FREE ALL POLITICAL PRISONERS

FREE ALL POLITICAL PRISONERS
FREE ALL POLITICAL PRISONERS

Thursday, May 9, 2013

ወያኔ ሕወሃት ያልከበደው ኢትዮጵያዊ ማነው?


ይኸነው አንተሁነኝ
ግንቦት 8 2013
ሌቱ መሽቶ ይነጋል፤ ሳምንታት ወራት ዓመታት በፍጥነት መንጎዳቸውን አላቋረጡም፤ ክረምትና በጋ ይፈራረቃሉ፤ ወቅቶችም ማንም ሳይረብሻቸው ጊዜያቸውን ጠብቀው እያለፉ ነው፤ አፍጣጭ ገላማጭ ያለባቸውም ማዘዣ ጣቢያቸው ከእኛ አይደለምና። የክረምቱን ዝናብ ቀድሞ ለማምጣት፤ ፀሐይዋን ትንሽ ቀደም ወይም ዘግየት ብላ እንድትወጣና እንድትገባ ለማድረግ፤ የምንተነፍሰው አየር ባንድ አካባቢ ብቻ እንዲነፍስ ለማዘዝ፤ ብርሃን ብቻ እንዲሆን ወይም ጨልሞ እንዲቀር ማድረግ የሰው ልጅ የሚችል ቢሆን በተለይ እኛ ኢትጵያዊያን ምን ይውጠን ነበር? ለሀገርም ለሕዝብም ለታሪክም ለባህልም እንዴው ለምንም የማይጨነቅ ገዥ ሕወሃት ለተጫነብን።
“ሲለምኑ ማፈር ድሮ ቀረ” አሉ አድስ አበቤዎች። እንደው ግን ሰራተኛው፣ ገንዘብ አስገቢና መላሹ፣ የሙስና ዘዋሪውና አስዘዋሪው፣ ቀጣሪውና አባራሪው፣ ባለስልጣኑና ባለፋብሪካው፣ ኢንቨስተሩና ነጋዴው፣ አምራቹ አከፋፋዩና ቸርቻሪው፣ መሬት ሰጭና ነሽው፣ አራሹና አሳራሹ ባጠቃላይ ሁሉም በሕወሃትና የአገዛዙ አባላት ቁጥጥር ስር በሆነበት ሀገራችን “ሲለምኑ ማፈር ቀረ” ቢባል የሚያስደንቅ አይሆንም። ህግን አክብሮ በራስ መንገድ መስራትና እራስን መደጎም አይቻልማ፣ ከህሊናው ጋር ሆኖ ከወያኔ ጋር መስራት የመጨረሻ እጣው ከስራ መባረርና ልመና ነዋ። ድሮ እኮ መስራት የማይወድ ነው የሚለምነው፣ ያኔ እኮ ቀን ከሌት ደክሜ በላቤ በደሜ ሀገሬን ሕዝቤን እራሴንም ላሻሻል የሚለው ሳይሆን መድከምን እየጠላ መጎሳቆልን እየሸሸ በምላሱ ስንቱን አውለብልቦ እራሱም ተውለብልቦ በመሽሞነሞን ለመኖር የሚፈልገው ነበር የሚለምነው። ስለዚህም በዚያ ዘመን መለመን ያሳፍር ነበር። አሁን ግን ቀረ።
ለነገሩ እኔ ልመናን አነሳሁ እንጅ በወያኔ ዘመን ምን ያልቀረ አለ፤ ድሮ ጀግና ያስብሉ ያስከብሩ ስለነበሩት የሀገር አንድነትና የባንዲራ ክብር ባደባባይ ማውራት ቀርቶ ማሰብ በራሱ ባሸባሪነት እያስከሰሰ ዘብጥያ ማውረድ ከጀመረ ወዲህ ባንዳንድ ተቃዋሚ ፓርቲዎች ዘንድ በቀር መነገር ካቆመ ቆየ። ለስራ ለትምህርትና ለመሳሰሉት ካልሆነ በቀር ካገር መውጣት ማስገዘቱ ቢቀር ዘመድ አሰብስቦ ያሳዝንም የስለቅስም ነበር አሁን እቴ ሁሉ ቀርቷል። ወያኔ ከመጣ ምን ያልታየ አለ፤ አንድ ከተማ ነቅሎ የሚወጣ ያህል በየእለቱ ይሰደዳል። የአረብ አገር ጎረመሶች የግርፋት ስቃይና መከራ መለማመጃ ብንሆንም፣  ስቅላቱ ከፎቅ መወርወሩ በፈላ ውሃና ዘይት መተበሱ ሳያባራ ቢቀጥልም ሕወሃት ያማረረው ሕዝባችን ዛሬም ይሰደዳል። የሜድትራኒያንና የቀይ ባህር የአሳ ሲሳይ ብንሆንም በሕወት ብልሹ አገዛዝ ምክንያት ርሃብ የገረፈው መታረዝ የጠበሰው ማጣት ያንገበገበው ሕዝባችን አላቆመም ይሰደዳል። “ስደት ድሮ ቀረ”  በወኔ ሕወሃት ዘመን አይሰራም ባገዛዙ እንደባህል እየተወሰደ ያለ ነገር ነውና። ሀገሮች በኢኮኖሚ ሲያድጉና ሲሻሻሉ ባለሙያም ሆነ ጉልበት ሰራተኛ ከውጭ ያስገባሉ እንጅ የራሳቸውን አንቱ የተባሉ ባለሙያዎችና ሌሎች ሰራተኞችን አያባርሩም። ሕወሃት የተሻለ ፕሮፓጋንዳ ማዘጋጀት ሳይጠበቅበት አይቀርም።
“No free lunch” ይላሉ አሉ ፈረንጆች። ምንም ነገር በነጻ አታገኝም፤ አንድ ነገር ለማግኘት መስራት አለብህ መድከም አለብህ ለማለት ይመስላል አባባሉ። በኢትዮጵያችንና በወያኔ አገዛዝ ግን ይህን የሚሉት የአስፋልት ዳር ነጋዴዎች ናቸው። ከሚነፍሰው ንፋስ ጋር ከግራ ከቀኝ የሚመጣውን የተዘበራረቀ ሽታ እየማጉ፣ የሙሉ ቀን የፀሐይ ግለቱን ተቋቁመው፣ አቧራ ብርድና ዝናቡን ታግሰው ትነስም ትብዛ የዕለት ጉሮሯቸውን ለመድፈን፣ ቁርስ ያልበሉ ልጆቻቸውን ምሳ ወይም እራት አጉርሰው ለማደር ደፋ ቀና ከማለት በተጨማሪ ያችን የሚውሉባትን የአስፋልት ጥግ ቦታ ለማግኘት ወያኔ መሆን እንደ መስፈርት ሲቀርብላቸው “No free lunch” ቢሉ ችግሩ ያለው ሳይፈልጉ ከተጫነባቸው ሕወሃት እንጅ ከእሳቸው አይደለምና አያስፈርድም። የሚደንቀው ግን ከዚህ ሁሉም በሗላ ወያኔ ሕወሃት ከልክ በላይ የስራ እድል የከፈትኩ፣ የኢትዮጵያዊያንን በተለይም የሴቶችን መብት ያስጠበቅኩ እኔ ነኝ እያለ መዘባረቁ ነው።
ለድሮው ክቡር የነበሩት ገዳማትና መስጊዶች ሳይቀሩ በወያኔ ዘመን ተደፍረዋል።  ሳንፈልግ የወደቀብን ሕወሃት ያልከበደው ኢትዮጵያዊ ወገን የለም። ሕወሃትም በአገዛዙ ያላሸበረው የህብረተሰብ ክፍል ያልቀወጠው አካባቢ ተፈልጎ አይገኝም። ለባለራዕዩ ሬሳ ሽኝት ኮልኮሎ ያቀረባቸው የጎዳና ተዳዳሪዎችና የኔቢጤዎች ሳይቀሩ እንደ ነጋዴ መጋዘን ካርቱን አንዴ በዚያ በኩል ሌላ ጊዜ በዚህ እየተባሉ ይዋከባሉ። እነዚህ ሁሉ ኢትዮጵያዊያን መሆናቸውን ሕወሃት ማስታወስ አይፈልግም። እርዳታ መስጠትም አያስብም። ያቅም ማነስ ነው እንዳንል ደግሞ ሌሎች ወገኖች ለረዷቸው ላጎረሷቸው ሕወሃት ሲያውክ ማስተዋላችን ለምን ይሆን? ይህ እጣ ለቆሸ ሰፈር ገንዳ አራጆችም አልቀረላቸውም። ከሌሎች የአዲስ አበባ ክፍሎች ያገለገሉ እቃዎችንና የሆቴል ትርፍ ምግቦችን የያዙ ገንዳዎችን ከበው የሚያወራርዱት የቆሽ ሰፈር ገንዳ አራጆች ከወያኔ የሰፈር ጥበቃና ከፌደራል ፖሊስ የሚደርስባቸው ወከባ ቀላል አይደለም።
በእርግጥ ከነኝህ ገንዳዎች የሚገኝ ትርፍ ምግብ ለምግብነት የሚውል ሆኖ አልነበርም፤ ግን ምን ይደረግ ሰው የወደቀ ምግብ ይቅርና እራሱን ይበላል።  ሕዝባችን እኮ እራሱን በልቶ በልቶ ጨርሶ በጠኔና በክሳት እየተንጠራወዘ ነው ያለው። ከቁጥር ስላልጎደለ አልተጮኸም እንጅ ሞቷል ተብሎ ሊለቀስለት የሚገባው የማህበረሰባችን ክፍል ጥቂት አይደለም። ይህ ሁሉ በግፍ በወደቀብን ሕወሃት እየተሰፈረልን ያለ መከራ ነው። ግን ለምን? አንዳንዱ የሕወሃት ሰው ከትግራይ በመጣ በነጋታው የውስጥ ሱሪ እንኳ ለምንና እንዴት ማድረግ እንዳለበት ገና በቅጡ ሳያውቅ በዘረኛ ባለስልጣን ወገኑ በተሰጠ ቀጭን ትእዛዝ በሽዎች የሚቆጠር ኩንታል ሲሚንቶ ወይም ስኳር ያለ ወረፋ እንዲወስድ ይፈቀድለትና የፈቃድ ደብዳቤዋን ብቻ ለመርካቶ ነጋዴ በመሸጥ ፋብሪካዎቹን እንኳ ሳያይ ባንድ ቀን ባለ ሚሊዮን ይሆናል። ሌላው ደግሞ ከሊስትሮነት ስራው፣ ከቆሸ ሰፈር ትርፍ ምግብ ለቀማው፣ ከአስፋልት ዳር ልመናና ጎዳና ተዳዳሪነት ሲባረርና ሲዋከብ እናያለን። ለምን ብለን መጠየቅ የለብንም? ከዚህ የባሰ የመብት መደፈርስ አለ እንዴ? ሁላችንም ልናስተውል ይገባናል።
ችግሮች እንዲቆሙ የተመኘንባቸው ወይም የሞከርንባቸው ዘመናት ገና ያኔ ያኔ አልፈዋል። ወያኔ ግን በችግር ላይ ችግር በመከራ ላይ መከራ ደራረበብን እንጅ መፍትሄ አላገኘንም።  “እምብዛም ዝምታ ለበግም አልበጃት ሃምሳ ራሷን ሆና አንድ ነብር ፈጃት” ነው ብሂሉ። እኛ ለመብታችን መከበር እስቃልቆምን ድረስ ሕወሃት በየጊዜው ሌሎች አዳዲስ ምክንያቶችን እየፈጠረ ለማሰር ለማሰደድና ለመግደል አይቦዝንም። በፊት በፊት በ ኦነግ፣ በግንቦት 7፣ በአሸባሪነት፣ በአልቃይዳና በሌሎችም እያመካኘ የስርና ያንገላታ የነበረው ሕወሃት አሁን ደግሞ የግንቦት 7 ሕዝባዊ ሃይል መመስረትን ተከትሎና በዚሁ ሃይል እያመካኘ ወጣቱን እያሰረና እያሰደደ መሆኑ ይሰማል። እና እኛስ እስከ መቼ ነው እንደተገረፍንና እንደተሰደድን የምንቀጥለው? አንተም ከማባረር አልተመለስክ እኔም ሁሌ መባረር መሮጥ ሰለቸኝ የምንለውስ ዛሬ ሊሆን ካልቻለ ለመቼና ለእንዴት ያለ ጊዜ ይቆጠባል?
ህወሃት ከበቂ በላይ የስቃይና የጥፋት ማስጠንቀቂያዎችን ሰጥቶናል። የግድ በግል በራሳችን ለይ ደርሶ ማየት እንሻለን እንዴ? ለዚያውም ባለፉት የሕወሃት ያገዛዝ ዘመናት ችግር ያልዳሰሰው ቤት ካለ መለቴ ነው። ይህን የጥፋት ሃይል አንድ ሆነን ቆመን መመከት ካልቻልን ዝምታን ከመረጥናና ወያኔ ባዘጋጀልን ወጥመድ ተጠልፈን ከገባን ኢትዮጵያ የምትባልን ሀገርም ሆነ የሕዝባችንን ከብር እንደገና ለመመለስ በጣም አስቸጋሪ ነው የሚሆነው። “ለሁሉም ጊዜ አለው” ሀገርንና ሕዝብን ለማዳንም ለኛ ለኢትዮጵያዊያን ረፍዷል ካልተባለ ጊዜው አሁን ነው። አንድ ላይ በመተባበር በውስጥ ሽኩቻ በአመራር ብቃት ማነስ በሕዝብ በመተፋት እና መጠላት የዘመመውን ሕወሃት ገፍተን እንጣለው።

No comments:

Post a Comment