይሆን? ቀደም ብዬ ከላይ እንዳሰፈርኩት ለፍርድ ቤቱ ያቀረባችሁት ቅሬታ ትክክለኝነቱ ላይ ማንም ጥርጣሬ የለውም ፡፡ በሁኔታውም እንደ ሰው እኛም ማዘናችንን እየገለፅን ግን ደግሞ የኛዎቹ ኮሚቴዎች ላይ የደረሰውን በጥቂቱም ቢሆን የማየት እድል ስለገጠማችሁ “ ታዲያሳ እንዴት አያችሁት?” በሚል መጠይቅ እንሞግታችኋለን ፡፡ አሁን እናንተ ላይ ደርሶ ከገለፃችሁት እጅግ ከባድ የሆነ የመብት ጥሰት ኮሚቴዎቻችን አስተናግደዋል ፡፡ ኮሚቴዎቻችን ማናችሁም ልትሸከሙት ቀርቶ ልታስቡት የሚከብድ የስቃይ ዶፍ የወረደባቸው እንደ እናንተ የሀገር ሀብት ዘርፈው ( የፖለቲካው መጠላለፍ እንዳለ ሆኖ ማለቴ ነው) ሳይሆን ንፁህ ህገ መንግስታዊ የመብት ጥያቄ በመጠየቃቸው ብቻ እና ብቻ ነው፡፡ ከፊሎቹ ደግሞ ለምን ቁርዐንና ሃዲስ አስተማራችሁ ተብለው በእጃቸው ላይ የተገኘው ቁርዐንና ሃዲስ እንደ ማስረጃ እየተቆጠረ ነው በእስር እየማቀቁ ያሉት ፡፡ ንፁሃኖቹ ኮሚቴዎቻችን እና ሌሎች ወንድሞች ያለ ወንጀላቸው ሽብርተኛ ተብለው በተለምዶው አጠራር ማእከላዊ ተብሎ በሚጠራው ማሰቃያ ካምፕ (በአፍሪካ ተወዳዳሪ የማይገኝለት ጓንታናሞ ) ውስጥ ማሰብ እና ማስተንተን በተሳናቸው ነፍሰ ገዳዮች የደረሰባቸው ከባድ ድብደባ ፣ እንዲሁም በፍርድ ቤት ሳይቀር እንዳይታይ ታግዶ በነበረው “ጂሃዳዊ ሃረካት ” ዘጋቢ ፊልም አማካኝነት ወንጀለኛ ሳይሆኑ ወንጀለኛ ተደርገው በአደባባይ ፍርድ ሲሰጥባቸው ፣ የኮሚቴዎቻችን ህፃናት ልጆችን ጨምሮ ቤተሰቦቻቸውና ህዝበ ሙስሊሙ ላይ የደረሰውን የስነ ልቦና ጉዳት ምን ያህል እንደሆነ ተረዳችሁት አይደል ? በናንተው ተጠፍጥፎ የተሰራውን “የእቃቃ ጨዋታ” የመሰለ የፍትህ ስርዐታችሁን ምን ያህል አሳፋሪ ደረጃ ላይ እንዳለ ታሳረሪዎቹም ኣሳሳሪዎቹም እንደተገነዘባችሁት እናምናለን፡፡
“የተከበራችሁ ባለስልጣናት ሆይ፡ እባካችሁ ጉድጓዱን አትቆፍሩ፣ ከቆፈራችሁም ጥልቅ አድርጋችሁ አትቆፍሩት እናንተም ልትገቡበት ትችላላችሁና ” ብለን ብንመክር ብናስመክር አልሰማ ብላችሁን ይሀው ዛሬ በቆፈራችሁት ጉድጓድ ውስጥ ጠልቃችሁ ስትገቡበት እያየን ነው ፡፡ በደረሰባችሁ የመብት ጥሰት ስትማረሩ እና ቤተሰቦቸችሁም ምን ያህል በስነ ልቦና እንደተጎዱ ስትነግሩን ፣ የእኛዎቹን ኮሚቴዎች ስቃይንና እሱን ተከትሎ የእኛም ስነ ልቦና ምን ያህል ተጎድቶ እንደነበር ስላያችሁልን በመጠኑም ቢሆን ደስ ብሎናል፡፡ እንደ እናንተ ልጆችና ቤተሰቦች ሁሉ የኛዎቹ ንፁሃን ኮሚቴዎቻችን ልጆችና ቤተሰቦችም የከፋ ስነልቦናዊ ጉዳት ደርሶባቸዋል ፡፡ እናንተ ዛሬ የፍርድ ቤት ወረቀት ሳይያዝ ቤታችሁ መበርበሩን ለፍርድ ቤቱ አቤት ከማለታችሁ ቀደም ብሎ የበርካታ ሙስሊም ኢትዮፕያዊያን ቤቶች በውድቅት ሌሊት እናንተ ባሰማራችኋቸው ጭንብል ለባሽ “ወሮበሎች “ ንብረቶቻቸው ተዘርፈዋል ፣ አካላዊም ጥቃት ደርሶባቸዋል ፡፡ የእናንተው ስራ ውጤት የሆነው እና ዛሬ እያማረራችሁት ያለው ፍትህ ስርዐት ትላንት ምንም ያላደረጉ እናቶችና ሴቶችን አስሮ አሰቃይቷል፡፡ አንዲት ወላድ ሴት (ከአራስ ቤት ከወጣች 5 ወር ቢሆናት ነው) በአንዋር መስጂድ ተገኝተሻል በመርካቶ አራተኛ ፖሊስ ጣቢያ አስረዋት አራስ ልጇ ተርቦ እሪሪ እያለ እያዩት አውሬዎቹ ፖሊሶቻችሁ ልጇን እንኳ እንዳታጠባ የከለከሏት ዘግናኝ ድርጊት ከተፈፀመ አመት እንኳ አልሞላውም ፡፡ እናም ክቡራን ባለስልጣኖቻችን ሆይ ፡ “ የመንግስት ሌቦች ” ተብላችሁ ዘብጥያ በወረዳችሁበት ቅፅበት ከሰብኣዊ መብት ጥሰት ጋር ተያይዞ ያቀረባችሁት አቤቱታ (ለዛውም እናንተ በቤተሰብ አያያዝ አይነት ተይዛችሁ እንደሆነ ልብ በሉ) ኮሚቴዎቻችንን ጨምሮ ሌሎች ንፁሃን ኢትዮፕያዊያን ላይ ከደረሰው ጋር ሲነጻጸር ምንም ማለት ነው፡፡ ቢሆንም ግን ቢያንስ ቢያንስ ለትዝብት ያህል እንኳ “ ጠፍጥፋችሁ ” የሰራችሁት የፍትህ ስርዐት ምን ያህል ሸውራራ እንደሆነ መታዘባችሁን ወደነዋል ፡፡ የሴራ ፖለቲካ ትኩሳቱን መቋቋም ተስኗችሁ ዛሬ “ በመንግስት ሌቦች ” የዳቦ ስም ዘብጥያ የወረዳችሁ ባለስልጣናት ሆይ እኛ ፍትህ ፍትህ እያልን በአደባባይ ስንጮህ የነበረው ለራሳችን ብቻ ሳይሆን ለእናንተም ፣ ለመላው ሀገራችን ህዝብ ጭምርም እንደነበር አያችሁት አይደል ?
ጠበቆቻችሁ ጋር እንዳትገናኙ መደረጋችሁም ሆነ በፍተሻ ወቅት እናንተው ባሰለጠናችኋቸው “ዋልጌ” የፀጥታ ሰዎች ባደረሱባችሁ ሰብአዊ ጥሰት ሀዘን ቢሰማኝም በኮሚቴዎቻችንና በሌሎች ወንድሞቻችን ላይ፣ በህፃናት ልጆቻቸው ፣ በሚስቶቻቸውና በሚያከብሯቸው ሰዎች ፊት የደረሰባቸውን እንግልት ስናስበው ደግሞ “በሰፈሩት ቁና …” የሚለውን ተረት እንድናስታውሳችሁ ተገደና ል፡፡ ይህን ስል ግን በድላችሁናል እንዲሁም የፍትህ ስርዐቱ በእናንተ የተፈበረከ ስለሆነ ደግ ሆናችሁ ፣ ይበላችሁ አንልም፡፡ ልክ ለኮሚቴዎቻችንና ለሌሎች ኢትዮፕያዊያን እንደምንመኘው ሁሉ ፍትሃዊ የፍትህ አያያዝ እና ፍትሃዊ ፍርድ እንድታገኙ እንመኛለን ፡፡ በእስር ቤት ሆናችሁም ቢሆን ግን “የፍትህ ያለህ ” ጩሀታችንን እንድትቀላቀሉት ግን የትግል ጥሪ እናቀርባለን፡፡ አብራችሁን “ የፍትህ ያለህ፣ ፍትህ ናፈቀን፣ ህግ ይከበር ፣ድምፃችን ይሰማ ” እንድትሉ ዘንድ እንጠይቃችኋለን፡፡ በእስር ቤትም ሆኖ መታገል እንዳለ ከሰላም አምባሰደሮቹ ኮሚቴዎቻችን እንዲሁም ከእነ ርእዮተ አለሙ እና እስክንድር መማር ትችላላችሁ ፡፡
እናንተም ዛሬ ለጊዜው አሳሪ የሆናችሁ ግና ስለነገው የማታውቁ ተረኛ “ ዘብጥያ ወራጆች ”፣ የዛሬ ባላስልጣናት ሆይ ፣ በልካችሁ ጠፍጥፋችሁ የሰራችሁት የመሰላችሁ “ ሸውራራው ” የፍትህ ስርዐት ነገ እናንተንም “ የመንግስት ሌቦች” ብሎ ሊበላችሁ እንደማይችል ምንም አይነት ዋስትና የላችሁምና ዛሬውኑ ከጓደኞቻችሁ በመማር የሀገሪቱ የፍትህ ስርዐት እንዲስተካከል ከአሁኗ ሰዐት ጀምሮ ለራሳችሁ ስትሉ እንድትታገሉ እንመክራለን፡፡ እናንተም ባላችሁበት የስልጣን ኮርቻ ላይ እንዳላችሁ አብራችሁን “ ፍትህ ናፈቀን ፣ ህግ ይከበር ፣ ድምፃችን ይሰማ ፣ ኮሚቴዎቻችን ይፈቱ፣ እነ እስክንድርና ርእዮተ ይፈቱ ” እያላችሁ ድምፃችሁን አሰሙ፡፡ ልብ በሉ ለኛ ብላችሁ አይደለም፡ ለራሳችሁ ስትሉ እንጂ! አለዛ በማንኛውም ሰዐት እንደ ጓደኞቻችሁ ሁሉ አንገታችሁን እያነቁ፣ በራቁታችሁ ዱብዱብ እያስደረጓችሁ ቃሊቲ መውረዳቸሁ ነው፡፡ ከሀገር መኮብለልን አማራጭ አድርጋችሁት ከሆነ እንድትረሱት በዚህ አጋጣሚ እመክራችኋለሁ፡፡ አንድ የውስጥ ወዳጄ የሞያሌም ሆነ የኤርፖርት መንገድ በስውር ጥበቃ እንደታሸገ ሹክ ብሎኛል፡፡ የማሪያም መንገድ እንደሆነ በጁነይዲን ሳዶ አብቅቷል ፡፡ እናም ነግ በኔ ነውና ባላችሁበት የመንግስት ስልጣን ላይ ሆናችሁም ቢሆን “ህግ ይከበር ፣ህግ ይከበር፣ ፍትህ ናፈቀን፣ ድምፃችን ይሰማ፣ ኮሚቴዎቻችን ይፈቱ ፣ እነ እስክንድርና ርእዮት አለሙ ይፈቱ በሉ ”፡፡ እኛ ከመስጂዶቻችን ሆነን እንቀበላችኋለን፡፡ ህግ ይከበር፣ ኮሚቴዎቻችን ይፈቱ!

No comments:

Post a Comment