FREE ALL POLITICAL PRISONERS

FREE ALL POLITICAL PRISONERS
FREE ALL POLITICAL PRISONERS

Monday, July 1, 2013

ከእሁድ እስከ እሁድ

(የሳምንቱ አጫጭር ዜናዎች)
SOMALIA MILITIA


አልሸባብ በሶማሊያ ተሽመደመደ፤ ሼኽ ዳሒር ሃዌስ ተይዘዋል፤
አሸባሪነትን በመዋጋት ሲሞዳሞዱ የቆዩት ኢትዮጵያና አሜሪካ ወዴት ያመሩ ይሆን?
የአልሸባብ መሪዎች በራሳቸው ተዋጊዎች መገደላቸው ተሰማ። ከተገደሉት መካከል አንደኛው ያሉበትን ለጠቆመና ላጋለጠ አምስት ሚሊዮን ዶላር ጉርሻ እንደሚሰጥ የታወጀባቸው ነበር። የቪኦኤ የአማርኛው ክፍል በዘገበው ዜና መሰረት አልሸባብ በሶማሊያ እየተንኮታኮተ የመክሰም ደረጃ ላይ መድረሱን አመላካች ይመስላል።
አብዱልአዚዝ አቡ ሙስ አብ ባሠራጨው የድምፅ መልዕክት የሙጃሕዲኑ ታጣቂዎች በመካከላቸው መከፋፈልን ለመፍጠር ይጥሩ በነበሩ አባሎቻቸው ላይ ዘመቻ ካካሄዱ በኋላ የተወሰኑትን በቁጥጥር  ሲያውል፣ እጅ ለመስጠት አሻፈረኝ ያሉ ነበሩ ብሏል። “ሁለቱ እጃቸውን እንዲሰጡ ሲጠየቁ አሻፈረን ብለው አንገራገሩ፣ በተኩስ መካከል ተገደሉ፤ አምላክ ነፍሳቸውን ይማርና በገነት ያስቀምጥ፡፡ ሃሣቡ እነርሱን ለመግደል አልነበረም፡፡ በቁጥጥር ሥር አውለን እሥልምና ችሎት ፊት ልናቀርባቸው ነበር” ሲል እስልምና ችሎት ፊት ሳይቀርቡ በተኩስ ልውውጡ ወቅት መገደላቸው እንዳሳዘነው መግለጹን የቪኦኤ ዜና ያስረዳል።
ሰዎቹ የተገደሉት ከሞቃዲሾ 350 ኪ.ሜ በስተደቡብ በምትገኝ ብራቫ የምትባል ከተማ ውስጥ እንደሆነ ታውቋል፡፡ የተገደሉት ሰዎች እነማን እንደሆኑ የአል-ሻባብ ቃል አቀባይ አልተናገረም፡፡ ይሁን እንጁ የቪኦኤ ሶማሊኛ አገልግሎት የተለያዩ ቅርበት ያላቸው ምንጮችን አነጋግሮ በተለያዩ ስም የሚጠሩት የአልሸባብ አመራር መሞታቸውን አመልክቷል። በዚሁ መሰረት ኢብራሂም ሃጂ ጃማ ፣ ኢብራሂም አል-አፍጋን ፣ በተቀጥያ መጠሪያው አቡ ባካር አል-ዛይሊዪ እና ሼኽ አብዲሃሚድ ሃሺ ኦልሃዬ ወይም በቅፅል ስም ሞዐሊም ቡርሃን የተገደሉ መሆናቸውን አረጋግጧል፡፡
መሪዎቹ የተገደሉት የዛሬ አሥር ቀን ሰኔ 12 መሆኑንም የቪኦኤ ምንጮችን የጠቀሰው የሶማሊኛ አገልግሎት ዘገባ አመልክቷል፡፡የአል-ሻባብ ምንጮች እንደሚሉት አል-አፍጋን የተገደለው ከመስጂስ እየወጣ ሳለ በተተኮሰበት ተከታታይ ጥይት ሲሆን ሙዐሊም ቡርሃን የተገደለው ከቤቱ ተይዞ ከተወሰደ በኋላ ነው፡፡
ይህ አጋጣሚ ከተፈጠረ ከሁለት ቀናት በኋላ ለተገደሉት ሁለት ሰዎች የቅርብ ወዳጅ እንደነበረ የሚነገረው ዋነኛው የአል-ሻባብ መሪ ሼኽ ሐሰን ዳሂር አዌይስ ከአካባቢው በጀልባ በማምለጥ ማዕከላዊ ሶማሊያ ውስጥ ተይዞ እጁ ለመንግሥት አስረክቧል። ከተገደሉት አንዱ ኢብራሂም አል-አፍጋን በአል-ሻባብ ውስጥ በርካታ የሥልጣን ቦታዎች የነበሩት ሲሆን የቡድኑ ምክትል መሪ፣ የገንዘብ መምሪያው ኃላፊና የኪስማዮ ገዥ ሆኖ ሠርቷል፡፡ ተይዘው ለፍርድ እንዲቀርቡ ያሉበትን መረጃ ለሚሰጥ በእያንዳንዳቸው ራስ የአምስት ሚሊዮን ዶላር ጉርሻ እንደምትሰጥ ዩናይትድ ስቴትስ ማስታወቂያ ካወጣችባቸው ሰባት የአል-ሻባብ መሪዎች አል-አፍጋን አንዱ ነው፡፡
አል-አፍጋን ዩናይትድ ስቴትስ፣ ቨርጂንያ ውስጥ ይኖር የነበረ ሲሆን እአአ በ1980ዎቹ ውስጥ ከሙጃሕዲን ጎን ተሰልፎ ለመዋጋት ወደ አፍጋኒስታን መሄዱንና በ1991 ዓ.ም የሶማሊያ ማዕከላዊ መንግሥት ሲወድቅና ሥርዓተ-መንግሥቱ ሲፈራርስ እጅግ የከፋ ዓይነት ጂሃድ ወደ ሶማሊያ ማስገባቱና ሶማሊያ ውስጥ የመጀመሪያውን የጂሃድ ማሠልጠኛ ሠፈር ማቋቋሙን ዘገባዎች ይጠቁማሉ፡፡
አል-አፍጋን ከአል-ቃይዳው መሥራችና መሪ ኦሣማ ቢን ላደን ጋርም ብዙ ግንኙነቶች እና ንግግሮች እንደነበሩት ቢን ላደን በ2011 ዓ.ም ከተገደለ በኋላ ሲናገር ድምጹ ይሰማ እንደነበር ታውቋል፡፡ ሌላው ተገዳይ ሙአሊም ቡርሃን አል-ሻባብ ውስጥ ዋነኛ የሚባል የሃይማኖት ሊቅ እና የቡድኑ የመማክርት ምክር ቤት አባል እንደነበረ ተገልጿል፡፡
የአልሻባብ አመራር በእንዲህ ዓይነት ሁኔታ ሲዳከም፤ ባለፉት በርካታ ዓመታት ኢህአዴግ የአሜሪካ ወዳጅ ነኝ በማለት እንዲሁም አሜሪካም “ኢትዮጵያ የምስራቅ አፍሪካ ሸሪካችን ነች” በማለት ሲሞዳሞዱበት የነበረው አጀንዳ “በቀጣናው አሸባሪዎችን መዋጋት የሚል ነበር”፡፡ በተለይም እነ አቶ መለስ አልሻባብ የአልቃይዳ ስሪት ነው፤ አሸባሪነትን እንዋጋለን በማለት በአልሻባብ ስም የፈለጉትን የፖለቲካ ጥቅም ሲፈጽሙ ኖረዋል፡፡ ታዲያ ይህ የአልሻባብ መዳከም በዕቅድ የተከናወነ ይሆን? ወይስ የተበላበት ዕቁብ ስለሆነ ሌላ የታሰበ አዲስ ፕሮጄክት አለ? አልሻባብ ቁጥር 2 ወይም “ጸረ አሸባሪነትን መዋጋት ቁጥር 2”? ወይስ ፕሬዚዳንት ኦባማ በአፍሪካ ጉብኝታቸው ከምስራቅ አፍሪካ ኢትዮጵያን አለመምረጣቸው ጋር ተዳምሮ አሜሪካ ለምስራቅ አፍሪካ ድራማ አዲስ የፖለቲካ ጽፈ ተውኔት አዘጋጅታ ይሆን? መቆየት ደጉ ብዙ ያሳየናል!
እንጀራ ብሔራዊ ደረጃ ወጣለት
አንዳንዴ ለገበያ የሚቀርበው እንጀራ ለበሽታ የሚዳርግ ነው
የጤፍ እንጀራ በኢትዮጵያ ደረጃዎች ኤጀንሲ ብሔራዊ ደረጃ እንደወጣለት ታወቀ። ፋና ኤጀንሲውን በመጥቀስ እንዳመለከተው ጤፍ ለመጀመሪያ ጊዜ ብሔራዊ ደረጃ ወጥቶለት መጽደቁን አመልክቷል። ዜናው ደረጃ የወጣለት ጤፍ ምን መስፈርቶች እንደተቀመጡለት አላብራራም። በኢትዮጵያ የጤፍ እንጀራ ወደ ውጪ በመላክ ንግድ የከበሩ ነጋዴዎች በብሔራዊ ደረጃ በጸደቀው አዲሱ የጤፍ ደረጃ መሰረት አዘጋጅተው ኤክስፖርት መላክ እንዳለባቸው የሚያስገድድ ሁኔታ ስለመቀመጡም የተገለጸ ነገር የለም።
በአውሮፓና አሜሪካ በተለያዩ ሱፐር ማርኬቶች፣ የግል የገበያ ሱቆችና የቤንዚን ማደያዎች ገበያ ላይ የሚገኘው የጤፍ እንጀራ injeraአንዳንድ ጊዜ ደረጃውን ያልጠበቀ፣ የሚኮመጥጥ፣ አይን የሌለው፣ የሚፈረካከስና ወዝ የሌለው እንጀራ የሚቀርብበት አጋጣሚ በርካታ ነው። በላስቲክ ታሽጎ ከፍሪጅ እየወጣ የሚሸጠው እንጀራ ጉዱ የሚታወቀው ቤት ከገባ በኋላ በመሆኑ በርካታ ተጠቃሚዎች እንደሚማረሩ ለማወቅ ችለናል።
አንድ እንጀራ እስከ ሰባ ብር በመግዛት የሚመገቡ የስካንዲቪያን አገራት ነዋሪዎች እንጀራ መመገብ  ቢወዱም ገበያው ላይ አንዳንዴ የሚቀርበው እንጀራ ለጨጓራ ችግር የሚዳርግ እንደሆነ ተናግረዋል። አዲስ ብሔራዊ ደረጃ ያወጣው ኤጀንሲ ህግ ማውጣቱን ብቻ ሳይሆን በተቀመጠው መስፈርት መሰረት ቁጥጥር ሊያደርግ እንደሚገባ ጠቁመዋል። እንጀራ ወደ ውጪ ለመላክ ፈቃድ ያወጡ ነጋዴዎች ህጉን አክብረው እንዲሰሩ የማስገደድ ተግባሩን እንዲገፋበትም ጠቁመዋል። ችግር ካጋጠማቸውም ማስረጃ በመያዝ ቅሬታቸውን ማሳወቅ የሚችሉበት አግባብ እንዲዘረጋላቸው ሃሳብ ያቀረቡም አሉ።
“(ከኢትዮጵያ ጋር) በፕሬዚዳንት ደረጃ ግንኙነታችንን ማጉላት አንፈልግም”
ከመካከለኛው አፍሪካ የአሜሪካንን ቀልብ የሚስብ አገር የለም። የደቡብ አፍሪካ መመረጥ ካላት ኢኮኖሚና ፖለቲካዊ ሚናዋ አንጻር ለጥያቄ የሚቀርብ አይደለም ያሉት ዴቪድ ሺን ከምስራቅ አፍሪካ አስር አገሮች መካከል አራቱን በመምረጥ የግል አስተያየታቸውን አቅርበዋል። ሴኔጋል የተመረጠችው ፈረንሳይኛ ተናጋሪና የምዕራብ አፍሪካ አገር በመሆኗ ነው።
የቪኦኤው ሰለሞን አባተ ያነጋገራቸው በኢትዮጵያ የአሜሪካ የቀድሞ አምባሳደር ዴቪድ ሺን ስለ ባራክ ኦባማ የአፍሪካ ጉብኝት ሲናገሩ ኬኒያን አንስተው ነበር። የፕሬዚዳንት ባራክ ኦባማ አባት ኬንያዊ ቢሆኑም ኦባማ ኬንያን የጉብኝታቸው አካል ያላደረጉት አዲሱ ፕሬዚዳንትና ምክትላቸው በዓለም አቀፉ ፍርድ ቤት ችሎት የሚፈለጉ በመሆናቸው እንደሆነ አስታውቀዋል። በወንጀል የሚፈለጉ መሪዎች ባሉበት አገር የአሜሪካ ፕሬዚዳንት ጉብኝት አያደርግም በማለት ተናግረዋል።
o in africaዩጋንዳ ፣ ኢትዮጵያና ታንዛንያን ለንጽጽር ያቀረቡት ዶ/ር ሺን ሶስቱም አገሮች አሜሪካ የምታስቀምጠውን መለኪያ አያሟሉም። በታንዛኒያ ግን የፕሬዚዳንቱ የስልጣን ጊዜ ባግባቡ ተገድቦ ተቀምጧል። የአመራር ለውጥ ያካሂዳሉ። ጎልቶ የሚወጣ የዴሞክራሲና የሰብአዊ መብት አያያዝ ጉድለት አይታይም ብለዋል። በዚህም የተነሳ ታንዛኒያ የተሻለች አገር ተብላ መመረጧን አመልክተዋል።
ለአፍሪካ ህብረት 50ኛ ዓመት በዓል ውጭ ጉዳይ ሚ/ር ጆን ኬሪ አዲስ አበባ መሄዳቸውንና ከመንግስት ክፍተኛ ባለስልጣናት ጋር መነጋገራቸውን ያወሱት ሺን፣ ኢትዮጵያ በኦባማ ጉብኝት እቅድ ውስጥ አለመሆኗ የማግለል ጉዳይ እንዳልሆነ አመልክተዋል። አሜሪካ ከኢትዮጵያ ጋር ያላትን ግንኙነት የመያዝ ፍላጎት  እንዳላት የጠቆሙት ሺን “ይህን ግንኙነት በፕሬዚዳንት ግንኙነት ደረጃ ማጉላት አንፈልግም” የሚል ማብራሪያ ሰጥተዋል። የቻይና ፕሬዚዳንት በቅርቡ ሶስት የአፍሪካ አገሮችን ሲጎበኙ ኢትዮጵያን አለመጎብኘታቸውን አንስተዋል። በምስራቅ አፍሪካ ፖለቲካ ጉዳዮች በቂ ግንዛቤና ጥናት ማካሄዳቸው የሚታወቀው ሺን “አሜሪካ ግንኙነቱን በፕሬዚዳንት ደረጃ ማጉላት አትፈልግም” ያሉበትን ምክንያት አላብራሩም።
አበባ እርሻ የሚሰሩ የኬሚካል ጉዳተኞች በርክተዋል
የውጪ ምንዛሬ ገቢው 40% ቀነሰ
በከፍተኛ ደረጃ የእርሻ መሬቶችን ወደ አበባ እርሻ ማሳ ለሚቀይሩ ባለሃብቶች በመሸጡ ተቃውሞ የሚሰነዘርበት የኢንቨስትመንት ዘርፍ የዜጎችን ህይወት እየተፈታተነ ነው። በአነስተኛ ክፍያ በአበባ እርሻዎች ውስጥ ተቀጥረው የሚሰሩ ወገኖች ከኬሚካል ጋር በተያያዘ እየደረሰባቸው ያለው የጤና መጓደል አስጊ እንደሆነ አሁንም ድረስ ትኩረት እንደሚፈልግ እየተነገረ ነው።
ለገቢው ልዩ ትኩረት የሚሰጠው መንግስት በበጀት ዓመቱ ከዘርፉ የጠበቀውን ገቢ አለመግኘቱን ተጠቁሟል። ከ2 ነጥብ 1 ቢሊዮን በላይ የአበባ ዘንግ፣ 114ሺ ቶን አትክልት እና 13ሺ ቶን ፍራፍሬ ባለፉት 11 ወራት ወደ ተለያዩ ሀገራት ቢላክም flower farm eesመጠኑ ከእቅድ በታች እንደሆነ ተገልጾዋል። ፋና የኢትዮጵያ  ሆርቲካልቸር ልማት ኤጄንሲን ጠቅሶ እንደዘገበው ወደ ውጪ ከተላኩት የአትክልት ምርቶች ከ212 ሚሊዮን የአሜሪካን ዶላር በላይ ገቢ ተገኝቷል። ገቢው ከእቅዱ ስልሳ በመቶ ብቻ ነው። ኤጀንሲው ለገቢው መቀነስ የአለም ኢኮኖሚ መቀዛቀዝና በአለም አቀፍ ደረጃ የአየር ሁኔታ መለዋወጥ እንደ ምክንያት አቅርቧል።
ከአበባ እርሻ ጋር በተያያዘ በርካታ ዜጎች ለበሽታ መዳረጋቸውና በቂ የጤና ዋስትና እንደሌላቸው በተደጋጋሚ የሚገለጽ ችግር ነው። በአበባ ማበልጸጊያ ድንኳን ውስጥ የሚሰሩ ዜጎች ለኬሚካል ብክለት መጋለጣቸው የከፋ ችግር ከመሆኑም በላይ ከእርሻዎቹ የሚወጡ ፍሳሾች ወራጅ ውሃና ወንዝ ጋር በመቀላቀል አደጋ እያስከተለ ነው። ከዚህም በላይ የአበባ እርሻዎች ከፍተኛ ሃይል ያለው መርዝ ስለሚጠቀሙ መሬቱ ለወደፊቱ እህል እንደማያበቅል ባለሙያዎች በጥናት አረጋግጠው ያቀረቡበት የማይመከር ኢንቨስትመንት እንደሆነ መጠቆሙ አይዘነጋም።
“ለቤተሰቦቼ እቃ ለመላክ ስጠይቅ ሃላፊነት አንወስድም ተባልኩ”
የፖስታ አገልግሎት ፖስታ ይጥላል፣ ያበላሻል፣ ያልተባለው ቦታ ይልካል
“ለወንድሜ ሞባይል ለመላክ ፖስታ ቤት ስጠይቅ የምልክበትን አገር ጠየቁኝ። ኢትዮጵያ እንደሆነ ነገርኳቸው። ኢትዮጵያ ከሆነ ለሚላከው ዕቃ ሃላፊነት አንወስድም አሉኝ” ስትል ለጎልጉል ግራ መጋባቷል በመግለጽ አውሮፓ እንደምትኖር የገለጸች ኢትዮጵያዊ ይህንን ጥያቄ የሰነዘረቸው ከወር በፊት ነበር።
በተመሳሳይ ፖስታ የሚጠቀሙ ወገኖች ችግር እንደሚገጥማቸው በተደጋጋሚ ሲናገሩ መስማት የተለመደ ነው። የላኩት ጥቅል postየጠፋባቸውና የተበላሸባቸው ያማርራሉ። ሰኔ 22 ቀን 2005 ዓም ፋና ይፋ ያደረገው ዜና ይህንኑ ችግር ወለል አድርጎ የሚያሳይ ሆኖ ተገኝቷል።
የኢትዮጵያ ፖስታ ድርጅት የደብዳቤና የጥቅል መልእክት አገልግሎት ደህንነትን በመጠበቅ በኩል ክፍተቶች እንዳሉበት የገለጸው ፋና ዜናውን ያገኘው በህዝብ ተወካዮች ምክር ቤት የሳይንስና ቴክኖሎጂ  ጉዳዮች ቋሚ ኮሚቴ የኢትዮጵያ ፖስታ አገልግሎት ድርጅትን የአስራ አንድ ወራት እቅድ አፈፃፀምን በገመገመበት ወቅት እንደሆነ አመልክቷል።
ቋሚ ኮሚቴው እንዳለው ከሆነ በድርጅቱ የሚበላሹ፣ የሚጠፉና በተሳሳተ አድራሻ የሚላኩ መልእክቶች እየበዙ መጥተዋል፣ በዚህም ምክንያት የተገልጋዮች ቅሬታም እየጨመረ ነው። ችግሩን ያደመጠው ቋሚ ኮሚቴው ይህ እንዲስተካከልና በቀጣይ በዘርፉ የሚታየው ተገቢ ያልሆነ አሰራር እንዲሻሻልና አገልገሎቱ የደንበኞችን ፍላጎትን በሚያረካ መልኩ እንዲሰጥ ማሳሰቡን ፋና አስታውቋል።
የሰሜን ተራሮች ፓርክ ከዓለም ቅርስነት እንዳይሰረዝ ስጋት አለ
የቱሪዝም ሚኒስትር አደጋውን ለመከላከል “አውደ ርዕይ አዘጋጀሁ” ይላል
የሰሜን ተራሮች ብሔራዊ ፓርክ ከአያያዝ ጉድለትና መንግስት በቂ ትኩረት ባለመስጠቱ አደጋ ላይ እንደወደቀ መገለጽ የጀመረው ከዓመታት በፊት ነው። ፓርኩ በከፍተኛ ችግር ውስጥ እንደሚገኝ በመጥቀስ ሰራተኞች ሳይቀሩ በየሚዲያው መንግስትን ተማጽነዋል። ለፌደራል፣ ለክልሉ መንግስትና ባለስልጣናት  “ከአገር ቤት የተሰረቀ ሃውልት ለማስመለስ ከሚሰጠው ትኩረት ሩቡን ያህል እንኳ ለሌሎችም ቅርሶች ትኩረት ሊሰጥ ይገባል። የሰሜን ተራሮች ድንቅ ፓርክ እየሞተ ነው” በሚል ጥቅል መልክት በተደጋጋሚ ከተለያዩ ወገኖች ሲሰነዘር ቆይቷል።simen
የባህልና ቱሪዝም ሚኒስቴር የሰሜን ተራሮች ብሄራዊ ፓርክን ከተጋረጠበት አደጋ ለመከላከል የተለያዩ ስራዎችን እያተከናወነ መሆኑንን ያመለከተው ፋና ብሮድካስቲንግ  “የሰሜን ተራሮች ብሄራዊ ፓርክ ዩኔስኮ በቅርስነት ከመዘገባቸው ቅርሶች አንዱ ሲሆን በአሁኑ ጊዜ ግን ፓርኩ ላይ እየደረሰ ባለው ጉዳት አሳሳቢ ደረጃ ላይ ደርሷል። ይህን ተከትሎም ፓርኩን ከዓለም ቅርስነት የመሰረዝ አደጋ ውስጥ ገብቶል እየተባለ ነው” በማለት መርዶ ያዘለ ዜና አስነብቧል።
ቅርሱ የተጋረጠበትን የመሰረዝ አደጋ ለማስቀረት የባህልና ቱሪዝም ሚኒስቴር ስለፓርኩ አያያዝ ለሚመለከታቸው አካላት ግንዛቤ ለማስጨበጥ አውደ ርእዩን ማዘጋጀቱን ፋና ገልጿል። በሚኒስቴሩ የአለም አቀፍ ግነኙነት ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተር አቶ አወቀ ጤናው የተጠቀሱበት ዜና ለሶስት ቀናት በሚቆየው በዚሁ አውደ ርዕይ ላይ ፓርኩን በዘላቂነት ለመታደግ የሚያስችሉ የተለያዩ ገብዓቶች እና ድጋፍ ይሰበሰባል ተብሎ እንደሚጠበቅ አመልክቷል።

No comments:

Post a Comment