FREE ALL POLITICAL PRISONERS

FREE ALL POLITICAL PRISONERS
FREE ALL POLITICAL PRISONERS

Friday, November 30, 2012

ESAT Daliy News-Amsterdam Nov. 30 2012 Ethiopia


የሁለቱ ም/ጠቅላይ ሚኒሰትሮች ሹመት ህገመንግስታዊ ድጋፍ የለውም ሲሉ አንድ ታዋቂ የህግ ባለሙያ ገለጹ


ህዳር ፳፩ (ሃያ አንድ) ቀን ፳፻፭ ዓ/ም
ኢሳት ዜና:-በሩዋንዳ ተቋቁሞ በነበረው የተበባሩት መንግስታት ድርጅት አለማቀፍ የወንጀለኞች ፍርድ ቤት ዋና አቃቢ ህግ በመሆን ያገለገሉት እና በህግ የማስተማር ሙያ ላይ ለረጅም ጊዜ አገልግሎት የሰጡት ዶ/ር ያቆብ ሀይለማርያም ለኢሳት እንደተናገሩት የሁለቱ ጠቅላይ ሚኒስትሮች ሹመት ህገመንግስታዊ ድጋፍ የለውም። ዶ/ር ያቆብ ” የህገመንግስቱ አንቀጽ 75 ጠቅላይ ሚኒስትሩ በማይኖሩበት ጊዜ ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሩ ተክቶ እንደሚሰራ ይደነግጋል  እንጅ ከሁለት ወይም ሶስት ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሮች መካከል ተመርጦ አንዱ ይተካቸዋል አይልም” ብለዋል
ዶ/ር ያቆብ ሹመቱ ከመሰጠቱ በፊት የተወካዮች ምክር ቤትና የፌዴሬሽን ምክር ቤቶች በጋራ  ተስማምተው ህጉን ማሻሻል ይችሉ እንደነበር ገልጸዋል።
ምናልባት ሌሎች ያልታዩ የህግ ድንጋጌዎች በመኖራቸው በነዚያ ድንጋጌዎች መሰረት የተደረገ ሹመት ሊሆን አይችሉም ወይ ተብለው ለተጠየቁት ዶ/ር ያቆም ፣ ምንም የሚያሻማ ነገር ነገር የለም በማለት መልሰዋል
ኢህአዴግ ስለ ህገመንግስት  መታስ በተደጋጋሚ ይናገራል፣ በዚህ ድንጋጌ ላይ ህገመንግስቱ በግልጽ እንደተጣሰ ተናግረዋል፣ ኢህአዴግ እሞትለታለሁ የሚለውን ህገመንግስት ለምን በአደባባይ ለመጣስ የፈለገ የመስልዎታል በሚል ለቀረበላቸው ጥያቄ ደግሞ፣ ዶ/ር ያቆም ኢህአዴግን በመሰረቱ 4 ድርጅቶች መካከል ያለውን የስልጣን ሽኩቻ ለማብረድ ታስቦ ሊሆን ይችላል ብለዋል
አቶ ሀይለማርያም ደሳለኝ የህወሀቱን ዶ/ር ደብረጺዮን ገብረሚካኤልንና የኦህዴዱን አቶ ሙክታር ከድርን ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር በማድረግ መሾማቸው ይታወሳል።

የድምጻችን ይሰማ የኮሚቴ አባላት ፍርድ ቤት ቀረቡ


ህዳር ፳፩ (ሃያ አንድ) ቀን ፳፻፭ ዓ/ም
ኢሳት ዜና:-የሙስሊም ኢትዮጵያውያንን ሰላማዊ ተቃውሞ በመምራታቸው በሽብርተኝነት ተከሰው በእስር ላይ የሚገኙት የድምጻችን ይሰማ የአመራር አባላት ዛሬ ልደታ በሚገኘው ከፍተኛው ፍርድ ቤት ቢቀርቡም ለህዳር 27 ቀን 2005 ዓም የጊዜ ቀጠሮ ተሰጥቷቸው ወደ እስር ቤት ተመልሰዋል።
የኮሚቴ አባላት ጠበቃ የሆኑት አቶ ተማም አባቡልጋ ለኢሳት እንደገለጡት የዛሬው ችሎት አቃቢ ህግ በጠበቆች በኩል ለቀረበው መቃወሚያ መልስ ለመስጠት  ተብሎ የተቀጠረ ነበር። አቃቢ ህግ መልሱን በንግግር ለፍርድ ቤት ማቅረቡን የገለጡት አቶ ተማም ፍርድ ቤቱ የግራ ቀኙን መከራከሪያ ሰምቶ ተከሳሾች በቀረበባቸው ክስ ቃላቸውን ይስጡ አይስጡ በሚለው ላይ ውሳኔ ለማስተላለፍ የፊታችን ሀሙስ መቀጠራቸውን ተናግረዋል።
አቶ ተማም እንዳሉት ፍርድ ቤቱ በመጪው ሀሙስ ክሱ እንዲቀጥል፣ እንዲሻሻል፣ ወይም ውድቅ እንዲሆን ብይን ይሰጣል።
ጠበቆች ባለፈው ሳምንት ባቀረቡት መቃወሚያ በአቃቢ ህግ የቀረበው ክስ ህገመንግስቱን የጣሰና በርካታ የህግ እጸጾች ያሉበት ነው በማለት መገልጻቸውን መዘገባችን ይታወሳል።
ይህ በእንዲህ እንዳለ ለኮሚቴ አባላቱ ድጋፋቸውን ለመስጠት ወደ ልደታ ያቀኑ ሙስሊሞች በፖሊሶች መባረራቸውን አንዳንዶችም በፖሊስ መኪኖች ተጭነው መወሰዳቸው ታውቋል።
ጉዳዩን በማስመልከት በአካባቢው የነበሩ የተለያዩ የእስልምና እምነት ተከታዮችን አነጋግረን እንደተረዳነው ፖሊሶች እናቶችን ብቻ በመለየት እየደበደቡ ወደ እስር ቤት ውሰደዋቸዋል
ሌላ ሙስሊም  በበኩሉ ” ወንዶችን ቢደበድቡ የተለመደ ነው፣ እናቶችንና እህቶቻችንን መደብደባቸው ግን ሊወጥልን አልቻለም” ብሎአል
የሙስሊም ኢትዮጵያውያን ተቃውሞ እንደቀጠለ ባለበት በዚህ ጊዜ መንግስት፣ ኮሚቴ አመራሩን የሚያወግዙ ሰልፎችን በተለያዩ ከተሞች እያዘጋጀ መሆኑን መዘገባችን ይታወሳል።
በኦሮሚያ ክልል አዳማን ጨምሮ በተለያዩ ዋና ዋነ ከተሞች ለማዘጋጀት የኮሚቴ አባላት መዋቀራቸውን ለማወቅ ተችሎአል።

የአቡነ ጴጥሮስ ሃውልትን አንስቶ በሙዚየም ለማቆየት ኮሚቴ መቋቋሙ ተነገረ


ህዳር ፳፩ (ሃያ አንድ) ቀን ፳፻፭ ዓ/ም
ኢሳት ዜና:-የህወሀት ኢህአዴግ ልሳን የሆነው  ሬዲዮ ፋና እንደዘገበው የአቡነ ጴጥሮስ ሃውልት በግንባታው ስለሚነካ በጊዜያዊነት ይነሳና በጥንቃቄ በሙዚየም ይቀመጣል፣ ግንባታው ሲጠናቀቅም ወደ ስፍራው ይመለሳል።
የዳግማዊ ምኒልክ ሃውልት ግን ከፕሮጀክቱ ጉድጓድ 15 ሜትር ርቀት ላይ የሚገኝ በመሆኑ አይነሳም ብሎአል።
ይፈርሳል በሚል የሚናፈሰው ወሬም ከእውነት የራቀ  ነው በማለት የኢትዮጵያ ምድር ባቡር ኮርፖሬሽን ፣ የአዲስ አበባ መንገዶች ባለስልጣን፣ የቅርስ ጥናትና ጥበቃ ባለስልጣንና ሌሎችም ባለድርሻ አካላትን ዋቢ አድርጎ ዘግቧል።
ሀውልቱ ሲነሳም ሆነ መልሶ በሚተከልበት ወቅት ምንም አይነት ጉዳይ እንዳይደርስበትም ከፍተኛ ጥንቃቄ እንደሚደረግና ምንም አይነት የቦታ ለውጥ እንደማይደረግበትም ራዲዮው ዘግቧል።
ራዲዮው ይህን መግለጫ የሰጡትን ሰዎች ማንነት ይፋ አላደረገም። ሀውልቱን የሚያነሳውና መልሶ የሚተክለው ድርጅት ማን እንደሆነም አልተጠቀሰም። በየትኛው ሙዚየም ለምን ያክል ጊዜ እንደሚቆይ፣ ሀውልቱ ቢፈርስ ወይም ጉዳት ቢደርስበት አፍራሽ ግብረሀይሉ የመልሶ ማሰሪያ ገንዘብ ማስያዝ እና አለማስያዙ ወይም ኢንሹራንስ መግባቱና አለመግባቱ በዜናው ላይ አልተገለጸም። ሀውልቱ ተመልሶ እንደሚተከል ምን አይነት ዋስትና እንደተሰጠም አልታወቀም።
የአቡነ ጴጥሮስ ሀውልት መነሳት ጉዳይ ከፍተኛ የህዝብ መነጋገሪያ መሆኑ ይታወቃል። እስካሁን ድረስ በአገር ውስጥ የሚገኙ የፖለቲካ ድርጅቶች፣ ምሁራን ወይም ባለሙያዎች አስተያየቶቻቸውን በመግለጫ መልክ ወይም በማንኛውም መንገድ አልሰጡም በማለት የአዲስ አበባው ዘጋቢያችን ዘገባውን አጠቃሎአል።

Thursday, November 29, 2012

Ethiopians chilldren adoption ! Gudifecha


ESAT Daliy News-Amsterdam Nov. 29 2012 Ethiopia


ESAT DC Daily News November 28 2012


ሞረሽ ወገኔ የአቡነ ጴጥሮስን ሀውልት የማፍረስ እቅድ ተቃወመ


ህዳር ፳ (ሃያ) ቀን ፳፻፭ ዓ/ም
ኢሳት ዜና:-ሞረሽ ወገኔ የአማራው ድርጅት የአቡነ ጴጥሮስ ሀውልትን ለማፍረስ መንግስት ማቀዱ የአማራው ታሪክን ለማጥፋት የተያያዘው እርምጃ አካል በመሆኑ እናወግዘዋለን ሲል አስታወቀ።
መላው የኢትዮጵያ ህዝብም ይህንን የመንግስት እቅድ በመቃወም ድምጹን እንዲያሰማ ሞረሽ ወገኔ ጥሪ አቅርቧል።
ሞረሽ ወገኔ ለዝግጅት ክፍላችን በላከው መግለጫ እንዳስታወቀው የአማራው ህዝብ ላይ የማጽዳት እርምጃ ሲወስድ የቆየው ገዥው ፓርቲ ታሪኩንም ሲያጠፋ ቆይቷል ካለ በኋላ የአባቶቻችን የክብር አጽም ያረፈበትን ቦታ አፈረሰ፣ የዋልድባ ገዳምን አረሰ፣ የዝቋላ አቦን አቃጠለ ሲል በአብነት ዘርዝሯል በመግለጫው።
የአማራ ህዝብና በአጠቃላይ በኢትዮጵያ ህዝብ ላይ የሚያደርገው ታሪክና ቅርስ የማጥፋት እርምጃ ተጠናክሮ ቀጥሏል ያለው ሞረሽ ወገኔ የአማራው ድርጅት የአቡነ ጴጥሮስ ሀውልት ሳይፈርስ በአንድነት ተነስቶ ቁጣውንና አሻፈረኝ ባይነቱን ሊያሳይ ይገባል በማለት በመግለጫው አሳስቧል።
ድርጊቱን ለኢትዮጵያ ታሪክና አንድነት ተጠብቆ መዝለቅ ጽኑ አላማ  ያላቸውን ኢትዮጵያዊያን በአንድነት ተነስተው የአቡኑን ሀውልት ለማፍረስ የታቀደውን እቅድ እንዲቃወሙ ጥሪውን አስተላልፏል።

በመንግስት በተጠራ ሰልፍ የሀርቡ ህዝብ ሳይገኝ ቀረ


ህዳር ፳ (ሃያ) ቀን ፳፻፭ ዓ/ም
ኢሳት ዜና:-በደቡብ ወሎ የሀርቡ አካባቢ ሙስሊም ነዋሪዎች በገዥው ፓርቲ የቀረበላቸውን የሰልፍ ጥሪ ባለመቀበል አንወጣም ማለታቸው ተገለጸ።
ባለስልጣናቱ ተማሪዎቹን ከትምህርት ቤት በማስወጣት ሰልፍ እንዲያደርጉ ማድረጋቸውም ተዘግቧል።
በገዥው ፓርቲ ባለስልጣናት የቀረበው የሰልፍ ጥሪ ያልተገኘ ነዋሪ 50 ብር እንደሚቀጣ ቢገለጽም ህዝቡ ለማስጠንቀቂያው ቦታ ባለመስጠት በሰልፉ ሳይገኝ ቀርቷል።
ከሬዲዮ ቢላል ያገኘነው መረጃ እንዳመለከተው የፌደራል ፖሊሶችና ያካባቢው ባለስልጣናት በየቤቱ እየዞሩ ለሰልፍ ውጡ በማለት ሲያስገድዱ የነበረ ቢሆንም አብዛኛው ሙስሊም አሻፈረኝ ሲል እምቢ ብሏል።
የሰልፉ አላማ በግልጽ አልተገለጸም ያለው የሬዲዮ ቢላል ዘገባ ሙስሊም ያልሆኑ የአካባቢው ባለስልጣናት ከትምህርት ቤት ይዘዋቸው ለሄዱት ህጻናት ሰልፈኞች አሸባሪነትን እንቃወማለን ፣ አካባቢያችን ሀርቡ ሰላም ናት የሚል መፈክሮችን እያሰሙ እንዲቀበሏቸው ሲሞክሩ እንደነበር ገልጿል።
በቀጥታ ከትምህርት ቤት ወደ ሰልፍ እንዲወጡ የተደረጉት የመጀመሪያና ሁለተኛ ደረጃ ት.ቤት ተማሪዎች አብዛኞቹ በገዢው ፓርቲ አባላት ሰዎች የሚነገረውን መፈክር ተቀብለው እንዳላስተጋቡም ከዘገባው መረዳት ተችሏል።
በሰልፉ ላይ የአካባቢው መኪኖች ሰልፉን እንዲያጅቡ ታዘው እንደነበር ያመለከተው ዘገባ አናደርገውም ብለው ሳይገኙ መቅረታቸውን ገልጿል።

የኢትዮጵያ ህዝብ ቁጣ ከተናጥል ወደ ማህበረሰባዊ ሊቀየር ይገባል ተባለ


ህዳር ፳ (ሃያ) ቀን ፳፻፭ ዓ/ም
ኢሳት ዜና:-የኢትዮጵያ ህዝብ በሚደርስበት የኢኮኖሚና የፖለቲካ በደል የሚያሰማውን የተናጥል ቁጣ በጋራ ማሳየት ይገባዋል ሲሉ ዶክተር ነጋሶ ጊዳዳ ገለጡ።
የኢሀዲግ መንግስት ለፓርቲው እንጂ ለህዝብ ደንታ የለውምም ብለዋል።
የአንድነት ለዲሞክራሲና ለፍትህ ፓርቲ ሊቀመንበር ዶ/ር ነጋሶ ጊዳዳ በሀገሪቱ ወቅታዊ ጉዳይ ላይ ባደረጉት ውይይት እንደገለጹት የኢትዮጵያ ህዝብ ብሶቱን ቋጥሮ በማጉረምረም ላይ የሚገኝ ነው ፤ ቁጣውም ቢሆን በተናጠል የሚገለጽ ነው፤ ይህ የተናጥል ቁጣና ማጉረምረም ግን እንደሌሎች ሀገሮች በጋራና በአንድነት ሊገለጽ ይችላል ብለዋል።
እስከ አሁን እንደታየው ማህበራዊ፣ ኢኮኖምሚያዊና ፖለቲካዊ ችግሮቹን ይዞ ሰቆቃና ብሶቱን በተናጥል ወይም በጥቂት ቡድን ደረጃ ያማርራል እንጂ በጋራ ሆኖ ድምጹን አላሰማም ያሉት ዶ/ር ነጋሶ ይህ ንዴቱና ብሶቱ ወደ ህብረተሰባዊ ንዴትና ቁጣ አልተለወጠም ብለዋል።
በሌሎች ሀገሮች የዳቦና የነዳጅ ዋጋ ላይ ትንሽ ጭማሪ ከታየ የህብረተሰብ ንዴቶች ይገነፍላሉ በኛ ሀገር ግን ከተናጥል ቁጣና ንዴት አልፎ ወደተደራጀና ህዝባዊ የእንቢተኝነት እንቅስቃሴ አልተለወጠም ያሉት የአንድነት ፓርቲ ሊቀመንበር ዶ/ር ነጋሶ ጊዳዳ አንባገነንነትና ለህዝብ ብሶት ግድ የሌለውን መንግስት ለመፈተን የተደራጀና ህብረተሰባዊ ቁጣ ያስፈልጋል ብለዋል።
ህዝባዊ ጥያቄንና ተቃዋሚ ፓርቲዎችን ለማፈን ሲል ገዥው ፓርቲ ህገመንግስት ይጥሳል ፤ ህግ በማውጣት ህግ አስከብራለሁ ብሎ ሰባዊ መብቶችን ይጥሳል ብለዋል።

አቶ ሀይለማርያም ደሳለኝ የተጠበቁ የስልጣን መሸጋሸጎችን አደረጉ


ህዳር ፳ (ሃያ) ቀን ፳፻፭ ዓ/ም
ኢሳት ዜና:-አቶ ሀይለማርያም ደሳለኝ ዛሬ ይፋ ባደረጉት ሹመት 2 ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትሮችን እና ሁለት ሚኒስትሮችን ብቻ በመሾም አቶ መለስ የመሰረቱትን ካቢኔ ይዘው እንደሚቀጥሉ አስታውቀዋል።  አስቀድሞ እንደተጠበቀው የኦህዴዱ አቶ ሙክታር ከድር በምክትል ጠቅላይ ሚኒስትርነት ማእረግ የሲቪል ሰርቪስ ሚኒሰትር በመሆን የአቶ ጁነዲን ሳዶን ቦታ ተክተዋል። የህወሀቱ ዶ/ር ደብረጺዮን ገብረሚካኤል ደግሞ በምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር ማእረግ የፋይናንስና ኢኮኖሚ ዘርፍ አስተባባሪ በመሆን ቀደም ብለው በያዙት የመገናኛ እና ኢንፎርሜሽን ቴክኖሎጂ ስልጣን  ላይ እንዲቆዩ ተደርጓል።
አዲስ ሹመት የተሰጠው ለውጭ ጉዳይ ሚኒስትርነት ቦታ ሲሆን፣ የጤና ጥበቃ ሚኒስትር የነበሩት አቶ ቴዎድሮስ አድሀኖም  የውጭ ጉዳይ ሚኒስትር በእርሳቸው ቦታ ደግሞ ዶ/ር ከሰተ ብርሀን አድማሱ የጤና  ጥበቃ ሚኒስትር ሆነው ተሹመዋል።
የኮሚኒኬሽን ጉዳዮች ሚኒስትሩ አቶ በረከት ስምኦን፣ የመከላከያ ሚኒስትሩ፣ አቶ ሲራጅ ፈርጌሳ፣ የፌደራል ጉዳዮች ሚኒስትር ዶ/ር ሽፈራው ተክለማርያም፣ የፍትህ ሚኒስትሩ አቶ ብርሀነ ሀይሉ፣ የገንዘብ ሚኒስትሩ አቶ ሶፍያን አህመድ፣ የግብርና ሚኒስትር አቶ ተፈራ ደርበው፣ የኢንዱስትሪ ሚኒስትሩ አቶ መኮንን ማንያዘዋል፣ የሳይንስ እና ቴክኖሎጂ ሚኒስትር አቶ ደሴ ደለቀ፣ የትራንስፖርት ሚኒሰትሩ አቶ ድሪባ ኩማ፣ የኮሚኒኬሽን ሚኒሰትሩ አቶ ደብረጺዮን ገብረሚካኤል፣ የከተማ ልማት ሚኒስትሩ አቶ መኩሪያ ሀይሌ ፣ የውሀ እና ኢነርጂ ሚኒስትሩ አቶ አለማየሁ ተገኑ፣ የማእድን ሚኒስትሯ ወ/ሮ ስንቅነሽ እጅጉ፣ የትምህርት ሚኒሰትሩ አቶ ደመቀ መኮንን፣ የሰራተኛና ማህበራዊ ሚኒሰትሩ አቶ አብዱላጢፍ አብዱል አህመድ ፣ የባህልና ቱሪዝም ሚኒስትሩ አቶ አማን አብዱልከድር፣ የሴቶች ፣ ልጆችና ወጣቶች ሚኒስትር ወ/ሮ ዘነቡ ታደሰ ባሉበት ስልጣን እንዲቀጥሉ ተደርጓል። አቶ መለስ ባባረሩዋቸው የንግድና እንዱስትሪ ሚኒስትር ቦታ አቶ ሀይለማርያም ሚኒሰትር ዲኤታ የነበሩትን የብአዴኑን አቶ ከበደ ጫኔን ሚኒስትር አድርገው ሾመዋል።
አቶ ሀይለማርያም ለካቢኔዎቹ አስተባባሪዎች ሁለት ጠቅላይ ሚኒሰትሮችን ከመሾም በስተቀር 98 በመቶ የሚሆነውን የአቶ መለስን ካቢኔ ሳይነኩ መቀጠሉን መርጠዋል። ኢሳት በሰሞኑ ዘገባው በአቶ ጁነዲን ቦታ አዲስ ሹመት ከመኖር በስተቀር መሰረታዊ የሚባል የካቢኔ ለውጥ እንደማይኖር ዘግቦ ነበር።
በዛሬው ሹመት ህወሃት የምክትል ጠ/ሚኒስትርነት እና የውጪ ጉዳይ ሚኒስትርነት ቁልፍ ቦታዎችን አግኝቷል፡፡
ሹመቱ የኢህአዴግ አባል ድርጅቶች በተለይም በኦህዴድ እና በህወሃት በተገቢው ሁኔታ አልተወከሉም የሚሉ ቅሬታዎችን
ለማርገብ የታሰበ ሳይሆን እንደማይቀር ለጉዳዩ ቅርበት ያላቸው ምንጮች ጠቁመዋል፡፡ ወ/ሮ አዜብ መስፍን በካቢኔው ውስጥ አለመካተታቸው አስገራሚ ሆኗል።
ሟቹ ጠ/ሚኒስትር አቶ መለስ ዜናዊ መስከረም 25 ቀን 2003 ኣ.ም በሰጡት ሹመት በመንግስት ሥልጣን ላይ
ለረዥም ጊዜ የቆዩትን ባለስልጣናት በመተካካት ስም ዞር ማድረግ ችለዋል፡፡ከነዚህ ባለስልጣናት መካከል ምክትል
ጠ/ሚኒስትር የነበሩት አቶ አዲሱ ለገሰ፣የአቅም ግንባታ ሚ/ር የነበሩት አቶ ተፈራ ዋልዋ፣የንግድና ኢንዱስትሪ
ሚ/ር አቶ ግርማ ብሩ፣የባህልና ቱሪዝም ሚ/ር አምባሳደር መሐመድ ድሪር፣የስራና ከተማ ልማት ሚ/ር የነበሩት
ዶ/ር ካሱ ኢላላ፣የውሃ ሃብት ሚ/ሩ አቶ አስፋው ዲንጋሞ፣የሴቶች ጉዳይ ሚ/ር ወ/ሮ ሙፍረሂት ከሚል፣የሰራተኛና
ማህበራዊ ጉዳይ ሚ/ር የነበሩት አቶ ሐሰን አብደላ የሚገኙበት እንደነበር ይታወሳል፡፡

የሁለት ምክትል ጠ/ሚኒስትሮች ሹመት ሕገ መንግስታዊ ድንጋጌን የጣሰ ነው ተባለ


ህዳር ፳ (ሃያ) ቀን ፳፻፭ ዓ/ም
ኢሳት ዜና:-በዛሬው ዕለት የኢትዮጵያ ፓርላማ የሰጠው ተጨማሪ የሁለት ምክትል ጠ/ሚኒስትሮች ሹመት ሕገመንግስታዊ ድንጋጌን የጣሰ መሆኑን የሕግ ባለሙያዎች አስታወቁ፡፡
በሕገመንግስቱ አንቀጽ 75 ለአንድ ጠ/ሚኒስትር ብቻ ዕውቅና እንደሚሰጥ ያስታወሱት ባለሙያዎቹ በዚሁ አንቀጽ
75(1)ለ ላይ የተመለከተው ጠ/ሚኒስትሩ በማይኖርበት ጊዜ ምክትል ጠ/ሚኒስትሩ ተክቶት ይሰራል የሚለው ንኡስ አንቀጽ አንድ ምክትል ጠ/ሚኒስትር ብቻ  እንደሚኖር የሚያሳይ ነው ይላሉ፡፡በአሁኑ ወቅት ቀደም ሲል የተሾሙትን ጨምሮ ሶስት ምክትል ጠ/ሚኒስትሮች መሾማቸውን ባለሙያዎቹ አስታውሰው ይህ ሕገመንግስታዊ ድንጋጌን የጣሰ አካሄድ ነው ብለውታል፡፡
ጠ/ሚኒስትር ሀይለማርያም እንዲህ ዓይነት ሹመት ለመስጠት ከሕገመንግስቱ በተጨማሪ በአሁኑ ወቅት በስራ ላይ ያለው
የአስፈጻሚ አካላትን እንደገና ለማደራጀት የወጣው አዋጅ ቁጥር 691/2003 ያግዳቸዋል ብለዋል፡፡በዚህ አዋጅ
ክፍል ሁለት አንቀጽ 6 ላይ የሚኒስትሮች ም/ቤት አባላት በሚል የዘረዘራቸው ጠ/ሚኒስትሩን፣ምክትል /ጠ/ሚኒስትሩን፣የሚኒስትር መ/ቤቶችን የሚመሩ ሚኒስትሮች እና በጠ/ሚኒስትሩ የሚሰየሙ ሌሎች ባለስልጣኖች መሆናቸውን ደንግጓል፡፡
ይህው አስፈጻሚ አካላትን እንደገና ለማዋቀር የወጣው አዋጅ አንቀጽ 4 የምክትል ጠ/ሚኒስትሩ ሥልጣንና ተግባር
በሕገመንግስቱ በአንቀጽ 75 የተመለከተው እንደሚሆን በግልጽ አስቀምጧል፡፡
ባለሙያዎቹ ሹመቱ በተለይ ሕገመንግስቱን የጣሰ መሆን እንዳልነበረበት አስታውሰው በዚህ ሹመት መሰረት ጠ/ሚኒስትሩ
በማይኖሩ ጊዜ ማን ይተካቸዋል የሚለው ግልጽ የሆነ ምላሽ የለውም ሲሉ ተችተውታል፡፡
ጠ/ሚኒስትሩ የዚህን ዓይነት ሹመት መስጠት አይችሉም ያሉት ባለሙያዎቹ መስጠት ቢፈለግ እንኳን በቅድሚያ
ሕገመንግስታዊ ማሻሻያ መቅደም ነበረበት በማለት አካሄዱን ነቅፈዋል፡፡
ይህ በእንዲህ እንዳለ ሹመቱ በዛሬው እለት እንዲሰጥ የተፈለገው በነገው እለት በኦሮሚያ ምክር ቤት ውስጥ ይነሳል ተብሎ የሚጠበቀውን ውዝግብ ከአሁኑ ለማብረድ መሆኑን ምንጮች ጠቁመዋል።
የኦህዴዱን አቶ ሙክታር ከድርን ምክትል ጠቅላይ ሚኒስትር በማድረግ በኦሮሚያ ምክር ቤት ስብሰባ ላይ ነገ ይነሳል ተብሎ የሚጠበቀውን ውዝግብ ለማብረድ ታቅዶ በዛሬው እለት አዲሱ ሹመት ይፋ እንዲሆን መደረጉን የኢህአዴግ ኦህዴድ ምንጮች ገልጸዋል።
ዛሬ በሚጀመረው የኦሮሚያ ምክር ቤት ስብሰባ ላይ፣ የምክር ቤት አባላቱ በአቶ ሀይለማርያም ሹመትና ኦህዴድ ከጨዋታ ውጭ  ሆኗል በሚለው ዙሪያ ከፍተኛ ውዝግብ ይነሳል ተብሎ ይጠበቃል። አዲሱ ሹመት በኦህዴድ ውስጥ ተፈጥሮ የነበረውን ውዝግብ ያርግበው አያርግበው የታወቀ ነገር የለም። ይሁን እንጅ አቶ ደመቀ ምክትል ጠቅላይ ሚኒሰትር ተብለው ከተሾሙ በሁዋላ ሌሎች ተጨማሪ ምክትል ጠቅላይ ሚኒሰትሮች እንዲሾሙ መደረጉ በአራቱ ድርጅቶች ውስጥ ያለውን ፍትጊያ የሚያመላክት መሆኑን ተንታኞች ይናገራሉ።

በአየር መንገድ ውስጥ በጉልበት ስራ ላይ ይሰሩ የነበሩ ከ500 በላይ ሰራተኞች በኢህዴግ ፎረም አባላት ከነገ ጀምሮ ሊተኩ ነው


ህዳር ፳ (ሃያ) ቀን ፳፻፭ ዓ/ም
ኢሳት ዜና:-ስማቸው እንዳይገለጥ የፈለጉ የአየር መንገድ ሰራተኞች ለኢሳት እንደገለጡት ከነገ ጀምሮ ከ500 እስከ 700 መቶ የሚጠጉ የጉልበት ሰራተኞች ስራቸውን ይለቃሉ። በተለያዩ ቀጣሪ ኤጀንሲዎች ውስጥ ከ4 አመታት ላላነሰ ጊዜ በጉልበት ስራ ላይ ተሰማርተው የነበሩ ሰራተኞች የሚባረሩት የኢህአዴግ ፎረም አባላት አይደላችሁም ተብለው ነው። ሰራተኞች እንደገለጡት በፎረም ተጠናክረው ሲመጡ ተመልሰው ሊቀጠሩ እንደሚችሉ ቃል ተገብቶላቸዋል። በሚባረሩት ወጣቶች ቦታ በስልጠና ላይ አሉ በሺ የሚቆጠሩ የወጣት ፎረም አባላት ከነገ ጀምሮ ስራ ይጀምራሉ።
ኢህአዴግ በወሰደው እርምጃ ያዘኑ ሰራተኞች እንደገለጡት፣ የኢህአዴግ ፎረም አባላት አይደላችሁም በሚል ከስራ መባረራቸው ህገመንግስቱን የሚጥስ ብቻ ሳይሆን ሳንወድ በግድ ለእንጀራ ብለን ኢህአዴግን እንድንደግፍ የሚያደርግ ነው።
ኢህአዴግ በቀጣዩ የወረዳና የከተማ ምርጫ አሸናፊ ሆኖ ለመውጣት ያስችለው ዘንድ የወጣት ፎረም አባላትን በጊዜያዊ ስራ እየሸነገለ ነው በማለት ተቃዋሚዎች በተደጋጋሚ ወቀሳ ያቀርባሉ።
በተያያዘ ዜናም ኢህአዴግ አንዳንድ አባላቱን ከድርጅት አባልነት ያስወጣ በማስመሰል በወረዳዎች ውስጥ በሚገኙ የምርጫ ጣቢያዎች አስመራጮች አድርጎ ሊያሾም መሆኑን ከድርጅቱ የተገኘው መረጃ አመልክቷል።
በይፋ የማይታወቁ የድርጅቱ አባላት በገለልተኛ ስም በምርጫ አስፈጻሚነት ለማወዳደርና ለማሰራት መታቀዱን ነው ለማወቅ የተቻለው።

የመለስ ዜናዊን ህልፈት ተከትሎ በኦሮሚያ ክልል የተጀመረው የስልጣን ብወዛ መቀጠሉ ተዘገበ


ህዳር ፲፱ (አስራ ዘጠኝ) ቀን ፳፻፭ ዓ/ም
ኢሳት ዜና:-በዚህም መሰረት የአዳማ ከተማ ወይንም የናዝሬት ከተማ ከንቲባ ተነስተው በምትካቸው ሌላ ሰው መሾሙን ጉለሌ ፖስት የተባለው ድረ ገጽ ዘግቧል።
እርምጃው የኦህዴድን መካከለኛ አመራር የመጥረግ አካል እንደሆነም ተመልክቷል።
ከሩብ ሚሊዮን በላይ ህዝብ የሚኖርባት አዳማ ከተማ ከንቲባ አቶ ጉታ ላንቼሮ በድንገት ተነስተው በምትካቸው የኮሙኒኬሽን ሚኒስትር ዴኤታ ባካር ሻሊ እንደተኳቸውም ተመልክቷል።
ባለፉት ሶስት ወራት በሙስናና በአስተዳደር በደል ተወንጅለው 35 የዞንና የወረዳ ባለስልጣናት ከሀላፊነታቸው መባረራቸውን፤ ከነዚህ ውስጥ አስራ አንዱ የተባረሩት ከቦረና ዞን እንደሆነም በዘገባው ተመልክቷል።
የኦሮሚያ ክልል ጠቅላይ ፍርድ ቤት ፕሬዚዳንት አቶ ታደለ ነጌሶ እና ምክትል ፕሬዚዳንቱ አቶ ሰኢድ ጁንዲ በቅርብ ግዚያት ውስጥ ከስልጣን ከተባረሩ የክልሉ ሀላፊዎች ውስጥ የሚጠቀሱ ናቸው።
የኦህዴድ ስራ አስፈጻሚ አባል እና የሲቪል ሰርቪስ ሚኒስትሩ አቶ ጁነዲን ሳዶ ከኦህዴድ ስራ አስፈጻሚ ኮሚቴ አባልነት መባረራቸው የሚታወቅ ሲሆን ባለቤታቸውም በአሸባሪነት ተከሰው መታሰራቸው ይታወቃል።

ሆላንድ ካር በኪሳራ ለመዘጋት የበቃው በመንግስት በኩል አስፈላጊው ድጋፍ ባለመገኘቱ መሆኑ ተነገረ


ህዳር ፲፱ (አስራ ዘጠኝ) ቀን ፳፻፭ ዓ/ም
ኢሳት ዜና:-በኢትዮጵያ መኪና በመገጣጠም የመጀመሪያው በመሆን ሲሰራ የቆየው ሆላንድ ካር በኪሳራ ለመዘጋት የበቃው በመንግስት በኩል አስፈላጊው ድጋፍ ባለመገኘቱ መሆኑን የኩባንያውን ባለቤት የጠቀሱ ዘገባዎች አመልክተዋል።
በአዲስ አበባ ከተማ በእንግሊዘኛ ቋንቋ የሚታተመው ሳምንታዊው የቢዝነስ ጋዜጣ ካፒታል እንደዘገበው ለኩባንያው የኢትዮጵያ ልማት ባንክ ብድር ለመስጠት ፍቃደኛ አልሆነም።
የሆላንድ ካር ባለድርሻና ስራ አስኪያጅ ኢንጂነር ታደሰ ተሰማ ለካፒታል ጋዜጣ ከአምስተርዳም በሰጡት ቃለምልልስ በኢትዮጵያ የብር የመግዛት አቅም በአንድ ጊዜ በከፍተኛ ደረጃ በመውደቁ አስቀድመው ውል የገቡላቸውን መኪኖች በኪሳራ ገጣጥመው ለመሸጥ መገደዳቸውን አስረድተዋል።
በእዚህም በእያንዳንዱ አባይ መኪና ላይ ተጨማሪ 80 ሺህ ብር ከኪሱ እያወጣ ለተጠቃሚው ለማስተላለፍ መገደዱን፤ በአዋሽ መኪኖች ላይ ደግሞ ወጪው እስከ ሰላሳ ሺህ መድረሱን ዘርዝረዋል።
በብር አቅም መድከም ሳቢያ የተከተለውን ይህንን ችግር ለመሻገር ከኢትዮጵያ ልማት ባንክ ብድር ጠይቀው እንዳልተሳካላቸው ፤ ከቻይና የጠየቁት ብድር ደግሞ በመዘግየቱ ኩባንያው ለመክሰር መገደዱን አብራርተዋል።
ኩባንያው የገጠመውን ችግር ለመፍታት እንዲሁም በአዲስ አበባ ያለውን የትራንስፖርት እጥረት ለመቅረፍ ከአዲስ አበባ መስተዳድር ጋር በመነጋገር የጀመረው የአቶቡስ ግንባታ ፕሮጀክት ብዙ ርቀት ከሄደ በኋላ መስተዳድሩ ውሉን በማፍረሱ የኩባንያው ኪሳራ የከፋ እንዲሆን እንዳደረገውም በዘገባው ተመልክቶል። አሀዱ የሚባል አውቷቡስ አምርተው እንደነበርም አስታውሰዋል።

በጉዲፈቻ ወደ ዴንማርክ የመጣች ህጻን ለከፍተኛ የስነ አዕምሮ ችግር መዳረጓን ከዴንማርክ የደረሰን ዘገባ አመለከተ


ህዳር ፲፱ (አስራ ዘጠኝ) ቀን ፳፻፭ ዓ/ም
ኢሳት ዜና:-የዛሬ አራት አመት ከወላጅ እናቷና አባቷ ተረክበው ህጻኗን ከወንድሟ ጋር የወሰዷት የዴንማር ሰዎች ህጻኗ ለቤተሰቦቿ ያላትን ናፍቆት በየአጋጣሚው በመግለጽ እናቷ ጋር እንዲወስዷት በመጠየቅና ያልተለመደ ባህሪ እያሳየች ደስታ በማጣቷ ለህጻናት ማሳደጊያ እንደሰጧት የኢሳት ምንጮች ከዴንማርክ ገልጣለች::
ከዴንማርክ የደረሰን ይሀው መረጃ እንደሚያመለክተው የህጻኗ ማእሾ ታሪክ በዴንማርክ ከፍተኛ መነጋገሪያ የሆነ ሲሆን ቤተሰቦቿን ያነጋገረና የህጻኗን ወደ ሀገር ቤት በመመለስ ጽኑ ፍላጎት ያሳየ ዶክመንተሪ ፊልም ተሰርቶ በቴሌቭዥን መሰራጨቱን ለምንጮቻችን ገልጻለች::
በህጻኗና በወላጆቿ ፍላጎት ወደ ሃገር ቤት መመለስ በሚለውና የለም መመለስ የለባትም በሚለው ላይ የዴንማርክ ህዝብ ድምጽ እንዲሰጥ ተደርጎ 67 ከመቶው ህጻኗ ወደ ሀገሯ ትመለስ በማለት ድምጽ መስጠቱን ምንጮች አረጋግጠዋል::
17 ከመቶ የአፍ መፍቺያ ቋንቋዋን ረስታለችና መመለስ የለባትም ሲሉ 20 ከመቶዎቹ ድምጽ ከመስጠት መቆጠባቸውንም ለማወቅ ተችሏል::
በህጻኗ ህይወት ታሪክ ዙሪያ ተሰርቶ በተሰራጨው ዶክመንተሪ ፊልም የህጻኗ ወላጆች ልጃቸው እንድትመልስ እያለቀሱ ሲለምኑ የሚታይ ሲሆን  የህጻኗ ጤናን ያዛባ የስነ አእምሮ ችግርም ህጻኗ እንዳጋጠማትም ፊልሙን የተመለከተው ምንጫችን ከዴንማርክ በስልክ ገልጻለች::
የዴንማርክ ዜጋ አንድ ህፃን ወደ ሃገሩ ሲያመጣ ከ450 ሺህ ብር በላይ ገንዘብ እንደሚከፍል የምንጮቻችን ዘገባ ያመለክታል::

በናዝሬት በአንድ አመት ውስጥ ብቻ 4 ከንቲባዎች ተቀያየሩ


ህዳር ፲፱ (አስራ ዘጠኝ) ቀን ፳፻፭ ዓ/ም
ኢሳት ዜና:-በቅርቡ በተደረገ ግምገማ ላለፉት አራት ወራት በስልጣን ላይ ቆይተው የነበሩት የናዝሬት ወይም የአዳማ ዋና ከንቲባ እና ከእኝሁ ባለስልጣን ጋር ግንኙነት አላቻው የተባሉት የከተማዋ የኦህዴድ የድርጅት ጉዳይ ሀላፊ ከቦታቸው እንዲነሱ ተደርጓል።
ገምጋሚዎቹ የኦሮሚያ ክልል ባለስልጣናት የነበሩ ሲሆን ግምገማውም በመልካም አስተዳዳር፣ በከተሞች እድገት፣ በኪራይ ሰብሳቢነትና በልማት ሰራዊት አደረጃጃት ላይ ያተኮረ ነበር።
የከተማው ከንቲባ የነበሩት አቶ ጉታና የከተማው የልማት ሀላፊ የነበሩት አቶ ከፍያለው የከተማዋን መሬት በመቸብቸባቸው ፣ ህዝብ ያሰማውን ሮሮ ተከትሎ እንዲወርዱ ተደርጓል።
ከእርሳቸው በፊት የነበሩት 3ቱ ከንቲባዎችም እንዲሁ መሬት በመቸብቸብና በሙስና ከሀላፊነት መነሳታቸው ይታወቃል። ከንቲባው አቶ ጉታ የፓርላማ አባል ሲሆኑ፣ በከተማዋ ውስጥ የሚታየውን የአስተዳዳር ብልሹነትና ስር የሰደደውን ሙስና እና መሬት ዝርፊያ ያስቆማሉ ተብሎ እምነት ተጥሎባቸው ነበር። ይሁን እንጅ ባለስልጣኑ ከሌሎች ግብረአበሮቻቸው ጋር በመሆን ከፍተኛ ሙስና ውስጥ መግባታቸው ለማወቅ ተችሎአል።
የድርጅት ቢሮ ሀላፊው አቶ ሳዳት በበኩላቸው በአዳማ ውስጥ ባሉ የሀላፊነት ቦታዎች ላይ የሚገኙ ሰዎችን እንዲመደቡ ያደረጉዋቸው ከአርሲ አካባቢ የተወለዱትን ብቻ ነው በሚል በዘርኝነት ተገምግመው ወርደዋል።
አንድ የኦህዴድ የማእከላዊ ኮሚቴ አባል ለኢሳት እንደገለጹት የድርጅቱ መሪዎች ከላይ እስከታች በሙስና የተዘፈቁ በመሆናቸው ፣ በየአካባቢው እየተገመገሙ የሚወርዱ የከተማ ከንቲባዎችና የድርጅት አመራሮች ወደ ሌሎች ቦታዎች ተመልሰው ይመደባሉ። በዚህም የተነሳ ሙስና ውስጥ የተዘፈቀ ባለስልጣን ምንም ችግር ሳይገጥመው ወደ ሌላ አካባቢ ሄዶ ይመደባል ብለዋል። በናዝሬት ውስጥ የሚታየው አይን ያወጣ የመሬት ዝርፊያ ፣ ነዋሪውን በእጅጉ እያሳሰበ ይገኛል።

መንግስት በመላ አገሪቱ ሙስሊሞችን እያስገደደ ለተቃውሞ ሰልፍ ሊያስወጣ ነው


ህዳር ፲፱ (አስራ ዘጠኝ) ቀን ፳፻፭ ዓ/ም
ኢሳት ዜና:-ከኢህአዴግ ምንጮች የተገኘው መረጃ እንደሚያመለክተው በአገሪቱ ውስጥ በሚገኙና መንግስት በሙስሊሙ ላይ በሚፈጽመው ኢሰብአዊ  ድርጊት የተነሳ ተቃውሞ ያስነሳሉ በተባሉ አካባቢዎች በሙሉ ፣ መንግስትን የሚደግፉ ሰልፎች ይደረጋሉ።
አብዛኛው ህዝብ ተገዶ እንዲወጣ፣ የድርጅት አባላት ከፍተኛ ተልእኮ እንደተሰጣቸው ለማወቅ ተችሎአል።
በዛሬው እለትም በቅርቡ የመንግስት ታጣቂዎች 4 ሰዎችን በገደሉበት ገርባ እና ደጋን መንግስትን የሚደግፉ ሰልፎች ተደርገዋል።
የሰልፉ ዋና አላማ በፍርድ ሂደት ላይ የሚገኙት የድምጻችን ይሰማ የሙስሊም ኮሚቴ አባላት አሸባሪዎች ናቸው የሚል መልእክት ለማስተላለፍ ነው።
ኢህአዴግ በኮሚቴ አባላቱ ላይ ለፍርድ ቤቱ ጠንካራ ማስረጃ ማቅረብ ባለመቻሉ በዳኞች ላይ ተጽኖ ለመፍጠር ማሰቡን የደረሰን መረጃ ያመለክታል።

ተቃዋሚ ፓርቲዎች የምርጫ መወዳደሪያ ምልክት ላለመውሰድ ወሰኑ


ህዳር ፲፱ (አስራ ዘጠኝ) ቀን ፳፻፭ ዓ/ም
ኢሳት ዜና:-በ2005 ዓ.ም ለሚደረገው የአዲስ አበባ ከተማና የአካባቢ ምርጫ የጊዜ ሰሌዳ ላይ ከፓርቲዎች ጋር ለመነጋገር በአዳማ ከተማ ምርጫ ቦርድ በጠራው ስብሰባ ፒቲሽን የተፈራረሙት የ34 ፓርቲዎች ህብረት፤ የምርጫ ችግሮች ሳይፈቱ  የመወዳደሪያ ምልክታቸውን እንደማይወስዱ በአንድ ድምጽ መወሰናቸው ታወቀ፡፡
34ቱ ፓርቲዎች  የምርጫ ምልክት ላለመውሰድ የወሰኑት ፤ ህዳር 8 ቀን 2005 ዓ.ም በመላው  ኢትዮጵያ አንድነት ድርጅት /መኢአድ/ ጽ/ቤት ባደረጉት ስብሰባ  ነው።
የ34ቱ ፓርቲዎች ጊዜያዊ አስተባባሪ ኮሚቴ ሰብሳቢ የሆኑት የአንድነት ፓርቲ  ዋና ፀሐፊና የመድረክ ሥራ አስፈፃሚ የሆኑት አቶ አስራት ጣሴ በጉዳዩ ዙሪያ ፍኖተ-ነፃነት ላቀረበላቸው  ጥያቄ በሰጡን መልስ፦ “እውነት ነው፡፡ ህዳር 8 ቀን 2005 ዓ.ም  በመኢአድ ጽ/ቤት ተሰብስበን ነበር፡፡ ያለፈው ስብሰባ ቃለ ጉባኤ  ተነቦና መጠነኛ መሻሻል ተደርጐበት ፀድቋል>>ብለዋል።
ሰነዱ የሁሉም ፓርቲዎች ሰነድ ሆኖ እንዲፀድቅ  መደረጉን የጠቀሱት አቶ አስራት፤ የኮሚቴው የሥራ እንቅስቃሴ ሪፖርት እንደቀረበና    ውይይት እንደተደረገበት፤ እንዲሁም ኮሚቴው  በአጭር ጊዜ ውስጥ ባከናወናቸው ተግባራት አድናቆትን እንዳገኘ ገልጸዋል፡፡
የብሔራዊ  ምርጫ ቦርድ ፀሐፊ አቶ ነጋ ጠርተው  ሲያነጋግሯቸው፦<< ተፈራርማችሁ ባታመጡም ቦርዱ ፓርቲዎችን ለማወያየት እቅድ ይዞ  ነበር፡፡ ይህንን ያህል ማጯጯህ ለምን አስፈለገ? የቦርዱ ሰብሳቢና ም/ሰብሳቢ ከአገር ውጪ ስለሄዱ ነው፡፡ ሲመጡ ያነጋራችኋል” እንዳሏቸው ጠቅሰዋል፡፡
<< እኛ ደግሞ ለምን እንደ ጮህን  በ2002 ዓ.ም የተደረገውን  የዝርፊያ ምርጫ በመጥቀስ  ነግረናቸዋል>>ያሉት አቶ አስራት <<ከዚህም በላይ  ብዙ ማለት እንደሚቻል አስረድተናቸው ተመልሰናል” ብለዋል።
በተያያዘ ዜና በሞት፣ አንድነት ፓርቲ በሥራ ዝውውርና በተለያየ ምክንያት በተጓደሉ የብሔራዊ ም/ቤቱ አባላት ምትክ ዘጠኝ አመራሮችን  ተክቷል፡፡
ከተተኩት ውስጥ አምስቱ ተለዋጭ  አባላት የነበሩ ሲሆኑ የፓርቲው መተዳደሪያ ደንብ ለብሔራዊ ም/ቤቱ በሚሰጠው
ሥልጣን መሠረት አራቱ በቀጥታ ከአባላት  ተመርጠው ብሔራዊ ም/ቤቱን ተቀላቅለዋል፡

የብር ዋጋ እየወደቀ ነው ተባለ


ህዳር ፲፱ (አስራ ዘጠኝ) ቀን ፳፻፭ ዓ/ም
ኢሳት ዜና:-የአንድ ዶላር የምንዛሪ ዋጋ በ17 በመቶ ጨምሮ በ16.35 ብር እንዲመነዘር የኢትዮጵያ ብሔራዊ ባንክ መወሰኑ ይፋ ከተደረገበት መስከረም 2003 ዓ.ም. ወዲህ ባሉት ሁለት ዓመታት፣ የብር ምንዛሪ አቅም እየቀነሰ ከ10 በመቶ በላይ ወርዷል ሲል የዘገበው ሪፖርተር ነው።
በኅዳር 2004 ዓ.ም. የየዕለቱ የውጭ ምንዛሪ ዋጋን በሚያመለክተው መረጃ መሠረት የአንድ ዶላር አማካይ የምንዛሪ ዋጋ 17 ብር  ከ20 ሳንቲም የነበረ ሲሆን፣ በኅዳር 2005 ዓ.ም. ያለው መረጃ የአንድ ዶላር የምንዛሪ ዋጋ ወደ 18. ብር ከ20 ሳንቲም ከፍ ብሎአል፡፡
ከኅዳር 2003 ዓ.ም. እስከ ኅዳር 2004 ዓ.ም. የነበረው የምንዛሪ ዋጋ ከ5.3 በመቶ በላይ ሲጨምር፣ በ2005 በጀት ዓመት የኅዳር ወር የምንዛሪ ዋጋ በአማካይ ወደ 18. ብር ከ20 ሳንቲም  ማደጉን ተከትሎ ከሌሎች መገበያያ ገንዘቦች አኳያ የብር የመግዛት አቅምን በአንድ ዓመት ከ5.56 በመቶ በላይ እንዲወርድ አድርጎታል፡፡ በአጠቃላይ ከኅዳር 2003 ዓ.ም. ወዲህ የብር የመግዛት አቅም በ30 ከመቶ እንዲወድቅ ምክንያት ሆኗል፡፡
ባለፉት ሁለት ዓመታት የታየው የምንዛሪ ለውጥ ግን በመስከረም 2003 ዓ.ም. በብሔራዊ ባንክ በአንዴ ከተደረገው ጭማሪ በተቃራኒው ቀስ በቀስ በየዕለቱ ይካሄድ በነበረው የውጭ ምንዛሪ ግብይት ላይ ተመርኩዞ እየጨመረ የመጣ ብሎአል ጋዜጣው፡፡
የዋጋ ግሽበት በሚፈለገው ደረጃ ሊቀንስ ካልተቻለባቸው ምክንያቶች አንደኛው የብር አቅም መዳከምና የውጭ ምንዛሪ ጉልበት በየጊዜው እያደገ መምጣቱ ነው በማለት ባለሙያዎችን በመጥቀስ ጋዜጣው ዘግቧል፡፡

ባለፉት 10 አመታት በአዲስ አበባ የተገነባው ከአጼ ሚኒሊክ ጀምሮ ከተገነባው ይበልጣል ሲሉ አቶ ኩማ ደመቅሳ ተናገሩ


ህዳር ፲፱ (አስራ ዘጠኝ) ቀን ፳፻፭ ዓ/ም
ኢሳት ዜና:-ከንቲባው ይህን የተናገሩት  በቅርቡ የአዲስ አበባ 125ኛ አመት ክብረ በአል ሲጠናቀቅ ባደረጉት የመዝጊያ ንግግር ነው።
አቶ ኩማ ከተማዋን የቆረቆሩትን እና በከተማዋ ላይ አሻራቸውን ያሳረፉትን በሙሉ በማውገዝ የኢህአዴግን ስራ ለማሞካሸት ሞክረዋል።
በነገሥታቱ ዘመን የከተማዋ የመሬት ይዞታ ለመኳንንት፣ ለመሳፍንትና ለጦር አበጋዞች ተከፋፍሎ አብዛኛው የከተማዋ ነዋሪዎች ሲሰቃዩ እንደኖሩ፣ የከተማዋ ዕድገት ማስተር ፕላንን ያልተከተለ በመሆኑና በመኳንንቱና በመሳፍንቱ ግላዊ ፍላጐት ተወስኖ ቆይቷል ሲሉ ነው ከንቲባው የገለጹት።
ባለፉት አሥር ዓመታት  በከተማዋ በሁሉም መስኮች የተገኘው ውጤትና እየታየ ያለው ለውጥ፣ ከመቶ ዓመታት በላይ በከተማዋ ተሠርተው ከነበሩት ልማቶች በብዙ እጥፍ ይበልጣል በማለት ነው አቶ ኩማ የተናገሩት።
አዲሱ ምክትል ጠቅላይ ሚኒሰትርና የትምህርት ሚኒሰትሩ አቶ ደመቀ መኮንን ፣ ‹‹ነዋሪዎቿ በቀጥታ ተሳትፈው የዕድገት ምህዋር ውስጥ ገብታ የዓለም አቀፍና የአፍሪካ መዲና ሆና የወጣችው  ካለፉት ሁለት አሥርተ ዓመታት ወዲህ ነው፤›› በማለት የአቶ ኩማን ንግግር አጠናክረዋል፡፡
ከተማዋን የቆረቆሩት አጼ ሚኒሊክም ሆኑ እቴጌ ጠሐይቱ እንዲሁም አጼ ሀይለስላሴ በጊዜው በፈቀደላቸው ቴክኖሎጂና በነበራቸው የገንዘብ አቅም እና እውቀት ለአዲስ አበባ ማደግ ከፍተኛ አስተዋጽኦ ማድረጋቸውን የታሪክ ባለሙያዎች ይናገራሉ።
አጼ ሀይለስላሴ አፍሪካ አንድነት ድርጅትንና የአለም የኢኮኖሚ ኮሚሽን ጽህፈት ቤት አዲስ አበባ እንዲሆን የታገሉና አዲስ አበባ ዛሬ ላገኘችው አለማቀፍ ክብር ከፍተኛ አስተዋጽኦ  ማድረጋቸውን ድርሳናት ያወሳሉ።
የአቶ መለስ መንግስት በአዲስ አበባ ላይ ከፍተኛ መዋለ ንዋይ በማፍሰስ ከተማዋ እንድትለማ ያደረገው ከምርጫ 97 በሁዋላ በአዲስ አበባ የደረሰበትን ሽንፈት ተከትሎ መሆኑን ታዛቢዎች ይናገራሉ።
ያም ሆኖ በከተማዋ የሚኖሩ ነዋሪዎች አሁንም በመሰረተ ልማት አቅርቦት በተለይም በውሀና በመብራት እጦት በእጅጉ እየተማረሩ ነው። ቤታቸው እየፈረሰባቸው ያለ በቂ ካሳ መንገድ ላይ እንዲያድሩ የተደረጉትም ቁጥራቸው ቀላል አለመሆኑን ኢሳት በተደጋጋሚ ሲዘግብ ቆይቷል።
አቶ ኩማ በከተማዋ  የሚታየውን የመሬት ዝርፊያ ለማስቆም ሳይችሉ ኢህአዴግን ከነገስታቱ ዘመን ጋር ለማወዳደር መቻላቸው ለትችት ዳርጎአቸዋል። አዲስ አበባ ከሌሎች የአፍሪካ አገሮች ጋር ስትነጻጸር አሁንም ኋላ የቀረች ከተማ ነች።

Tuesday, November 27, 2012

የኢትዮጵያ ሕዝብ አርበኞች ግንባር በጃንሱማ ጥቃት ፈጸመ።


የኢትዮጵያ ሕዝብ አርበኞች ግንባር በጃንሱማ ጥቃት ፈጸመ።

EPPF Training Camp

የኢትዮጵያ ሕዝብ አርበኞች ግንባር ሰራዊት በወያኔ ቅጥረኛና ምንደኛ የልዩ ሃይል ታጣቂ ቡድን ላይ የጀመረውን የማጥቃት ዘመቻ አጠናክሮ በመቀጠል ሕዳር 15-2005 ዓ.ምአርማጭሆ ሳንጃ ወረዳ ልዩ ስሙ ጃንሱማ በተባለ ቦታ ባደረገው ውጊያ 14 የጠላት ወታደሮችን በመግደልና 12 በማቁሰል ከፍተኛ ወታደራዊ ድሎችን በማስመዝገብ ግንባሩ የተሰማራበትን ግዳጅ በድል እየተወጣ መሆኑን የግንባሩ ወታደራዊ መምሪያ አስታውቋል።

የኢትዮጵያ ሕዝብ ከዘራፊውና ከነፍሰ-ገዳዩ የወያኔ አምባገነናዊ ገዥ ቡድን ለማላቀቅ ያለው ብቸኛ አማራጭ መንገድ በትጥቅ ትግል ስርዓቱን ማንበርከክ መሆኑን ጠንቅቆ ያወቀው የኢትዮጵያ ሕዝብ አርበኞች ግንባር ሰራዊት ሀገርንና ወገንን ለመታደግ ቆርጦ በመነሳት በሰሜኑ የሐገራችን ክፍል ወታደራዊ ስትራቴጅውን ነድፎ እየተንቀሳቀሰ መሆኑ የሚታወቅ ሲሆን፣ ሰሞኑን አርማጭሆ ሳንጃ ወረዳ ልዩ ስሙ ጃንሱማ በተባለው ቦታ ባደረገው የማጥቃት ዘመቻ 26 የጠላት ወታደሮችን ሙትና ቁስለኛ በማድረግ ወታደራዊ የበላይነትን የተቀዳጀ ሲሆን፣ ከሞቱት 14 የልዩ ሃይል ታጣቂ ቡድን መካከል አበበ የሚባለው የቀራቅር ተወላጅና አለልኝ የሚባል የደባርቅ ተወላጅ የሆኑት ከፍተኛ አመራሮች መሞታቸውን የኢትዮጵያ ሕዝብ አርበኞች ግንባር ወታደራዊ መምሪያ ገልጿል።

ይህ በእንዲህ እንዳለ የኢትዮጵያ ሕዝብ አርበኞች ግንባር ሰራዊት አርማጭሆ ሳንጃ ወረዳ ልዩ ስሙ ጃንሱማ በተባለ ቦታ በፈፀመው ወታደራዊ የማጥቃት ዘመቻና በጠላት ላይ ባደረሰው ከፍተኛ ኪሳራ የተደናገጠው የወያኔ ቡድን ተጨማሪ ጦር ወደ አካባቢው እያጓጓዘ መሆኑንም ከአካባቢው የተሰራጩ የዜና ምንጮች አጋልጠዋል።

ይሁን እንጅ በዓላማቸው ፅናትና በሐገራዊ ፍቅር የተገነባው የኢትዮጵያ ሕዝብ አርበኞች ግንባር ሰራዊት በጀመረው ሕዝባዊና ሐገራዊ ተልዕኮ የፈረጠመ ክንዱን በጠላት ላይ በማሳረፍ አይበገሬነቱንና ቁርጠኝነቱን ሰሞኑን በተከታታይ ባደረጋቸው ውጊያዎች አስመስክሯል ሲሉ የአካባቢው ነዋሪዎች ገልፀዋል።

በመጨረሻም ውጊያው በተፈፀመባቸው አካባቢዎች የሚኖሩ የሕብረተሰብ ክፍሎች የኢትዮጵያ ሕዝብ አርበኞች ግንባር ሰራዊት የጀመረውን ወታደራዊ የማጥቃት ዘመቻ አጠናክሮ እንዲገፋበትና እኛም የተለመደውን ሁለንተናዊ ድጋፍ ከማድረግ ባሻገር ግንባሩን ለመቀላቀል የሚያስችል መነሳሳትን የፈጠረ አኩሪ የአርበኝነት ገድል መፈፀሙን ነዋሪዎች አስታውቀዋል።

የኢትዮጵያ ሕዝብ አርበኞች ግንባር በበኩሉ በስልጣን ላይ ያለው ፀረ-ሕዝብና ፀረ-ኢትዮጵያ ወንጀለኛ የወያኔ ቡድን የመጨረሻ ግብዓተ-መሬቱ እስኪፈፀም ድረስ ወታደራዊ የማጥቃት ዘመቻውን አጠናክሮ እንደሚቀጥል ገልፆ የአገዛዙን እድሜ ለማሳጠርም የተለመደው ሕዝባዊ ድጋፍ ተጠናክሮ እንዲቀጥል ለመላው ነፃነት ናፋቂና ሀገር ወዳድ ኢትዮጵያዊያን ሀገራዊ መልዕክቱን አስተላለፏል።

የኢትዮጵያ ሕዝብ አርበኞች ግንባር

ESAT Daliy News-Amsterdam Nov 27 2012 Ethiopia


በኢትዮጵያ ከግማሽ ሚሊዮን በላይ ጎዳና ተዳዳሪዎች አሉ


ህዳር ፲፰ (አስራ ስምንት) ቀን ፳፻፭  ዓ/ም
ኢሳት ዜና:-በአዲስ አበባ ከተማ ከአንድ መቶ ሺህ በላይ ጎዳና ተዳዳሪዎች መኖራቸውን የተባበሩት መንግስታት የህጻናት መርጃ ድርጅት ጥናት አመለከተ።
የኢትዮጵያ መንግስት ማእከላዊ ስታትስቲክ መስሪያ ቤት ደግሞ በአዲስ አበባ ያሉት ጎዳና ተዳዳሪዎች 60 000 ብቻ ናቸው የሚል መረጃ አሰራጭቷል።
የተባበሩት መንግስታት የአለም አቀፉ የህጻናት መርጃ ድርጅት ዩኒሴፍ እንዳመለከተው በኢትዩኦጵያ በአጠቃላይ ከግማሽ ሚሊዮን በላይ ጎዳና ተዳዳሪዎች ሲኖሩ ከዚህ ውስጥ አንድ መቶ ሺዎቹ በርዕሰ መዲናዋ አዲስ አበባ ይገኛሉ።
የኢትዮጵያ ማእከላዊ ስታትስቲክ መስሪያ ቤት በአጠቃላይ በኢትዮጵያ የሚገኙ ጎዳና ተዳዳሪዎች 150 000 ብቻ ናቸው ሲል አመልክቷል። ከዚህ ውስጥ አንድ ሶስተኛው ወይንም 60 000 ሺዎቹ በአዲስ አበባ ይገኛሉ ብሎል።
አለም አቀፍ ተቋማት የሚያወጡትን መረጃ የኢትዮጵያ መንግስት የማይቀበልባቸው አጋጣሚዎች የበዙ ናቸው። የአለም ጤና ድርጅት ከአለም ባንክ ጋር በጋራ ባወጡት ሪፖርት ከኢትዮጵያ ህዝብ ውስጥ 17.6 በመቶ ወይም 14 ሚሊዮን ህዝብ የአካል ጉዳተኛ ነው ማለታቸው ሲታወስ አዲሱ ጠቅላይ ሚኒስትር ሀ/ማሪያም ደሳለኝ ሳይንሳዊ በሆነ መንገድ አልተጠናም በማለት መቃወማቸው ተዘግቧል።

በአዲስ አበባ በሺዎች የሚቆጠሩ ቤቶች ፈርሰዋል


ህዳር ፲፰ (አስራ ስምንት) ቀን ፳፻፭  ዓ/ም
ኢሳት ዜና:-የአዲስ አበባ መስተዳድር በአዲስ አበባ ከተማ በሁለት ክፍለ ከተሞች ብቻ ያፈረሳቸው ቤቶች በሺዎች የሚቆጠሩ መሆናቸውን አዲስ አበባ ከተማ የሚታተመው አዲስ ፎርቹን ጋዜጣ ዘገበ ።
ሳምንታዊው የእንግሊዘኛ ጋዜጣ አዲስ ፎርቹን እሁድ ዕለት እንደዘገበው በቦሌ ክፍለከተማና በንፋስልክ ላፍቶ ክፍለ ከተሞች የፈረሱ ቤቶች 7ሺህ ደርሰዋል። መስተዳድሩ ከገበሬዎች በግዢ ወደ ነዋሪዎች የተላለፉት መሬቶች ሕጋዊ ማረጋገጫ የላቸውም በመለት እንዳፈረሳቸውም ተመልክቶዋል።
በንፋስልክ ላፍቶ ክፍለ ከተማ በሐና ማርያም አካባቢ እንዲሁም በቦሌ ክፍለ ከተማ በቡልቡላ አካባቢ ህገ-ወጥ በሚል በአጭር ቀናት መስጠንቀቂያ የፈረሱት ቤቶች 7ሺህ መድረሳቸውን የገለጸው አዲስ ፎርቹን ጋዜጣ መስተዳድሩ ባስጠናው ጥናት በአዲስ አበባ ያለውን የቤት እጥረት ለመፍታት ተጨማሪ 360 ሺህ ቤቶች መገንባት እንደሚኖርባቸው አመልክቶዋል።
ከምርጫ 1997 ወዲህ በከተማዋ ሕገ-ወጥ ቤቶች መስፋፋታቸውን ከህዳር 2003 ጀምሮም ይኸው ሁኔታ መቀጠሉን ከዘገባው መረዳት ተችሎአል።
የአቶ መለስ መታመም መሰማቱና ሞታቸው መከተሉ ተጨማሪ ቤቶች እንዲገነቡ ምክንያት እንደሆነም አዲስ ፎርቹን ካጠናቀረው ዘገባ መረዳት ተችሎዋል።
ሰለባዎቹን በማነጋገር በአዲስ አበባ ከተማ በተለይ በሐና ማርያም አካባቢ ከ30 ሺህ ሰዎች በላይ መፈናቀላቸውን መዘገባችን ይታወሳል።

839 ሺህ 580 ኢትዮጵያውያን የፌስቡክ ተጠቃሚ ናቸው


ህዳር ፲፰ (አስራ ስምንት) ቀን ፳፻፭  ዓ/ም
ኢሳት ዜና:-ከዓለማችን በሕዝብ ቁጥር ከቀደሚዎቹ 15 ሐገራት ውስጥ የምትገኘው ኢትዮጵያ በማህበራዊ ሚዲያ በ88ኛ ደረጃ ላይ መገኘትዋን አንድ ጥናት አረጋገጠ ።
ሶሻል ቤከርስ የተባለ ተቐም ይፋ ባደረገው መረጃ ከኢትዮጵያ ሕዝብ ውስጥ ከማህበራዊ መገናኛ ማለትም ፌስ ቡክ የሚጠቀሙ ከ1 በመቶ በታች 0.95 በመቶ ሲሆኑ በቁጥር ሲቀመጥ 839 ሺህ 580 ኢትዮጵያውያን የፌስቡክ ተጠቃሚ ናቸው ።
ከቀደመው ዓመት ጋር ሲነፃጸር 27.4 በመቶ መጨመሩንም ከወጣው ጥናት መረዳት ተችሎአል። ይህም በአንድ አመት ውስጥ ተጨማሪ 180 ሺህ 800 ኢትዮጵያውያን የፌስ ቡክ ተጠቃሚ መሆናቸውን ያስረዳል። በህዝብ ቁጥር ከኢትዮጵያ በግማሽ የምታንሰው ኬንያ በፌስ ቡክ ተጠቃሚዎች ቁጥር ከኢትዮጵያ በዕጥፍ እንደምትበልጥ ከጥናቱ መረዳት ተችሎዋል።
አንድ ነጥብ 9 ሚሊዮን ኬንያውያን የፌስ ቡክ ተጠቃሚ ሲሆኑ ከአምናው ጋር ሲነፃፀር በ327ሺህ 440 ጨምሮ ተገኝቶዋል ። የኬንያውያን የፌስ ቡክ ተጠቃሚዎች ቁጥር አሁንም በመጨመር ላይ መሆኑን ባለፈው ሳምንት ብቻ የተመዘገበው ዕድገት 4.78 መድረሱ ጠቐሚ ሆንዋል። ባለፈው ሳምንት ኢትዮጵያ ያስመዘገበችው ዕድገት 0.95 ከመቶ ነው።

አቶ ሀይለማርያም ደሳለኝ ካቢኔ አያዋቅሩም ተባለ


ህዳር ፲፰ (አስራ ስምንት) ቀን ፳፻፭  ዓ/ም
ኢሳት ዜና:-በሟቹ የቀድሞ ጠ/ሚኒስትር እግር የተተኩት ጠ/ሚኒስትር አቶ ኃይለማርያም ደሳለኝ አዲስ ካቢኔ እንደማያዋቅሩ
ለኢህአዴግ ቅርበት ያላቸው ምንጮች ጠቆሙ፡፡
 ምንጮቹ  አዲስ ካቢኔ የማይዋቀረው በምርጫ አሸንፎ የመጣ አዲስ ጠ/ሚኒስትር ባለመኖሩ ነው ብለዋል፡፡
አቶ ኃለማርያም በአቶ መለስ እግር የተተኩ በመሆናቸው አዲስ ካቢኔ ለፓርላማ አቅርበው የሚያጸድቁበት ምንም
ምክንያት የለም ብለዋል  ምንጮቹ፡፡
በዚህም ምክንያት የካቢኔ ሹም ሽር ሊያደርጉ ይችላሉ ተብሎ በአንዳንድ ወገኖች ሲጠበቅ የነበረውን የማይሆን ነው ብለዋል።
አቶ ኃይለማርያም ከተሾሙ በኃላ ባሉት ሁለት ወራት ጊዜያት ውስጥ የሰጡት ሁለት ሹመቶችን ነው፡፡ አንዱ ቃለመሃላ
በፈጸሙበት ዕለት ለፓርላማ አቅርበው ያስጸደቁት የምክትል ጠ/ሚኒስትርና የትምህርት ሚኒስትር አቶ ደመቀ መኮንን
ሹመት ሲሆን ሌላኛው በውጪ ጉዳይ ሚኒስቴር ሚኒስትር ዴኤታ ሆነው ሲያገለግሉ የነበሩትን አቶ ብርሃነ ገ/ክርስቶስ
ተጠባባቂ የውጪ ጉዳይ ሚኒስትር አድርገው መሾማቸው ነው፡፡
ይህም ሆኖ ግን የሲቪል ሰርቪስ ሚኒስትሩ አቶ ጁነዲን ሳዶ የትዳር አጋራቸው በሽብርተኝነት በመከሰሳቸውና እሱንም
ተከትሎ በኦህዴድ በመገምገማቸው ከመንግስታዊ የሚኒስትርነት ኃላፈነታቸው እንደሚነሱ የሚጠበቅ ሲሆን መቼ ይሆናል
የሚለው ለጊዜው እንደማይታወቅ ተጠቁሟል፡፡
በተጨማሪም ኦህዴድ በፓርላማ የመንግስት ተጠሪ ሚኒስትርና የኦህዴድ
ጽ/ቤት ኃላፊ የሆኑት ወ/ሮ አስቴር ማሞ ከፌዴራል ኃላፊነታቸው ተነስተው ወደ ክልሉ እንዲዛወሩ መወሰኑን የአገር
ቤት ጋዜጦች መዘገባቸው የሚታወስ ቢሆንም ይህም ክፍተት በሚኒስትር ዴኤታ እየተሸፈነ እንደሚቆይ ምንጫችን
ጠቅሶአል፡፡
አቶ ሀይለማርያም ካቢያቸውን ለመሾም ያልቻሉት በኢህአዴግ ውስጥ በተለይም በኦህዴድ ውስጥ በተፈጠረ ሽኩቻ ነው የሚሉ ዘገባዎች ሲቀርቡ እንደነበር ይታወሳል።

በሽብር ወንጀል ተከሰው በእስር ላይ በሚገኙት 31 ሰዎች ላይ የክስ መቃወሚያ ቀረበ


ህዳር ፲፰ (አስራ ስምንት) ቀን ፳፻፭  ዓ/ም
ኢሳት ዜና:-አቃቢ ህግ በእነ ኡስታዝ አቡበክር አህመድ መዝገብ በሽብርተኝነት በተከሰሱት የድምጻችን ይሰማ የኮሚቴ አባላት ላይ ያቀረበው ክስ ህገመንግስቱን የጣሰ ና በርካታ የህግ ድንጋጌዎች ግድፈት ያለበት መሆኑን በዝርዝር በመጥቀስ ነው፣ የተከሳሾች ጠበቆች ተቃውሞአቸውን ለፌደራሉ ከፍተኛው ፍርድ ቤት 4ኛ ወንጀል ችሎት ያቀረቡት።
ጠበቆቹ 7 ገጾች ያሉት ህገመንግስቱን የተመለከቱና 24 ገጾች ያሉት ዝርዝር መቃወሚያዎችን አቅርበዋል።
በተከሳሾች ላይ የቀረበው ክስ  ህግ ህገ-መንግስታዊ ባለመሆኑ ክሱም የማያስከስስ ግልፅ ያልሆነ እና ተከሳሾች በዚህ ሁኔታ ክሱን አውቀውት ሊከላከሉ የማይችሉ መሆኑን ጠበቆች በተቃውሞአቸው ገልጸዋል።
በዝርዝር ባቀረቡት መቃወሚያ ደግሞ ” ተከሳሾች በአንቀጽ 3 እና 4 በአንድ ላይ ሊከሰሱ አይገባም፣ የአቃቢ ህግ  የክስ አቀራረብ በአንዱ መክሰስ ባይሳካ በሌላው ይሳካ ይሆናል በሚል የተሳሳተ ግምት በግልጽ የወንጀለኛ መቅጫ ህግ ሥነስርአትን፣ የወንጀል ህግ መርህን እና ህገመንግስትን የሚጥስና  ክሱም ከህግ ውጪ የቀረበ ነው።” በማለት ገልጸዋል።
አቃቤ ህግ ያቀረበው ክስ አግባብነት ባላቸው የወንጀል ህጎች እና የወንጀለኛ መቅጫ ስነስርአት ተከትሎ ያልቀረበ በመሆኑ እና በዚሁ ክስም የተገለጹት ድርጊቶች በወንጀል የማያስጠይቁ በህግ የተፈቀዱ መብቶች እና ተግባራት በመሆናቸው ተከሳሾችን ለመክስ የሚያበቃ በቂ ምክንያት የለም ሲሉም ጠበቆች ተቃውመዋል።
የኢትዮጵያ መንግስት ተከሳሾች በሽብር ተግባር ላይ መሰማራታቸውን የሚያመለክት ጠንካራ ማስረጃ ሊያቀርብ አለማቻሉን ተከትሎ፣ እስረኞችን እንዲፈታ አለማቀፍ ጫናው በዝቶበታል።

በአላማጣ ታፍነው የተወሰዱ ከ20 በላይ ሰዎች የደረሱበት አልታወቀም


ህዳር ፲፰ (አስራ ስምንት) ቀን ፳፻፭  ዓ/ም
ኢሳት ዜና:-በራያና አዘቦ ፣ በአላማጣ ከተማ ከኤልክትሪክ መስመር መቃጠል ጋር በተያያዘ በጥርጣሬ የተያዙ ከ20 በላይ ግለሰቦች ወደ ማይጨው ከተማ ተወስደው መታሰራቸውን የአካባቢው ነዋሪዎች ቢናገሩም ፣ ዘመዶቻቸው እንዳይጠይቋቸው በመደረጉ ስለደህንነታቸው ሁኔታ ለማወቅ አልተቻለም።
ወጣቶች የታሰሩት ለኢንቨስተሮች ተብሎ የተዘረጋውን የኤልክትሪክ ምሰሶ አቃጥላችሁዋል በሚል ነው። የአካባቢው ነዋሪዎች ለኢሳት እንደገለጡት ታፍነው የተወሰዱት ወጣቶች በእስር ቤት ጉዳት ሳይደርስባቸው አልቀረም።
በጉዳዩ ዙሪያ የመንግስት ባለስልጣናትን ለማናገር ያደረግነው ጥረት አልተሳካም።
በሌላ በኩል ደግሞ ስራ ለመቀጠር ወደ ጅጅጋ የሄዱ 9 ወጣቶች በፖሊስ ተዘርፈውና ተደብድበው ለልመና መዳረጋቸውን የአካባቢው ወኪላችን ገልጿል። ከባህርዳር ዩኒቨርስቲ የተመረቁት 9ኙ ወጣቶች የተነሱት ሞጣ እየተባለች ከምትጠራ በምስራቅ ጎጃም ዞን በምትገኝ ከተማ ሲሆን፣ ወደ ጂጂጋ ያቀኑትም ለመምህርነት ስራ ተወዳድረው በማሸነፋቸው ነው። መምህራኑ ወደ ምድብ ቦታቸው እስከሚሄዱ  ድረስ አልጋ ተከራይተው በመጠባባቅ ላይ ሳሉ፣ ሌሊት ፖሊሶች ወደ ክፍላቸው በመግባት ከ1600 እስከ 2000 ብር እንዲሁም የሞባይል ስልኮቻቸውን በድብደባ ቀምተዋቸዋል። ፖሊሶቹ ገንዘብ አልተወሰደብንም ብላችሁ ፈርሙ በማለት ካስፈረሙዋቸው በሁዋላ የመሳፈሪያ 50 ብር በመስጠት ሀረር ወስደው ጥለዋቸዋል። መምህራኑ ወደ አካባቢያቸው የሚመለሱበት የትራንስፖርት ገንዘብ ስላጠራቸው በአሁኑ ሰአት ሀረር ከተማ ውስጥ በልመና ላይ መሆናቸውን ወኪላችን ገልጿል።
ኢሳት በቅርቡ ክልሉን የጎበኘ አንድ ሰራተኛን አነጋግሮ፣ በክልሉ ውስጥ በሚኖሩ የሌላ አካባቢ ተወላጆች ላይ ልዩ ሚሊሺያዎች የሚፈጽሙትን በደል ማጋለጡ ይታወሳል።
ይህ በእንዲህ እንዳለ በከተማዋ የሚኖሩ የሶማሊ ተወላጅ ያልሆኑ ነዋሪዎች፣ ሶማልኛ ካልተናገራችሁ መታወቂያ አይታደስላችሁም በመባላቸው ችግር ውስጥ መግባታቸውን ገልጸዋል።
ነዋሪዎች እንደሚሉት የችግሩ ምንጭ ከዋናዋ ሶማሊያ የመጡ ግለሰቦች በስልጣን ላይ መውጣታቸው ነው። አብዛኛው የሶማሊተወላጅ እንደሌላው ተወላጅ ሁሉ በእኩል ስቃይ ይደርስባቸዋል።

በአድዋ ከተማ አደባባይ ላይ ተሰቅሎ የነበረ የ አቶ መለስ ፎቶ ተቀዳዶ ተጣለ-የራስ አሉላ አባ ነጋ ት/ቤት ስያሜ በአቶ መለስ ስም ተቀየረ


ህዳር ፲፰ (አስራ ስምንት) ቀን ፳፻፭  ዓ/ም
ኢሳት ዜና:-በትግራይ ክልል  በአድዋ ከተማ አደባባይ ላይ ተሰቅሎ የነበረ የአቶ መለስ  ዜናዊ ፖስተር ተቀዳዶ ተጣለ
ኢየሩሳሌም አርአያ ምንጮቹን ጠቅሶ እንደዘገበው በሁኔታው የተበሳጩት የክልሉ ካድሬዎች ለተፈጸመው ድርጊት ጣታቸውን ወደ አረና ለትግራይ ፓርቲ ቀስረዋል።
የህወሀት ካድሬዎቹ፦« የመድረክ ተለጣፊ የሆነው አረና ፓርቲ ነው ይህን የፈፀመው » በማለት ያልተጨበጠ የፈጠራ ወሬ እያሰራጩና በድርጅቱ ላይ  እየዛቱ ነው።
የዜናው ምንጮች  ግን ፦”ድርጊቱን የፈፀመው የአካባቢው ህዝብ እንጂ የትኛውም ተቃዋሚ ፓርቲ አይደለም”ሲሉ  ተናግረዋል።
አድዋ የ አቶ መለስ ዜናዊ የትውልድ ከተማ መሆኑ ይታወቃል።
ይህ በ እንዲህ እንዳለ በትግራይ ተምቤን – አብዪአዲ  ውስጥ የሚገኘውና በጀግናው ራስ አሉላ አባነጋ ስም ተሰይሞ የቆየው የሁለተኛ ደረጃ ት/ቤት ስሙ ተቀይሮ በመለስ ዜናዊ ስም እንዲሰየም መወሰኑን  ምንጮቹ አክለው ገልጸዋል።
በደርግ ዘመን የተሰራውና በራስ አሉላ ስም ተሰይሞ  የ9ኛ እና የ 10ኛ ክፍል ተማሪዎችን ተቀብሎ ሲያስተምር የቆየው ይኸው ትምህርት ቤት፤ ከ2002 ዓ.ም ጀምሮ በአገር ውስጥና በውጭ አገራት የሚገኙ የአካባቢው ተወላጆች ባዋጡት ገንዘብ   እስከ 12ኛ ክፍል ተማሪዎችን ማስተናገድ እንዲችል የማስፋፊያና  አቅም የማሳደግ  ሥራ  ተከናውኖለታል።
የትምህርት ቤቱ የማስፋፊያ ግንባታ ተጠናቆ ባለፈው ነሃሴ ወር ሊመረቅ በዝግጅት ላይ እንዳለ አቶ መለስ በማለፋቸው ፕሮግራሙ መሰረዙ የታወቀ ሲሆን፤ የክልሉ ከፍተኛ ባለስልጣናት በስፍራው በተገኙበት  ከሁለት ሳምንት በፊት ተመርቋል።
በምረቃው ሥነ-ስርዓት ላይ  የራስ አሉላ ስም ተሰርዞ « መለስ ሁለተኛ ደረጃ ት/ቤት » ተብሎ መሰየሙን ባለስልጣናቱ በይፋ ተናግረዋል።
በት/ቤቱ በይፋ የመለስ ስም ተፅፎ መለጠፉ  የገለጹት የዜናው ምንጮች፤ በህዝብ ገንዘብ መዋጮ የተገነባን ት/ቤት  ስያሜ መለወጥ፤ በጡንቻና በማን አለብኝነት ህዝብን የመናቅ  ተግባር ነው ሲሉ የአካባቢው ተወላጆች ማውገዛቸውን ተናግረዋል።
በተለይ በአውስትራሊያ፣ በጀርመን፣ በኖርዌይ፣ በአሜሪካ፣ በካናዳና… ሌሎች አገራት የሚኖሩ የአካባቢው ተወላጆች ባካሄዱት ቴሌ ኮንፈረንስ ከፍተኛ ተቃውሞ አሰምተዋል።
ተሳታፊዎቹ ፦ « የአፄ ምንሊክንና የሰማዕቱ አቡነ ጴጥሮስን ሃውልት ለማፍረስ የተጀመረው አፍራሽ እንቅስቃሴ ወደ ራስ አሉላ ተሻግሯል። ይህ የሚያመለክተው  ሰዎቹ የቆየውን የኢትዮጵያን ታሪክ ለማጥፋት ቆርጠው መነሳታቸውን ነው። ይህ ትውልድ ታሪኩን አስጠብቆ የማቆየት፤ የተጀመረውን አደገኛ አፍራሽ እንቅስቃሴ ከማውገዝ ባለፈ ለትግል መነሳሳት አለበት።ኢትዮጵያዊያን እጅ ለእጅ መያያዝ አለብን፤» ነው ያሉት።
አንድ የውይይቱ ተሳታፊ፦« የኢትዮጵያዊነት ጉልህ መታወቂያና መገለጫ የሆኑ አኩሪ ታሪኰችንና ታሪክ ሰሪ ጀግኖችን ለማጥፋት  ቴዎድሮስ ሃጎስ፡ በረከት ስሞዖንና ስብሃት ነጋ የሚመሩት አካል በአገራችን ላይ የጥፋት ዘመቻ ከፍተዋል» ሲሉ ተናግረዋል።
ቀደም ሲል  « የዶጋሊ ዘመቻ » እየተባለ በየአመቱ ራስ አሉላ የሚዘከሩበት ታሪካዊ ቀን እንደነበረ እና ሕወሓት ወደ ስልጣን ከመጣ በሑዋላ ግን ይህ በዓል  እንዲቀር መደረጉን እነዚሁ ወገኖች ያስታውሳሉ።
በሌላም በኩል በመቀሌ ከተማ ፒያሳ አካባቢ የአፄ ዮሃንስን መታሰቢያ ሃውልት ለማቆም ተጀምሮ የነበረው እንቀስቃሴ እንዲቆም መደረጉን የቅርብ ምንጮች አጋልጠዋል።  ሐውልቱ እንዳይሠራ የተወሰነው ባለፈው አመት ከህዝብ በተዋጣ ገንዘብ ሓውልቱን ለማቆም የመሰረት ድንጋይ ከተጣለ በሁዋላ እንደሆነ ተገልጿል።

የአውሮፓ ገበሬዎች ወተት በአውሮፓ ህበረት ህንጻዎች ላይ በመርጨት ተቃውሞአቸውን ገለጹ


ህዳር ፲፰ (አስራ ስምንት) ቀን ፳፻፭ ዓ/ም
ኢሳት ዜና:-ገበሬዎቹ ተቃውሞአቸውን የገለጹት የወተት ዋጋ በመውደቁ ነው። በሺዎች የሚቆጠሩ ገበሬዎች ፣ በርካታ ትራክተሮችን በማሰለፍ የቤልጂም ዋና ከተማ በሆነችው ብራሰልስ ተመዋል።
የወተት ዋጋ 25 በመቶ እንዲጨምር የጠየቁት ገበሬዎቹ የአውሮፓ ህብረት ህንጻዎችን በወተት በመርጨት ነጭ አድረገዋቸዋል።
የአውሮፓ ገበሬዎች ገበያው ሊሸከመው ከሚችለው በላይ የወተት ምርት የሚያመርቱ በመሆኑ ህብረቱ በየአመቱ ከ47 ቢሊዮን ዩሮ በላይ በማውጣት ለመደጎም ተገዷል።

Monday, November 26, 2012

ከሀላፊነታቸው ተነስተው የነበሩት ጄነራል ሞላ ተመለሱ


ህዳር ፲፯ (አስራ አምት) ቀን ፳፻፬ ዓ/ም
ኢሳት ዜና:- በኢትዮጵያ መከላከያ ሰራዊት ውስጥ ብወዛ ለማድረግ ከላይ የተጀመረው እንቅስቃሴ ሳንካ እንደገጠመው የመከላከያ ምንጮች ገለጡ።
በሜጀር ጀኔራል ማህሪ ዘውዴ እንዲተኩ የተወሰነባቸው የአየር ሀይል አዛዥ ሜጀር ጄነራል ሞላ ሀይለ ማሪያም ተመልሰው ስፍራቸውን መያዛቸውን የአየር ሀይል ምንጮች ገለጸዋል።
የቀድሞው ጠቅላይ ሚኒስትር መለስ ዜናዊ ከዚህ አለም በሞት መለየታቸው ለህዝብ ከመገለጹ በፊት በመከላከያ ሰራዊት ውስጥ ሲካሄድ የቆየውን ግምገማ ተከትሎ የአመራር ሽግሽግ ለማድረግ የተጀመረው ሙከራ ከመነሻው ሳንካ ገጥሞታል።
የአየር ሀይል አዛዥ ሜጀር ጄነራል ሞላ ሀይለማሪያም በሜጀር ጄነራል መሀሪ ዘውዴ እንዲተኩ ከተወሰነ በሆላ በህውሀት ውስጥ በተፈጠረ መሳሳብ ሂደቱ መቀልበሱ ተሰምቶል።እንዲነሱ ተወስኖባቸው የነበረው ሜጀር ጄነራል ሞላ ሀይለማሪያምም ሆኑ ሜጀር ጀነራል መሀሪ ዘውዴ ሁለቱም የህውሀት ታጋዮች እንደነበሩም ለማወቅ ተችሎል።
በስራቱ ውስጥ ወጥ የሆነ አመራር አለመኖሩና ተሰሚ የሆነ ግለሰብ ነጥሮ አለመውጣቱ እንዲሁም በህውሀት ውስጥ የአውራጃ ስሜት እየጎላ መምጣቱ ለችግሩ በምክንያትነት እየተጠቀሰ ይገኛል።

ፍኖተ ነጻነት ጋዜጣን ማተሚያ ቤቶች ሁሉ አናትምም አሉ


ህዳር ፲፯ (አስራ አምት) ቀን ፳፻፬ ዓ/ም
ኢሳት ዜና:- የአንድነት ለዲሞክራሲና የፍትህ ፓርቲ ልሳን የሆነችው ፍኖተ ነጻነት ጋዜጣ በየትኛውም ማተሚያ ቤት እንዳይታተም መደረጉ ተገለጸ ፤ ጋዜጣዋን ሲያትሙ የነበሩ የግል ማተሚያ ቤት ባለቤቶች ላይ ማስፈራራትና ዛቻም ተፈጽሞል።
የአንድነት ፓርቲ ምክትል የህዝብ ግንኙነት ሀላፊ አቶ ዳነኤል ተፈራ ከኢሳት ሬዲዮ ጋር ባደረጉት ቃለምልልስ እንደገለጹት የፍኖተ ነጻናት ጋዜጣ ጉዳይ የፖለቲካ ጉዳይ ሆኖል፤ ጠቅላይ ሚኒስትሩ በፓርላማ ቀርበው 34 ማተሚያ ቤት አለ በነሱ ማሳተም ይችላሉ ቢሉም ካድሬዎቻቸውና ደህንነታቸው በየማተሚያ ቤቱ በመዞር ማስፈራራትና ዛቻ በመፈጸም ጋዜጣዋ በየትኛውም ማተሚያ ቤት እንዳትታተም አድርገዋል ብለዋል።
ይህንን የረቀቀ አፈና ለመታገልና ለመስበር ፓርቲያቸው የተለያዩ ዘዴዎችን ለመቀየስ ተገዶል ያሉት አቶ ዳነኤል ለጠቅላይ ሚኒስትር ፣ ለብሮድ ካስት ኤጀንሲና ለኮምንኬሽን ጽ/ቤት ደብዳቤም ቢጽፉም መልስ የሚሰጣቸው እንዳላገኙ ተናግረዋል።
የግል ማተሚያ ቤቶችን አዳርሰናል መጀመሪያ እሺ ብለው ከተስማሙ በሆላ ፍኖተ ነጻነት መሆኖን ሲያውቁ አሻፈረን ይላሉ ያሉት የህዝብ ግንኙነቱ በተለይ አንዱ ማተሚያ ቤት የመጀመሪያ ዙር አትሞ ካወጣ በሆላ ሁለተኛው እትም ሳያልቅ አላትምም ማለቱን ተናግረዋል።
እነዚህ የማተሚያ ቤት ባለቤቶችም በመንግስት ሰዎች ማስፈራሪያና ዛቻ እንደደረሰባቸው በስጋት እንደነገሮቸው አጋልጠዋል አቶ ዳነኤል።
ስለዚህም ጋዜጣችው ከሀገሪቱ የህትመት ስራት ውስጥ እንድትወጣ ተደርጎል፤ ግን ደግሞ ማተሚያ መሳሪያ በመግዛት ጭምር እስከ መጨረሻው ይህንን የረቀቀ የአፈና ድርጊት እንደሚታገሉት አስታውቀዋል።

አሜሪካዊ የአኟዋክ ተወላጆች በቦሌ ለ 48 ሰአት ታሰሩ


ህዳር ፲፯ (አስራ አምት) ቀን ፳፻፬ ዓ/ም
ኢሳት ዜና:-የኢትዮጵያ መንግስት ሁለት ኢትዮጵያዊ የአሜሪካ ዜጎችን ለ 48 ሰአታት ማሰሩ ተሰማ። በኢትዮጵያ የአሜሪካ ኤምባሲ ከመንግስት ሰዎች ጋር ተሞግቶ እንዳስፈታቸውና ከቦሌ በቀጥታ ወደ አሜሪካ እንደላካቸው ተገልጿል።
የአኟዋክ ብሄር ተወላጅ የሆኑትን አሜርካዊያንን ከቦሌ አውሮፕላን ማረፊያ ይዞ ያሰረው የኢትዮጵያ መንግስት ግለሰቦቹ መንግስታዊ ያልሆነ ድርጅት ለመመስረት ወደ ጋምቤላ መጓዛቸውን ቢገልጹም የለም የፖለቲካ አጀንዳ አላችሁ፤ ታጣቂዎችን ትደግፋላችሁ በማለት መሆኑን የኢሳት ምንጮች ገልጸዋል።
ለድርጅት ምስረታ ወደ ኢትዮጵያ ተጉዘው የነበሩት ሁለቱ የአኙዋክ ተወላጆች አሜሪካዊያን ለዚህ ፕሮጀክት ወደ ጋምቤላ በተጓዙበት ጊዜ ስራቸው ላይ የክልሉ ሀላፊዎች ችግር በመፍጠራቸው ርዕሰ መስተዳድሩ ጋር ቀርበው በክልሉ ስላለው የአሰራር ብሉሹነትና ሙስና መናገራቸውን ለማወቅ ተችሏል።
ምንጮቻችን እንደገለጹት ምናልባትም በቦሌ እንዲያዙ ምክንያት የሆነው የክልሉ መስተዳድር ለፌደራል ባለስልጣናት ግለሰቦቹ አስተዳደራቸውን መተቸታቸውን በመናገራቸው ሊሆን ይችላል ብለዋል።
አሜሪካዊ ዜግነት ያላቸው ሁለቱ የአኝዋክ ተወላጆች ል 48 ሰአታት ከታሰሩ በሆላ የአሜሪካ ኤምባሲ ዜጎቼ ይፈቱ ብሎ በመጠየቁ መፈታታቸውንና ከዛው ከአውሮፕላን ማረፊያ ወደ አሜሪካ መላካቸውን ለማወቅ ተችሏል።

በመቀሌ ዩኒቨርሲቲ ሙስና ተስፋፍቷል


ህዳር ፲፯ (አስራ አምት) ቀን ፳፻፬ ዓ/ም
ኢሳት ዜና:-በጀርመናዊ ፕሬዚዳንት የሚመራው የመቀሌ ዩኒቨርሲቲ በሁለት ምክትል ፕሬዚዳንቶች ብቻ ከ 300 ሚሊዮን ብር በላይ መባከኑ ተገለጠ።
ሁለቱን ምክትል ፕሬዚዳንቶች ይነሱልኝ ሲሉ ለትምህርት ሚስቴር ሳይቀር ደብዳቤ የጻፉት ጀርመናዊ ፕሬዚዳንት ማስፈራሪያና ዛቻ ደርሶባቸዋል ተብሎል።
ከኢትዮ ሚዲያ ያገኘነው መረጃ እንዳመለከተው በ300 ሚሊዮን ብር ሙስና የተጠረጠሩትን የዩኒቨርሲቲው ምክትል ፕሬዚዳንቶች ዶ/ር ክንድያ ገ/ህይወትና ዶ/ር አብድርቃድር ከድር ናችው።
አቶ መለስ በህይወት በነበሩ ጊዜ ግንኙነታቸው ቀጥታ ከሳቸው ጋር ነበር የሚባሉት ጀርመናዊ ፕሬዚዳንት በዩኒቨርሲቲው ከፍተኛ ገንዘብ እየባከነ መሆኑን ገልጸው ለሚመለከተው የመንግስት አካል ደብዳቤ በመጻፋቸውና ለት/ሚኒስቴርም ግልባች በመላካቸው በቦርድ ሰብሳቢው በአቶ ቲዎድሮስ ሀጎስ ሳይቀር ማስፈራራት እንደተደረገባቸው ኢትዮ ሚዲያ ዘግቧል።

የህዳሴው ግድብን ግብጽና ሱዳን ሊመሩት ይገባል ተባለ


ህዳር ፲፯ (አስራ አምት) ቀን ፳፻፬ ዓ/ም
ኢሳት ዜና:-ኢትዮጵያ በመገንባት ላይ የምትገኘው የህዳሴ ግድብ የአባይ ተፋሰስ ሀገሮችን የአባይ ውሀ ድርሻ በጽኑ የሚጎዳ በመሆኑ የጋራ ስምምነት ላይ ሊደርስ ይገባል ሲሉ አንድ የፖለቲካ ምሁር ገለጹ።
ግድቡ ሲጠናቀቅ ኢትዮጵያ የአባይን ወንዝ ውሀ 86 በመቶ በመቆጣጠር በአባይ ላይ የበላይነቱን ትይዛለችና፤ በተለይ ግብጽና ሱዳን ከወዲሁ መፍትሄ ሊያበጁ ይገባል ብለዋል።
ኢትዮጵያ በበኩሏ ከህዳሴው ግድብ ግብጽና ሱዳን ይጠቀማሉ እንጂ የሚጎዳ ወገን የለም ስትል መከራከሯን ቀጥላለች ብሎል በሱዳን የሚታተመው ሱዳን ቪዥን ጋዜጣ።
በአለም አቀፉ የአፍሪካ ዩኒቨርሲቲ የኢትዮጵያ የህዳሴው ግድብ በግብጽና በሱዳን ላይ ያለው ተጽኖ በሚል ረስ በተካሄደ ፎረም የተሳተፉት የፖለቲካ ምሁር ፕሮፌሰር ሀሰን አልፍሬ የህዳሴው ግድብ ፍትሀዊ የሚሆነው ግብጽና ሱዳን ተረክበው ስራውን ሲያከናውኑትና ግድቡን ሲመሩት ብቻ ነው ብለዋል።
እንደፕሮፌሰሩ ይህ ካልሆነ ኢትዮጵያ ብቻ ግድቡን መገንባት ቀጥላ ካጠናቀቀች በሆላ የአባይን ካርድ በግሏ ታስገባለች፤ 86 ከመቶ የአባይን ውሀ በመቆጣጠር። ይህ ደግሞ የሁለቱን ሀገሮች የአባይ ድርሻ በጽኑ ይጓዳል ሲሉ አስጠንቅቀዋል።
ሌላው ምሁር በዚሁ ጉዳይ ላይ ደቡብ ሱዳንም ሌላ ስጋት እንደምትኋን ገልጸዋል፤ በተለይም የታላቁ አባይ ታላቅ ገባር የነጭ አባይ በርግዛቷ በመኖሩ ሲሉ ተናግረዋል። ስለዚህም የህዳሴው ግድብ የሚመለከታቸውን ያለማከረ አደገኛ ፕሮጀክት ነው ተብሎል።
የእትርሻ፣ የመስኖ ግድብ፣ የአካባቢ ጥበቃ፣ የኤሌክትሪክ ሀይል ባለርሙያዎችና ፖለቲከኞች እንደተሳተፉበት በተገለጸው በዚህ ፎረም የኢትዮጵያ የማእድንና የኢነርጂ ሚንስትር ኢትዮጵያ የግብጽና የሱዳንን ተጠቃሚነት የመገደብ የተደበቀ አጀንዳ የላትም ሲሉ አስተባብለዋል።

በሀገረማርያም በተደረገ ስብሰባ ህዝቡ የመንግስትን የአፈና አገዛዝ ነቀፈ


ህዳር ፲፯ (አስራ አምት) ቀን ፳፻፬ ዓ/ም
ኢሳት ዜና:-በቦረና ዞን በሀገረማሪያም ከተማ ህዳር 14 ቀን 2005 ዓም  ”ከተማዋን ለማልማት” በሚል አጀንዳ  በተጠራ ስብሰባ ላይ ነው ህዝቡ የ21 አመታት የአፈና አገዛዝ በቃን በማለት የተናገረው።
የኢሳት ወኪል እንደዘገበው  የዞን እና የወረዳ ባለስልጣናት ከተለያዩ የህብረተሰብ ክፍሎች የተውጣጡ ከ500 በላይ ሰዎችን ሰብስበው የ2004 ዓም አፈጻጸም ግምገማንና የ2005 ዓም እቅድን  ይፋ አድርገዋል።
ባለስልጣናቱ ለ2005 ዓም ለከተማዋ ግንባታ ከተያዘው በጀት ውስጥ ነዋሪው 50 በመቶ የሚሆነውን ወጪ ይሸፍናል ተብሎ እንደሚጠበቅ መግለጻቸውን ተከትሎ በተሰጠው እድል ነው ህዝቡ ስሜቱን ሲገልጽ የዋለው።
ወኪላችን እንደሚለው  ነዋሪዎች ፣ ”  እንዳንናገር ታፍኑናላችሁ፣  21 አመታት ሙሉ ስታስፈራሩን ቆይታችሁዋል፣ እኛ ተለጉመን ያለን ህዝብ ነን ለምንድነው በማናምንበት ጉዳኢ ላይ አስተያየት እንድንሰጥ የምታስገድዱን።” እያሉ ይናገሩ ነበር።
የመንግስት ባለስልጣናቱ የአፈጻጸም ችግር እንደነበር በመማንና ችግሮችን ለማስተካካል እንደሚሰሩ በመግለጽ ህዝቡን ለማግባባት ሞክረው ነበር። ይሁን እንጅ ህዝቡ ” ለ21 አመታት ምንም የሰራችሁት ነገር የለም ፣ መልካም አስተዳዳር ፣ ዲሞክራሲያዊ አስተዳዳር በሌለበትና ሰብአዊ መብቶች በማይከበሩበት ሁኔታ ምንም ልማት ሊኖር አይችልም። እዚህ ቦታ ላይ ራሳችሁን ትሾማላችሁ፣ ራሳችሁን ታነሳላችሁ፣ ህዝቡ በስልጣኑ ተጠቅሞ የሚያስቀምጠው፣ የሚያወርደው ሰው የለም፣ ስራችሁን አናይም ፣ የምናየው ነገር ቢኖር ህዝቡን ስታስፈራሩ ብቻ ነው” የሚል መልስ ሰጥቷል።
ስብሰባውም በውዝግብ መጠናቀቁ ታውቋል።
በተመሳሳይ ዜና ደግሞ በሀረሪ ክልል የሚገኙ የግብርና ባለሙያዎችን ለመገምገም በተጠራ ስብሰባ ላይ ውዝግብ ተፈጥሮ እንደነበር በስብሰባው ላይ የተሳተፉ ባለሙያዎች ለኢሳት ተናግረዋል።
ከህዳር 6 እስከ 12 አቶ ሀምዛ በሚባሉት የሀረሪ የግብርና ቢሮ ሀላፊ ሰብሳቢነት በተጠራ ስብሰባ ላይ የዲኤ ሰራተኞች፣ የቢሮ አመራሮች፣ ኤክስፐርቶችና የስራ ሂደቶች ተሳትፈዋል፡፡ የግምገማው ርእሶች  ”  የልማት ሰራዊት ግንባታን በሙሉ እምነት ተቀብሎ ከማደራጀትና ከመምራት አንጻር ያለበት ሁኔታ፣ ምርጥ ተሞክሮ መቀመር እና ማስፋፋት ፣ ሶስቱን የልማት ሀይሎች አቀናጅቶ መምራት፣ እንዲሁም የኪራይ ሰብሳቢነት አመለካከትን መታገል”  የሚሉት ነበሩ።
አቶ ሀምዛ አሁን የምንገመግማችሁ ከአመለካት፣ ከክህሎት እና ከግብአት አንጻር ነው” በማለት ካተናገሩ በሁዋላ፣ ” እኔ ክልል ላይ ስገመገም አልሰራሁም ብየ ነው የመጣሁትና እናንተም አልሰራንም ብላችሁ ተናገሩ።” በማለት  ባለሙያዎችን ሲማጸኑ ውለዋል።
ሰራተኞችም ” እኛ የሰራነውንም ያልሰራነውንም እስከ ምክንያቱ  እንገልጻለን።” በማለት አስተያየት ሲሰጡ ባለስልጣኑ በማቋረጥ ”  ያልሰራችሁበትን ምክንያት መስማት አልፈልግም፣ አልሰራሁም ብቻ በሉ” በማለት አስጠንቅቀዋል። ባለስልጣኑ የስብሰባው ዋና አላማ ገበሬውን አንድ ለአምስት ለማደራጀት መሆኑን በማስታወስ ሰራተኞች ትኩረት ሰጥተው ገበሬውን እንዲያደራጁ መመሪያም አስተላልፈዋል።
ሰራተኞች ” የአንድ ለአምስት አደረጃጃት ግቡን አልመታም፣ ገበሬው ለመደራጀት ፍላጎት የለውም፣ ህብረተሰቡ አንድ ለአምስት አደረጃጃት ለፖለቲካ መጠቀሚያ ተብሎ የተዘጋጀ ነው የሚል ትችት በማቅረቡ ሳይፈልጉ ያደራጀናቸው ገበሬዎች አንፈልግም እያሉ ነው።” በማለት ተናግረዋል።
አብዱልመጂድ  የተባለ የተፈጥሮ ሀብትና ሴፍቲኔት ኤክስፐርት ” ያልረሳሁበትን ምክንያት መግለጽ አለብኝ፣ ይህን ካልገለጽኩኝ አልገመገምም” የሚል ጠንካራ አቋም በማንጸባረቁ፣ የቢሮ ሀላፊው ” አርፈህ ማትቀመጥ ከሆነ ከዚህ ትባረራለህ” በማለት እንዳስጠነቀቁት ስብሰባውን የተካፈሉት ባለሙያዎች ገልጸዋል።
አብዱልመጅድ ጥያቄ መጠየቁን ባለማቆሙ፣ የቢሮው ሀላፊው መድረኩ ላይ ከስራ አባረውታል።  ሌሎች አንጋፋ ሰራተኞች ” የሶስት ልጆች አባት ነው” በሚል ባለስልጣኑን ቆመው በመለመን ወደ ስራው እንዲመለስ ማድረጋቸውም ታውቋል።
የግብርና ሰራተኞች በሚደርስባቸው የሰብአዊ መብቶች ጥሰት መማረራቸውንም ገልጸዋል

የቆዳ እንዱስትሪው በጨው እጥረት አደጋ ላይ ነው ተባለ


ህዳር ፲፯ (አስራ አምት) ቀን ፳፻፬ ዓ/ም
ኢሳት ዜና:-በዚህ ዓመት ከኤክስፖርት 200 ሚሊዮን ዶላር እንደሚያስገባ እቅድ የተያዘለት  የቆዳ ኢንደስትሪ በጨው አቅርቦት እና  በተለያዩ ግብዓቶች እጥረት አጣብቂኝ ውስጥ መግባቱን የዘገበው ሪፖርተር ነው
የ ቆዳ ኢንዱስትሪዎች ማህበር በ አምስት ወር 150 ሺህ ኩንታል ቸው ሊደርሰን ሲገባ፤ያገኘነው ግን አምስት ሺህ ኩንታል ብቻ ነው አለ።
የአፋር ክልል በበኩሉ፦-<< ምንም ዓይነት  የ አቅርቦት ችግር አልተፈጠረም> ይላል።
የኢትዮጵያ ቆዳ ኢንዱስትሪዎች ማኅበርና -ግብዓት አቅራቢው የኢትዮጵያ ቆዳ ልማት አክሲዮን ማኅበር  በጋራ እንዳስታወቁት፣ በከፍተኛ የጨው አቅርቦት ችግር ውስጥ የሚገኙት ኢንዱስትሪዎች ጥሬ ቆዳ እየተበላሸባቸው ከመቸገራቸውም በላይ፣ በጥራት ችግር ምክንያት የቆዳ ምርታቸው ተገቢውን ዋጋ ማግኘት ተስኖታል፡፡
የቆዳ ኢንዱስትሪዎች ከመላ አገሪቱ የሚሰበስቡት ቆዳ- በጨው ታሽቶና ደርቆ የሚዘጋጅ ሲሆን፣ ለምርት ሥራም ሆነ ቆዳና ሌጦ ሳይበላሽ ለማቆየት በዓመት እስከ 350 ሺሕ ኩንታል አዮዲን ያልተቀላቀለበት ጨው ያስፈልጋቸዋል፡፡
ይሁንና  ዘንድሮ ኢንደስትሪዎቹ  የሚያስፈልጋቸውን ጨው  ጨርሶ  ለማለት በሚያስደፍር አኳሁዋን  ሊያገኙ አለመቻላቸው ተገልጿል።
ባለፉት አምስት ወራት ከሚያስፈልጋቸው 150 ሺሕ ኩንታል ውስጥ ማግኘት የቻሉት አምስት ሺሕ ብቻ እንደሆነ  ነው  የኢትዮጵያ ቆዳ ኢንዱስትሪዎች ማኅበር ዋና ጸሐፊ አቶ አብዲሳ አዱኛ የተበናገሩት፡፡
በ አፋር ክልል ከአፍዴራ ጨው አምራቾች ድጋፍ ሰጭ ማኅበር  ላለፉት ስድስት ዓመታት የጨው አቅራቢ ሆኖ ይሠራ የነበረው አንድ ግለሰብ ብቻ መሆኑን ጠቀሱት አቶ አብዲሳ፣ በአሁኑ ጊዜ ቁጥራቸው ሦስት እንዲደርስ ቢደረግም የአቅርቦቱ ችግር ተባብሶ እንደቀጠለ ገልጸዋል፡፡
የኢትዮጵያ ቆዳ ልማት አክሲዮን ማኅበር ዋና ሥራ አስኪያጁ አቶ ይሄይስ መርሻ በበኩላቸው፣ የፌደራል መንግሥት -አንዴ በንግድ ሚኒስቴር ሚኒስቴር ሌላ ጊዜ በኢትዮጵያ የምግብ፣ የመድኃኒትና ጤና እንክብካቤ አስተዳደርና ቁጥጥር ባለሥልጣን በኩል፦ ኢንዱስትሪዎቹ የሚያስፈልጋቸው የጨው መጠን በዝርዝር ቢጽፍም፣ የሚፈለገው የጨው መጠን ባለመገኘቱ ብቻ ሳይሆን የሚቀርበውም ጥራት የጎደለው አፈራማ ጨው በመሆኑ፣ በቆዳና በሌጦ ላይ ብክለት እያስከተለ አገሪቱ ማግኘት የሚገባትን የውጭ ምንዛሪ እያሳጣት ይገኛል ብለዋል፡፡
አቶ ይሄይስ ፤የጨው ምርቱ በገፍ እያለ ሆን ተብሎና ሞኖፖልን በመጠቀም የጨው እጥረቱ በቆዳ ኢንዱስትሪዎቹ ላይ እንዲከሰት ተደርጓል ባይ ናቸው።  በዚህም ሳበያ አገሪቱ ከዚህ ቀደም የነበራት 30 በመቶ ጥራት ያለው ጥሩ ቆዳ- በአሁኑ ጊዜ ወደ 10 በመቶ መውረዱን ተናግረዋል፡፡
ከአፋር ክልል የሚመጣውን ጨው በዛ ከተባለ በኩንታል እስከ 160 ብር ፋብሪካዎቹ ለመግዛት ዝግጁ ቢሆኑም፣ የሚጠየቁት ዋጋ እስከ 300 ብር ማሻቀቡን ተናገሩት አቶ ይሄይስ፤ አዮዲን እንተቀላቀለበት ጨው እኩል ዋጋ መጠየቁ- የቆዳና ሌጦ ማምረቻ ወጪን እንደሚያንረው አብራርተዋል።
ለጨው ፍጆታ ብቻ እስከ 12 ሚሊዮን ብር በማውጣት ለማምረት መገደድ በውጭ ገበያ ተፎካካሪ እንደማያደርግ ም ገልጸዋል።
እንደ አቶ ይሄይስ ገላፃ እንደ ህንድ፣ ፓኪስታንና የመን የመሳሰሉ አገሮች ለአንድ ኩንታል ጨው በአማካይ ሦስት ዶላር ሲያወጡጸ የኢትዮጵያ ቆዳ ፋብሪካዎች ወጪ  እስከ ስምንት ዶላር ይደርሳል።
ይህ የሆነውም ዋጋው የናረው ጨው በመኖሩ ሳይሆን አቅርቦቱ በኮታ እንዲሆን በመደረጉ ነው ይላሉ  ሥራ አስኪያጁ።
ስለ ጉዳዩ የተጠየቁት የአፋር ክልል ፕሬዚዳንት አቶ ኢስማኤል አሊሴሮ፣ የጨው አቅርቦት እጥረት የለም  በማለት ኢንዱስትሪዎቹ  ያቀረቡትን ጥያቄ ውድቅ አድርገዋል፡፡
በየቀኑም ከሚጫነው 30 መኪና ጨው በተጨማሪ በወር 360 ኩንታል እንደሚሰራጭ የጠቀሱት ፕሬዚዳንቱ፣ <<የአቅርቦት ችግር ፈጽሞ ሊኖር አይችልም >>በማለት አስተባብለዋል፡፡
አቶ እስማኤል እንዳሉት ከክልሉ ጋር እየሰሩ ያሉት አቅራቢዎች በኩንታል 80 ብር እየተቀበሉ ነው የሚያከፋፍሉት።  የቆዳ አክስዮን ማህበር ሥራ አስኪያጅ አቶ ይሄይስ እንደሚሉት ደግሞ  ፋብሪካዎች በኩንታል  160 ብር ለመግዛት ዝግጁ ቢሆኑም ዋጋው ወደ 300 ብር አሻቅቧል።
በኩንታል  80 ብር የተረከቡትን ጨው- በ300 ብር የሚያከፋፍኩት እነማን ናቸው? የሚለው በተብራራ መልክ አልተቀመጠም።
<<ችግሮች ካሉ ወደ እኛ መጥተው እንነጋገር >>ያሉት አቶ ኢስማኤል፣ በጨው አቅርቦቱ መሀል እየገቡ ሊያስቸግሩ የሚችሉ አካላት ሊኖሩ እንደሚችሉም ግን  ሳይጠቁሙ አላለፉም፡፡
ይሁንና በአቅርቡቱ መሀል ጣልቃ እየገቡ ችግር እየፈጠሩ ናቸው ያሏቸው አካላት እነማን እንደሆኑ ፕሬዚዳንቱ በግልጽ አልተናገሩም።