FREE ALL POLITICAL PRISONERS

FREE ALL POLITICAL PRISONERS
FREE ALL POLITICAL PRISONERS

Saturday, July 20, 2013

ሳውዲ አረቢያ በኢትዮጵያ የቤት ሰራተኞች ላይ የጣለችው እገዳ እና አንድምታው


ከነብዩ ሲራክ፣ ሳዑዲ አረብያ
በማለዳው ከእንቅልፍ ስነቃ ለዛሬው ለማለዳ ወግ ቅኝቴን ሁለት ሰሞነኛ ትኩስ ወጎች ከፊ ለፊቴ ገጭ ብለው ጠበቁኝ! አንዱ ሰሞነኛ ወግ ስልጣኔ ዘመነኛ የመገናኛ ዘዴዎችን ማግኘት የታደለው የሃገሬ ሰው አይኑን አፍጦ በማህበራዊ ገጾች እና በተለያዩ የኢንተር ኔት ድህረ ገጽ ስር ባሉ የመረጃ መረቦች ሲከታትለው የሰነበተው የጁሃር መሃመድ ሃይማኖትና ዘርን ቀላቅሎ የተናገረበት አሳፋሪ፣ አሳዛኝ እና አነታራኪ ንግግር ነው። ሁለተኛው ሳውዲ ነዋሪውን የሃገሬ ሰው ግራ ያስደነገጠ ያስደሰተው ሲሆን ጉዳዩም የሳውዲ መንግስት የቤት ሰራተኞች ከኢትዮጵያ እንዳይመጡ ጊዜያዊ እገዳ የጣለበት ጉዳይ ነው! ሁለቱንም ሰሞነኛ ጉዳዮች መነጋገሪያ ሆነው ሰንበተዋልና መረጥኳቸው! ያም ቢሆንም የማተኩረው ባንዱ ርዕስ ላይ ብቻ ይሆናል! እናም የዛሬ ወግ ትኩረቴን በአያሌው ስለሳበውና ሚዛንም ወደደፋብኝ የሳውዲ እገዳ ጉዳይ ላቅና…
የእገዳው ሰበብ …
Saudi Arabia, Nebyu Sirakበያዝነው ወር ብቻ ሁለት ህጻናት በሳውዲ ዋና ከተማ ውስጥ በኢትዮጵያውያን የቤት ሰራተኞች የመገደላቸውን ዜና ተከትሎ የሳውዲ መንግስት ከኢትዮጵያ የቤት ሰራተኛ ማስመጣቱን የማስቆም ፍላጎት እንደለ ጭምጭምታ የሰማሁት ከሁለት ቀናት በፊት ቢሆንም የመታገዱን እርግጠኛነት የሰማሁት ግን ባሳለፍነው ረቡዕ አመሻሹ ላይ ነበር ። ይህንን ለማረጋገጥ ወደ ጅዳ ቆንስል ሃላፊ ደጋግሜ ብደውልም ሃላፊው ስልካቸውን አያነሱም ። ውሎ አደረና የደረሰኝ የጓሮው ሁነኛ ምንጭ እውነት ሆኖ ትናንት ሃሙስ ማለዳ እገዳው በይፋ ታወቀ! በተደበላለቀ ስሜት ተናጥኩ ፣ ሌላው ሁሉ ቢቀር የብዙውን ድሃ ወገን በልቶ የማደር ህልም እውን ማድግ የሚቻልበት መልካሙን እድል መጠቀም አለመቻላችን በቁጭት አደበነኝ። በሌላ ጎኑ በቤት ሰራተኞች ዙሪያ መንግስት ትኩረት ባለመስጠቱ በኮንትራት ሰራተኛ ስም ህጋዊ የሳውዲ እና የኢትዮጵያ መንግስት ስምምነት አለመኖርን፣በዜጎች መብት ጥበቃ የተሟላ ስራ በመንግስታችን በኩል ያለመፈጸሙ ህጸጽ እና የምሰማው፣የማየው የወገን ስቃይና በደል አውጥቸ አውርጀ “በእገዳውን ቢያንስ እረፍት ይገኛል!” ስል የእፎይታ ደስታ ተሰማኝ!
መረጃ ለማቀበል ካለኝ ፍላጎት አንጻር በእገዳው አንድምታ ዙሪያ ገብ መረጃዎችን ለመሰባሰብ በጾምና በጸሎት ለፈጣሪው በሚገዛው ነዋሪ መካከል ተረጋግቼ መረጃ ስብሰባየን ገፋሁበት! ራስ ሰንጠቆ ከሚገባው ከጅዳ የበጋ ሙቀት ጋር የቀይ ባህር ወበቅ ከጭንቀት የማይሸሸውን የስደተኛ ነፍስ ይፈትናል ።
ስለ ሳውዲ መንግስት እገዳ መረጃ መሰብሰቡ ባያደክመኝም አንዱን አንዱን ስል የተኛሁት ሊነጋጋ ቢሆንም በማለዳው ከአልጋየ ሳልወርድ በማቀርበው ወግ ዙሪያ ማብሰልሰል ይዣለሁ… ሁሌም እንደማደርገው የማለዳ ወጌን ከመጀመሬ እና የወጌን ሁነኛ ርዕስ ከመምረጤ አስቀድሞ የመረጃ ግብአት ይሆኑኝ ዘንድ ቅኝቴን የጀመርኩት እለታዊ ጋዜጦችን በመዳሰስ ነበር። የአረቡ አለም ዋና ዋና የሚባሉትን መገናኛ ብዙሃን ድህረ ገጾ እጎበኛቸዋለሁ። የመካከለኛ ምስራቅን ፖለቲካው አድፍጣ የምትዘውረው ሃገር የሳውዲ አረቢያ ጋዜጦች ከቅርብ አመታት ወዲህ ማናቸውንም አይንት ጽንፈኝነት ከመቃዎም ጀመሮ ድሮ ድሮ ሊነኩ ቀርቶ ሊወሱ አዳጋ ያስከትላሉ በሚባሉ የመንግስት ተቋማት ይተቻሉ፣ መገናኛ ብዙሃኑ ከዚህ አልፈው ሄደው ከመንግስት እኩል ባይባልም ከፍ ያለ ቦታ ያላቸው የሃይማኖቱ ተቋማት አሰራርና በአካሔዱ ላይ ነጻ አስተያየት ጥቆማዎችን ያቀርባሉ። ከመንግስት ተቋማትን ዝርክርክነት እስከ አካባቢ አረብ ሃገራትን የፖለቲካ አሰላለፍ ዘልቀው የሚተቹ የፖለቲከኞች ትንታኔ ጽሁፎችን በግልጽ ያወጣሉ። በዚህ ረገድ የሚቀርቡ መረጃዎችን በቅርብ ለተመለከተ መረጃዎቹ በሳውዲ ንጉሳውያን ቤተሰብ አመራር ስር በሚተዳደር ሃገር ስር የወጡ ናቸው ብሎ እስከመጠራጠር ሊያደርስዎ ይችል ይሆናል። ይህም አካሔድም የሳውዲ መንግስት የተለያዩ ምክንያቶች ደርድሮ ነጻ መገናኛ ብዙሃንን አስሮም ቢሆን እንደመልቀቅ የሚያደርግበትን አካሄድ መኖሩን ማስተዋል ይቻላል! እናም ይብዛም ይነስ መረጃዎችን ትንፋሸን ዋጥ አድርጌም ቢሆን ማንበቡን ለምጀዋለሁ ! እናም በጀመርኩት ርዕስ ዙሪያ የምፈልጋቸውን መረጃዎች ስብሰባ ቅኝቴን አገባድጀ ወደ እኔው የማለዳ ወግ ሙንጨራ ገባሁ! እርግጥ ነው በሳውዲ ዋና ከተማ ሪያድ ካሳለፍነው ወር ወዲህ ለሚስ የተባለች የ6 አመት ሳውዲ ህጻንንና ሌላ ኢስራ የተባለች የ 11 አመት ሶርያዊት ታዳጊ ላይ የተፈጸመውን አሰቃቂ ወንጀል በየትኛውም ሚዛን መወገዝ ያለበት ድርጊት ነው። በኢትዮጵያውያን ተገደሉ መባሉ ደግሞ ያሳዝናል ፣ ያሳፍራል! ይህንንም ተከትሎ ሳውዲ ጊዜያዊ እገዳ አድርጋለች። የሳውዲ መንግስት ኢትዮጵያውያን የቤት ሰራተኛ ቅጥር በጊዜያዊነት ማስቆሙን በሚመለከት በሃሙስ ምሽቱ የጀርመን ራዲዮ ዜና መጽሄት ላይ ከጋዜጠኛ ተክሌ የኋላ ጋር ያደረግኩትን ቃለ ምልልስ ሰምቸ ጨረስኩ። ወዲያውኑ በራዲዮ መረጃው የደረሳቸው በርካታ ወዳጆቸ በስልክ ፣በፊስ ቡክ ገጼና በጓሮ መልዕክት መላኪያ ሳጥን በርካታ አስተያየቶችን ልከውልኛል።
የእገዳው ድጋፍ ፣ ተቃውሞ እና ሰሚ ያጣው ጩኸት ኑሮ…
ከደረሱኝ አስተያየቶች መካከል “እገዳውን እንደግፋለን! ” ያሉኝ አብዛኛው ኢትዮጵያውያን “ያለ ህጋዊ የስራ ኮንትራት መጥተው ግፍና በደል ሲፈጸምባቸው የሚደርስላቸው የመንግስታቸው አካል አለ ማለት አይቻለም። “ያሉኝ አስተያየት ሰጭዎች ስለደገፉበት ምክንያት ማስረዳት ሲቀጥሉ ” አቅም አዳም ያልደረሱ ታዳጊ እህቶቻችን ሳይቀሩ በደላላ ተግዘው እየመጡ ከሚደርስባቸው ግፍ አንጻር ባይመጡ ይሻላል !” በሚል የሳውዲ መንግስት የጣለውን እገዳ እንደሚደግፉ ገልጸውልኛል። በኮንትራት ሰራተኞች ቅጥርና ዝውውር ዙሪያ ያለውን መጠነ ሰፊ ችግር የሚገልጹ አስተያየት የሰጡኝ ወገኖች መንግስት ሌላው ቢቀር ዜጎቹን ከድህነት ማላቀቅ ባይችል በአረብ ሃገራት የተገኘውን የስራ እድል ዜጎች ተጠቃሚ እንዲሆኑ ለማድረግ አልቻለም ሲሉ ቅሬታቸውን በመግልጽ “በመታገዱ የምንሰማው የመከራ ጩኸት እስኪ ይብረድልን! “በማለት ወቀሳቸውን በመብት ማሰከበሩ “አልሰራም! !” ባሉት መንግስት ላይ አነጣጥረው መታገዱ ጥሩ ሆኗል የሚል አስተያየት የሰጡኝ በርካታ ናቸው።
በመታገዱ የተከፉትም ሃሳባቸውን ገልጸውልኛል ። መንግስት ስራውን ባለመስራቱ ለችግሩ ሁሉ ምክንያት ነው በማለት መንግስትን የሚወቅሱት አስተያየት አቅራቢዎች ኮንተራት ስራ ብሎ እንቅስቃሴ ሲጀመር በሃገራት መካከል ሁለትዮሽ ስምምነት አለመደረጉ ትልቁ ስህተት መሆኑን ያስረዳሉ። ከዚያም ቀጥሎ ስራው ሲጀመር ባልተቀናጀ በቂ ጥናት ፣ ያለ በቂ ቅድሚያ ዝግጅት ፣ ያለ በቂ ስልጠናና የመሳሰሉትን ዝግጅቶች አለማድረጉ በማመላከት ስህተቶቹ ለእገዳ ምክንያት መሆናቸውን በአጽንኦት ያስረዳሉ። ” የሳውዲ ሰራተኛ ቅጥሩ እገዳ ይጎዳናል! ” የሚለውን ሃሳብ የሚደግፉት እኒሁ ነዋሪዎች አጥፊው መንግስታችን ነው ሲሉ ደጋግመው ይወቅሳሉ። ተጠያቂዎቹ ከማዕከላዊ መንግስት ቸልተኝነት እስከ ውጭ ጉዳይ ሚኒስትር የኢንባሲና ቆንስል ሹሞች ይወርዳል በማለት ሲያስረግጡ ” መንግስት ለዜጎች የመጣውን እድል እንዲጠቀሙ ማድረግ አልቻለም !” ብለውኛል። ወደዚህ መሰል መደምደሚያ ምን እንዳደረሳቸው ጠይቄያቸው ሲመልሱ “መንግስት ዜጎችን የመደገፉ ሃላፊነት ተዘንግቶታል እንኳ ቢባል ከገቢ አንጻር ያልተመለከተበት አካሄድ አውጥቶ ላወረደው ግራ ያጋባል!” በመለት የመጣውን ወርቃማ እድል መንግስት እንዳልተጠቀመበት እና ይህም እንዳሳዘናቸው ገልጸውልኛል።
እርግጥ ነው የሰራተኞች አቅርቦት ኮንትራት ሰም መንግስት የማመልከቻ ደብዳቤ ለማጻፍ ከሚያስከፍለው ጀምሮ ፖስፖርት በማደስ ፣ ቪዛ በማጽደቅ ፣ በውክልና ፣ በምስክርነትና በመሳሰሉት ከፍተኛ የሆነ በአመታዊ ሪፖርት ተለይቶ ባይነገረንም ከቆዳና ሌጦ ያላነሰ ገቢ አስገብቷል ። ጥቅሙ ከመንግስትም ወርዶ ከህጋዊ እስከ ህገ ወጥ ደላላ ከግለሰብ የሁሉንም ካዝናዎች ማጣበቡ እውንት ነው! ዜጎችም ቢሆን ብዙ መከራ እና ስቃይ እያዩም ቢሆን የተወሰነ በሚያገኙት ገቡ የደፈኑት የወላጅ ዘመድ አዝማድ የችግር ቀዳዳ መጠነ ሰፊ መሆኑን መካድ አይቻለም። በድህነት እየተጠበሰ ያለ ወላጅ በኑሮ ውድነት ኑሮው ይባስ ሲከፋበት ከፋ ህይወቱን በልጆቹ መስዋዕትነት ሊያልሳልፍ በእድሜ ያልበሰሉ ገና ያልጠነከሩ ታዳጊ ልጆችን ከህገ ወጥ ደላሎች ቀቢጸ ተስፋ ተደልሎ ወደ አረብ ሃገር እየላከ ነው ። ከሁሉም የሚሳዝነው ወላጅም ሆነ መንግስት ታዳጊዎች የሚላኩባቸው ሃገራት በሰራተኛ ሰብአዊ መብት ይዞታ በማይመሰገኑ ፣ ቤት ሰራተኛ አያያዝ የሚወገዙ የአረብ ሃገራት ያለ ህግና ስርአት መላካቸው ስለመሆኑ ብዙ ማለት ይቻላል። በአደጋ በተከበበት መንገድ የሚገፋው በአረቡ አለም የቤት ሰራተኝነተ ህይዎት በተለያዩ ምክንያቶች ግፍ ተፈጽሞባቸው ስንኩል ሆነውና ሞተው በድናቸው ሃገር ሲገቡ ማየት ተለምዷል። የታደሉት ሬሳቸው የሚታወቅበት፣ ያልታደሉት ሬሳቸው ሳይቀር የማይታወቅበት አስከፊ የአረብ ሃገሩ ስደት ለመሆኑ ወላጅና መንግስት ከበቂ በላይ መረጃ አላቸው። ወላጅ ድህነት ችግሩ ብሶበትና በደላሎች ቀቢጸ ተስፋ ተታሎ በአብራኩ ክፋዮች ላይ ጨክኗል! መንግስት ችግሩ ትውልድን እያጠፋ ለመሆኑ በእማኝ እያየና እየሰማ ችግሩን ለመከታተልና ለማስቆም ብጣሽ ህግ ማውጣት ተስኖታል። ለተበዳዮች መብት ማስከበርም ሆነ ሲበደሉ ፍትህ መጠየቁን ትቶታል። የሁሉም ስደተኛ ሰራተኛ ህይወት ይህን ሁሉም ይህን ይመስላል አይባልም። ያም ሆኖ ቁጥራቸው ይህ ነው የማይባል የአረቡ ስደት ተጠቂዎች መሆናቸው የሚታበል ሃቅ አይደለም። እስካሁን በዜጎች ላይ እየደረስ ያለው ግፍና መከራ ግን ለቀሪው ትምህር ሆነው ስደቱን ሊገድበው አልቻሉም።
የሳውዲ መንግስትን የሰራተኛ ማስገባት ጊዜያዊ እገዳ ጠልቀን ማየት ከሞከርን እርምጃውን ደገፍነም ተቃወምን ፣ አስደሰተንም አስከፋን አንድ እውንታ ድጋፍ ፣ ደስታ፣ ተቃውሞ ፣ መከፋቱን አንድ ያደርጋቸዋል! በእገዳውን የመደሰትና የመደገፋችን ስሜት ምንጩ መንግስት ለዜጎች ተቆርቁሮ የመብት ጥበቃ አለማድረጉ ሲሆን በአንጻሩ እገዳውን ያስከፋን መንግስት በድህነት አረንቋ ውስጥ ያሉ ዜጎች በመጣውን እድል መታደግ ባለመቻሉ ነው ብሎ መደምደም ይቻላል ባይ ነኝ! በዚህም ጎን ለጎን በያዝነው ሳምንት አጋማሽ የወጣው የሳውዲ መንግስት ጊዜያዊ እገዳ መንግስታችን እያፈሰው ያለው ገቢ ጋብ ብሎ ኢኮኖሚውን ከማሽምድመድ ባይደርስም በዙሪያው ተጠቃሚ ለሆኑት ደላሎች ታላቅ መርዶ ነው! በባለጊዜዎች ከለላ ሲንቀሳቀሱ ለከበሩት የምስለኔዎቻችን ወዳጆችም እገዳው ዱብ እዳ ነው! በአንጻሩ የፈልግው ይምጣ ብለው ሰርተው ለመለወጥ ቋምጠው ለመሰደድ በቋፍ ላይ ላሉት ዜጎች መልካም የምስራች አይደለም! መርዶ እንጅ! የሳውዲ በቅርቡ የሳተውን የምህረት አዋጅ ተከትሎ መኖሪያ ፈቃድ ለማግኘት በወረፋ ላይ ላሉትም ቢሆን ዜናው መልካም አይደለም! ገጽታችን እንገንባ እያሉ ገጻችን እያበላሹ ለዚህ ላበቁን ይብላኝላቸው እንጅ በሳውዲ ለከተምን እየተሰራ ያለው አንገታችን አስደፍቶናል ! በአረብ ባገሩ ስደት ህይወት የዜጎችን በደል ፣መከራና ሰቆቃ ከባለቤቶቹ ስቀበል ለባጀሁት ጎልማሳም ስሜቱ ከላይ የገለጽኩት አይነት የተቀላቀለ ነው! አገዳው ያስደስታልም! ያሳዝናል ፣ ያስቆጫልም! እየሆነ ያለው ደፍሞ ያሳፍራል! መንግስት ሆይ! በደል ፣ ጭንቀት ሃዘናችን ስማ!
በጎ በጎውንም አስብልን!
ነቢዩ ሲራክ

No comments:

Post a Comment