FREE ALL POLITICAL PRISONERS

FREE ALL POLITICAL PRISONERS
FREE ALL POLITICAL PRISONERS

Tuesday, July 16, 2013

የሚወለዱበት፣ የሚሞቱለትና የሚሞቱበት መሬት (ፕ/ር መሰፍን ወ/ማርያም)


ፕ/ር መሰፍን ወ/ማርያም
የሚወለድበትን መሬት ማንም ሰው አይመርጥም፤ የዘመኑ ቅንጦት ኢትዮጵያ አርግዞ አሜሪካ መውለድ ቢሆንም፣ ልጁ ምርጫው ውስጥ የለበትም፤ አንኳን ልጁ አባትዬውም ምርጫው ውስጥ የሚገባ አይመስለኝም፤ በእንደዚህ ያለው ኢትዮጵያን አስጠልቶ-ሌላ-እንዲሆን በተፈጠረ ቅንጦት የሚወለድ ኢትዮጵያዊ ምን እንደሚሆን መተንበይ ያዳግታል፤ ልጁ ወይም ልጅቱ በራሳቸው ዝንባሌ፣ ፍላጎትና ጥረት ከኢትዮጵያ ጋር ያላቸው ግንኙነት በእልህ ከአልተለወጠ እናቶቻቸው የተለሙላቸው ማንነት ከኢትዮጵያዊነት ይገነጥላቸዋል፤ ነገር ግን የኢትዮጵያዊነት ስሜት እንዲህ በቀላሉ ተቀርፎ የሚወድቅ አይደለም፤ ሲደንቀኝ የቆየ ነገር ልናገር፤ አንድ ጊዜ በኢሰመጉ ተልእኮ ካናዳ ሄጄ አንድ ስብሰባ ላይ አንድ አርመን ወጣት ነበረ፤ ይህ ሰው ለኢትዮጵያ ያለው ስሜት በጣም የጋለ ነበር፤ በሌላ ዘመን ደግሞ ፋጡማ ሮባ በአትላንታ ማራቶን በአሸነፈች ጊዜ ደግሞ በቴክሳስ የሚኖር ከአንድ ግሪክ ገንፍሎ የወጣው ንግግር በጣም ልብን የሚነካ ነበር፤ ለዚህ አርመንና ለዚህ ግሪክ የኢትዮጵያዊነት ስሜት በዘር የተላለፈላቸው አይመስለኝም፤ ስለዚህም አሜሪካ የሚወለዱትም ኢትዮጵያውያን ልጆች እናቶቻቸው ሳያውቁ ከውስጣቸው የሚያስተላልፉላቸው ስሜት ኢትዮጵያዊነታቸውን ይገነባው ይሆናል፤Prof. Mesfin Woldemariam
እንደሚመስለኝ የሚሞቱለት መሬት ከውስጥ ከነፍስ ጋር በተገናኘ ስሜት የተቆራኘ ነው፤ መሬቱንና ስሜቱን ምን አገናኛቸው? ምን አቆራኛቸው? እንዴት ተቆራኙ? የሚሉትንና ሌሎችንም ጥያቄዎች ለመመለስ መሞከር እዚህ ቦታው አይደለም፤ ለዚች መሬት የሞቱላት በሚልዮኖች የሚቆጠሩ ሰዎች መኖራቸውን አምነን በመቀበል እንነሣ፤ ምናልባትም አብዛኛዎቹ ቁራጭ መሬትም አልነበራቸውም፤ እንዲያውም አብዛኞቹ ለመቃብር ያህል ሁለት ክንድ መሬት አንኳን አላገኙም፤ በተሰለፉበት ወድቀው የአውሬና የአሞራ ምግብ ሆነው የቀሩ ናቸው፤ ለመሬት ፍቅር ሞተው ለመቃብር የሚሆናቸው መሬት እንኳን አላገኙም፤ ነገር ግን የሚደንቀው እነሱ ሞተው ለመቃብርም የሚሆን መሬት ሳያገኙ የሚቀጥለውን ትውልድ ባለመሬት አደረጉት።
እንደሚመስለኝ የአንድ አገር አንዱ ትውልድ በሞቱ ለሚቀጥለው ትውልድ የሚያስተላልፈው መሬት ብቻ አይደለም፤ ሲሞት ይዞት የነበረውን ጎራዴና ጋሻ፣ ለሞት ያበቃውን የመሬት ፍቅር፣ ክብርና ኩራትም ጨምሮ ነው፤ መሬቱን ብቻ ተረክቦ ሌላውን መጣል የውርደት መጀመሪያ ይሆናል፤ እዚህ ላይ ብዙ ሰዎች በሚጠሉት ቃል መጠቀም ልገደድ ነው፤ ባንዳ የሚባለው መሬቱን ከክብርና ከኩራቱ ጋር ለጠላት ያስረከበ ነው፤ (እውነተኛው ባንዳ እንዲያውም ዜግነቱንና ወገኖቹን ክዶ፣ የሰውነቱን ክብር ሸጦ የጠላት ሎሌ በመሆን ወገንን እያስጠቃ ተዋርዶ የሚያዋርድ ነው)፤ ለባንዳው መሬት ርስትና ዓጽመ-ርስት የሚባሉ ነገሮች ትርጉም የላቸውም፤ ዓጽመ-ርስት የሕይወት መስዋእት የተከፈለበት መሬት መሆኑ ለባንዳው ባዕድ ነገር ነው።
የኢትዮጵያ መሬት ከአድዋ ዘመቻ እስከዛሬ ስድስት ያህል ትውልዶችን አስተናግዶአል፤ ከአድዋ አስከማይጨው ሁለት ትውልዶች፣ ከማይጨው እስከ1967 ሁለት ትውልዶች፣ ከ1967 አስከ2005 ሌላ ሁለት ትውልዶች እነዚህ ትውልዶች በኢትዮጵያ መሬት ላይ ያመጡትን ለውጥ ሁሉም የሚያውቀው ይመስለኛል፤ ቢሆንም ልዩነታቸውን ማመልከት የሚያሻ ይመስለኛል፤ በአድዋ የዘመተው ትውልድ በርስትና በዓጽመ-ርስት ላይ የተተከለ ልበ-ሙሉ ባለቤት ነበር፤ የማይጨው ዘማች በግርማዊነታቸው ቸርነትና መልካም ፈቃድ ላይ የተመሠረተ ስጦታና የማደሪያ መሬት ነበረው፤ በአንዳንድ ቦታ ብዙ ገበሬዎችን ከመሬት ባለቤትነት የነቀለና ወደጭሰኛነት የለወጠ ሥርዓት ነበር፤ ከ1967 ወዲህ ሁለት ዓይነት የመሬት አጠቃቀም ይታያል፤ አንዱ የደርግ ሥርዓት የኢትዮጵያን ሕዝብ በሙሉ ከዳር አስከዳር እኩል ባለመሬት ለማድረግ ያወጣው አዋጅ ርስትንም ማደሪያንም ሽሮ የመሬት ባለቤትነትን በዜግነት ላይ ተከለ፤ የወያኔ ሥርዓት ሲመጣ የገጠር መሬትን በፖሊቲካ ታማኝነት ደለደለ፤ የከተማ ቦታን ደግሞ በአጼ ዘመን ሲሠራ እንደነበረው ለቅርብ ሎሌዎችና ታማኛ አገልጋዮች እንደማደሪያ ዓይነት እየሆነ ተሰጠና አዲስና በጣም ከፍተኛ የከተማ ባለሀብቶች መደብ ተፈጠረ፤ በገጠርም ለልዩ ሰዎችና ለስደተኞች፣ እንዲሁም ለውጭ አገር ባለሀብቶች (ቻይና፣ ህንድ፣ ሆላንድ … ) ተደለደለ፤ እንዲህ እንዲህ እያለ በወያኔ አገዛዝ በውጭ አገር ከበርቴዎችና በአገር ውስጥ የቢሮና የጠመንጃ ከበርቴዎች እየበረከቱ ደሀው ተደፈጠጠ፤ የወያኔ አገዛዝ የማርክስና የሌኒንን መፈክር አንግቦ ተነሣና ደሀን የጠላበት ደረጃ ላይ ደረሰ፤ እንደሚስለኝ የተለመደው የአስተሳሰብ ስሕተታቸው ነው፤ ደሀነትንና ደሀን አንድ አድርገዋቸዋል!
በወያኔ አገዛዝ በገጠሩም ሆነ በከተማው መሬት ላይ የተወሰደው በጣም ደፋር እርምጃ በጣም የሚያስደንቅና ገዢዎችንም ተገዢዎችንም ለታሪክ ትዝብት የሚዳርግ ነው፤ አንድ ኪሊሜትር መንገድ ለመሥራት ስንት ደሀ ቤተሰብ ይፈናቀላል? አንድ ትልቅ ሕንጻ ለመገንባት ስንት መድረሻ የሌላቸው ደሀዎች አውላላ ሜዳ ላይ ይወድቃሉ? ነገር ግን ጨቋኝና ተጨቋኝ በስምምነት ለሚቀጥለው የጥቃት ዙር ይዘጋጃሉ፤ ይህ የትም ሌላ አገር የሚሆን አይመስለኝም፤ የኢትዮጵያውያን ልዩ ችሎታ ነው፤ እዚህ ወደዝርዝር ምክንያቱ አልገባም፤ ግን ምክንያት አለው።
እንኳን ለቀለብ ማምረቻ የሚሆን መሬት፣ አንኳን የመኖሪያ ቤት የሚሠራበት መሬት ለመቃብርም የሚሆን ሁለት ክንድ መሬት በሊዝ ሆኖአል፤ ወደፊት ደሀ የሚጣልበት መሬት አይገኝም ይሆናል፤ እንግዲህ የሚሞቱበት መሬት ወደማይኖርበት ሁኔታ እየደረስን ነው ማለት ነው፤ ስለዚህም አስቀድመን ማሰብ የሚያስፈልገን ይመስለኛል፤ በራሴ በኩል አውጥቼ አውርጄ ውሳኔ ላይ ከደረስሁ ቆይቻለሁ፤ መቀበር አልፈልግም፤ ሕይወቴን በሙሉ ተቀብሬ ኖሬአለሁ! ወይም በመቃብር ውስጥ ኖሬአለሁ፤ ድንጋይ እየተደራረበ ተጭኖብኝ አምላክ ድንጋዩን አፈር አድርጎ እያቀለለልኝ ሳልጨፈለቅ ቆይቻለሁ።
ስሞት ደግሞ፣ ወይም አንዳንዶቻችሁ ቃልም እንደምትፈሩ ለማሳየት እንደምትሉት ለህልፈት ስበቃ የሬሳን ፈቃድ የሚፈጽም ከተገኘ መቀብር አልወርድም፤ ድንጋይ አይጫንብኝም፤ ይበቃኛል፤ ኑዛዜ– ከሚለው ግጥሜ ቀንጭቤ ፍላጎቴን ልግለጽላችሁ፡ –
የሕይወት ጽዋዬ ጥንፍፍ ብሎ ሲያበቃ፤
ሲቀር ባዶውን፣ የቆየ ባዶ ዕቃ፤
ሲበቃኝ፤ በቃህ ስባል፣
ትንፋሼ ሲቆም በትግል፣
ስሸነፍ ተሟጦ ኃይል፣
ሰው መሆኔ ቀርቶ፣- አስከሬን ስባል፣
እወቁልኝ ይህን ብቻ፣- የገባኝን ያህል
ሞክሬ ነበር ሰው ለመሆን፤
ሰውነት በከፋበት ዘመን።
በቁማችን ስንቃጠል ስንቀጣጠል ኖረን ስንሞት እሳትን ለምን እንፈራለን? ጭቆናና መታፈን ለምደን መቃብር እንወዳለን፤ እንደአህያችን ጭነት ለምደን ድንጋይ ለመሸከም ቀባሪ አታሳጣን እንላለን፤ –
መሬት አልነበረኝም በሕይወቴ
መሬት አልፈልግም፤ አሁን በሞቴ
አቃጥሉልኝ ሬሣዬን፤
አመድ እስኪሆን፤
አዋሽ ውስጥ ጨምሩልኝ አመዴን፤
አመዴ
ከአዋሽ ይቀላቀል ከዘመዴ
ይቺን አትንፈጉኝ አደራ
አመዴ እንኳን እንዲኮራ
የወያኔ አገዛዝም ሬሳ አቃጣይ ድርጅት ቢከፍት ለመቃብር የሚውለውን መሬት ለቻይና በማከራየት ኪራይ ሰብሳቢነቱን ያጠናክር ነበር፤ ህንዶች ሬሳ በማቃጠል ልምድ ስላላቸው አንድ የህንድ ባለሀብት ሬሳ በማቃጠሉ ሥራ ቢሰማራ የኢኮኖሚውን እድገት በጣም ያፋጥንላቸው ነበር፤ ለአገዛዙም፣ ለባለሀብቱም አዲስ የሥራ መስክ ይፈጥራል፣ ሬሳ የማቃጠሉ ተግባር በቁሙ የተጎዳውን ደሀ ሲሞት ደግሞ መድረሻ እንዳያሳጣው የደሀ ሬሳ ለማቃጠል የሚያስፈልገው ወጪ ‹‹ድህነትን ለመቀነስ›› ከሚለው በጀት ወይም እርዳታ ቢወጣ ችግሩን ሁሉ ያቀላጥፈዋል፤ ደሀውም እየተደሰተ ይቃጠላል ወይም ችግሩ አብሮት እንደሚቃጠል እያወቀ ይደሰታል።
የወደፊቱ ኢትዮጵያዊ የሚወለድበት መሬት የለውም፤ የትም የሚወለድ ነው፣ ፍቅሩን ከመሬት ላይ አንሥቶ ጥሬ ገንዘብ ላይ በመካቡ የሚሞትለት መሬት የለውም፤ ከመሬት ጋር ያለው የዓጽመ-ርስት ቁርኝት ስለተበጠሰ የሚሞትበት መሬት የለውም፤ ‹‹አፈር ነህና ወደአፈር ትመለሳለህ፤›› የተባለው ቀርቶ ድንጋይ ነህና ወደድንጋይ ትመለሳለህ የሆነ ይመስላል፤ መሬት የሰውነት መለኪያ መሆኑ ቀርቶ የሀብት መለኪያ ሆኖአል።

No comments:

Post a Comment