FREE ALL POLITICAL PRISONERS

FREE ALL POLITICAL PRISONERS
FREE ALL POLITICAL PRISONERS

Tuesday, March 26, 2013

ከእሁድ እስከ እሁድ


(የሳምንቱ አጫጭር ዜናዎች)
bottle


አንድ ላስቲክ ውሃ 10 ብር!!
በአፋር የቡሬ ነዋሪዎች ለከፍተኛ የውሃ ችግር መዳረጋቸውን ውሃ የሚሸጥበትን ላስቲክ በፎቶ በማያያዝ የጎልጉል የአይን ምስክር ከስፍራው አስታውቋል። በክልሉ የጎልጉል ተከታታይ የሆኑ እንደገለጹት በመጠጥ ውሃ ችግር እየደረሰ ያለው ችግር ከፍተኛና ህይወትን የሚፈታተን ነው። አካባቢው የጦር ቀጠና ከመሆኑ አንጻርና የንጹህ መጠጥ ውሃ ችግር አሳሳቢ እንደሆነ ያስታወቀው የአይን ምስክር “እባካችሁ የሚሰማ ካለ ንገሩልን” ሲል ጥሪ አስተላልፏል።
የውሃ ችግር ጊዜ የሚሰጥ ባለመሆኑ አንድ ላስቲክ ውሃ 10 ብር ለመግዛት መገዳዳቸውን፣ በዚህም ቢሆን እንደ ልብ ማግኘት እንደማይቻል አመልክቷል። በስፍራው ያለውን የውሃ ችግር አስመልክቶ ሎጊያ የሚገኝ ጎልጉል የአይን ሪፖርተር አስተያየቱን እንዲሰጠን ጠይቀነው የበኩሉን ማጣራት ካደረገ በኋላ ችግሩ መኖሩን አረጋግጦልናል። ቡሬ አካባቢ ያለው ውሃ ችግር በዋናነት የሚጠቀስ ቢሆንም በተመሳሳይ የሚቸገሩና በድርቅ የተመቱ ቦታዎች እንዳሉ አመልክቷል። አንዳንድ የወታደር ተሽከርካሪዎች ውሃ እንደሚሸጡ መረጃ ማግኘቱንም ገልጿል።
“የልማት ሰራዊት” ያልተገነባበት ምክንያት ይገምገም ተባለ
ባህር ዳር ከተማ የአራት ቀን ጉባኤ ለማካሄድ የከተመው ኢህአዴግ በበቂ ሁኔታ የልማት ሰራዊት አለመገንባቱን፣ ከፍተኛ የሚባል የገንዘብ ችግር እንዳጋጠመው፣ ኢንዱስትሪው ግብርናውን ተረክቦ ያገሪቱን ኢኮኖሚ እንዲመራው የተያዘው እቅድ የተፋዘዘ መሆኑንና የግሉ ዘርፍ በሚገባ አለመንቀሳቀሱን በመግለጸ ጉባኤው ችግሮችን መርምሮ መፍትሄ እንዲፈልግ ተጠየቀ፡፡
የ2004 የግብርና ምርት አድገት ከተያዘለት መሰረታዊ የእድገት መጠን አማራጭ “አንሶ ማደጉን”፣ ለዚህም ምክንያቱ የልማት ሰራዊት ባግባቡ መፈጠር ባለመቻሉ ነው። በተፈጥሮ ጥበቃ የተሻለ የልማት ሰራዊት መገንባት ቢቻልም በሰብል ልማት ዘርፍ ግን ምቹ ሁኔታ ከመፍጠር ያለፈ ስራ እንዳልተከናወነ ተጠቆመ። “ጓድ” ሃይለማርያም ደሳለኝ ዘጠነኛው የኢህአዴግ ጉባኤ የልማት ሰራዊት መገንባት ያልተቻለበትን ምክንያት ፈትሾ፣ የድርጅቱንና የህዝቡን የማስፈፀም አቅም በመገንባት ዘርፉን ወደፊት ለማሸጋገር የሚያስችል አቅጣጫ የማስቀመጥ ሀላፊነት እንዳለበት አመልክተዋል።
የፋና ብሮድ ካስቲንግን ጨምሮ የተለያዩ የኢህአዴግ መገናኛዎች እንዳሉት “ጓድ” ሀይለማርያም በንግግራቸው በአገሪቱ ከቅርብ ጊዜ ወዲህ “የአክራሪነት አስተሳሰቦች” ብቅ ማለታቸውን አንስተዋል። እነዚህ የአክራሪነት አስተሳሰቦች ከመሰረታዊ የአገሪቱ ህገ መንግስት መርህዎች ጋር የሚጋጩ ናቸው ብለዋል። የህዝቡን ዲሞክራሲያዊ አንድነትና እኩልነት፣ የመንግስትን ከሀይማኖት ነፃ ሆኖ ሁሉንም በእኩልነት የማገልገል ሀላፊነቱን የሚፃረሩ በመሆናቸው ሁሉም ሊታገላቸው እንደሚገባም ጠቁመዋል። በሃይማኖት ቤቶችና ደጆች አስተዳደራቸው ውስጥ ሙሉ በሙሉ የሚዋኘውን መንግሥታቸውን አቶ ሃይለማርያም በንግግራቸው “አሁንም መንግስት በሃይማኖት ጣልቃ አይገባም” ሲሉ ገልጸውታል።
አንደበት
“……አቶ መለስ ህወሓትን ከፊት አድርገው አዲስ አበባ ሲገቡ እውነተኛ ብሔራዊ እርቅ አድርገው ቢሆን ኖሮ ዛሬ ተገፍተን በስደት ያለን ሁላችን በየሙያችን አገራችንና ወገኖቻችንን እናግዝ ነበር። የሆነው ግን የተለየ ነው። መለስ “እነሱ” ብሎ ሌሎችን በመወንጀል ጥላቻን ማወጅ ጀመረ። ትውልድን የሚያንጽ ብሄራዊ ሚዲያ ሳይቀር የጥላቻና የቂም ስብከት እንዲያስተጋባ ተደረገ። የዚህ መዘዝ ዛሬ ላይ ጣለን። የጋራ ንቅናቄያችን “እነሱ” የሚል ቋንቋ የለውም። ስንጀምር “እኛ” ብለን ነው። ይህ ልዩ ያደርገናል። የሰው ልጆች ጥላቻን ለመሸከም አይመጥኑም። ጥላቻ የሚዘራብን እንደሰው ስለማንታይ ነው። እንደ ሰው ስላልተከበርን ነው። ሰው መልካም ነገር እንዲያደርግ ከፈጣሪ የተሰጠው ልዩ ስጦታ አለው፡፡ መለስ ግን ይህንን ረስቷል። በብሄር ብሄረሰብ ስም ሲምል ሁላችንንም ሳያሳፍር ነው። ብቻውን ወይም ጥቂት ሰዎች ይዞ ወደ ጥፋት ሄደ፤….”
የአዲሲቷ ኢትዮጵያ የጋራ ንቅናቄ ዋና ዳይሬክተር  አቶ ኦባንግ ሜቶNovember 16, 2012 ለጎልጉል ከሰጡት ቃለ መጠይቅ የተወሰደ
“በአፋር የከብት መኖ ለምግብነት እየዋለ ነው”
በአፋር ክልል ካለፉት አራት ወራት ጀምሮ የተከሰተው ከፍተኛ ረሀብና የውሀ እጥረት የበርካታ ህጻናትን ህይወት መቅጠፉን ነዋሪዎች እንደገለጹለት ጠቅሶ ኢሳት ዘገበ። ምንም እንኳ 60 በመቶ በሚሆነው የአፋር አካባቢ ከፍተኛ የሆነ የምግብና የውሀ እጥረት ቢከሰተም፣ ችግሩ ከሁሉም ወረዳዎች አስከፊ በሆነበት የእዳ ወረዳ 6 ህጻናት በአንድ ወር ውስጥ ሞተዋል። ይህ አሀዝ በአንድ ሰፈር ብቻ የተጠናከረ እንጂ በአጠቃላይ በወረዳው በተከሰተው ረሀብና የውሀ እጥረት የሟቾች ቁጥር በብዙ መቶዎች ሊደርስ እንደሚችል ኢሳት ነዋሪዎችን ጠቅሶ አመልክቷል።
አንድ ጀሪካን ውሀ በ60 ብር ለመግዛት መገደዳቸውን ስማቸው እንዳይጠቀስ የፈለጉ የእዳ ወረዳ ነዋሪ መናገራቸውን የገለጸው ኢሳት፣ የአካባቢው ነዋሪ ፍየሎቹና ግመሎቹ አልቀውበት ወደ አሳይታ ስደት መጀመራቸውን፣ አሳይታ በሰላም የደረሱት በህይወት ሲትረፉ ሌሎች ደግሞ በመንገድ ላይ ማለቃቸውን አትቷል።
የመንግስት እርዳታ እንዳልመጣላቸው የተናገሩት ነዋሪዎቹ ፣ አስቸኳይ እርዳታ ካልደረሰ አስከፊ እልቂት እንደሚከሰት መናገራቸውን ኢሳት አውስቷል። በአካባቢው የትጥቅ ትግል በማድረግ ላይ የሚገኘው የአፋር ጋድሌ (የአፋር ተቃዋሚ ድርጅት) ሊ/መንበር ኮሎኔል ሙሀመድ አህመድ ከፍተኛ ረሀብ በአካባቢው መግባቱን ድርጅታቸው እንደሚያውቅ ለኢሳት ማረጋገጫ ሰጥተዋል።
ይህ በእንዲህ እንዳለ እሁድ ኢሣት ፍኖተ ነጻነትን ጠቅሶ ባሰራጨው ተመሳሳይ ዜና በአፋር ረሃብ ጠንቶ የሰዎችን ህይወት ማጥፋቱን አስታውቋል፡፡ የተረፉትም በዕርዳታ የመጣ የከብት መኖ እየጋገሩ ለመመገብ መገደዳቸውን አመልክቷል፡፡
ሚድሮክ ከ632 ሚሊዮን ብር የግብር ዕዳ አለበት
ሚድሮክ ኢትዮጵያ ኃላፊነቱ የተወሰነ የግል ማኅበር ከንግድ ትርፍ ግብርና ከተጨማሪ እሴት ታክስ ከ632 ሚሊዮን ብር በላይ ዕዳ በመንግሥት እንደሚፈለግበት ሪፖርተር ምንጮቹን ጠቅሶ ዘግቧል። በዜናው መሰረት የኢትዮጵያ ገቢዎችና ጉምሩክ ባለሥልጣን የከፍተኛ ግብር ከፋዮች ቅርንጫፍ ጽሕፈት ቤት በቅርቡ ለሚድሮክ ኢትዮጵያ በላካቸው ሦስት የትርፍ ግብር ውሳኔ ማስታወቂያዎች የተጠቀሰው ገንዘብ እንዲከፈል ጠይቋል፡፡
ደብዳቤው አዋጅ ጠቅሶ ከማንኛውም ንግድ ትርፍ፣ ከተጨማሪ እሴት፣ ከተጨማሪ ግብር በመቶኛ በማስላት የተጠየቀውን ገንዘብ በ30 ቀናት ውስጥ ገቢ እንዲያደርግ መጠየቁን ያስረዳው የሪፖርተር ዘገባ ሚድሮክ ግዳጁን ካልተወጣ በህግ እንደሚጠየቅ እንደተገለጸለት ያስረዳል። በሌላም በኩል ቅሬታ ካለ አቤት ማለት እንደሚችሉ በደብዳቤው ላይ መጠቀሱን ለሪፖርተር የነገሩት የሚድሮክ ምንጮቹ ናቸው።

አልጀዚራ ከታነቀ በኋላ ጠንካራ ሪፖርት አቀረበ
የአልጀዚራ የቴሌቪዥን ስርጭት ሙሉ በሙሉ ኢትዮጵያ ውስጥ እንዳይተላለፍ መደረጉን አልጀዚራ ድርጊቱን በመቃወም ያስታወቀው በሳለፍነው ሳምንት ነበር። ጣቢያው ስርጭቱ የተቋረጠበትን ምክንያት እንዲገልጹለት ኢትዮጵያ መንግስት ጥያቄ ቢያቀርብም መልስ እንዳልተሰጠው አስታውቋል። አልጀዚራ የቢቢሲ የስለላ ሪፖርት የኢትዮጵያን መንግስት ባጋለጠ ማግስት ማስተባበያ የሚመስል ስርጭት አስተላልፎ እንደነበር የሚያስታውሱ መንግስትን በመደገፍ መልኩ ሳይሆን አልጀዚራ ለበርካታ ጉዳዮች ሽፋን እንደማይሰጥ በመጥቀስ “የጁን አገኘ” ሲሉ ተጠምደዋል። አልጀዚራ በወቅቱ የምግብ እህል ርዳታ ለፖለቲካ አላማ ይውላል በተባለበት ቦታ አርሶ አደሮች ቤታቸው ድረስ በመግባት ነበር ሰፊ ከኢቲቪ የበለጠ ሪፖርት ያቀረበው።
የአልጃዚራ ድረገጾች እንዲታነቁ የተደረጉበት ዋናው ምክንያት የቴሌቪዥን ጣቢያው ለኢትዮጵያውያን ሙስሊሞች ተቃውሞ በሰጠው ሽፋን እንደሆነ አመልክቷል። እንደ ጉግል የመረጃ ትንተና በኢትዮጵያ ውስጥ የእንግሊዝኛው ድረገጽ ባለፈው ዓመት ሀምሌ ወር 50ሺ ተጠቃሚ የነበረው ሲሆን፣ በመስከረም ወር የተጠቃሚው ቁጥር ወደ 114 ወርዷል። የአረቢኛው ድረገጽም ከ5,371 ተጠቃሚዎች ወደ 2 መውረዱን ያሳያል። ይህንን መረጃ የዘረዘረው አልጀዚራ ይህ መረጃ የሚያሳየው ጣቢያው በነሃሴ ወር የኢትዮጵያ መንግስት በእምነት ጣልቃ እንደሚገባ ካስተላለፈ በኋላ በተወሰደው የእግድ ርምጃ መሆኑንን አመልክቷል። አልጀዚራ ከታገደ በኋላ የኢትዮጵያ የሰብአዊ መብት ሁኔታና የጋዜጠኞችን እስር በስፋት በዶክመንታሪ መልክ አቀናብሮ አስተላልፏል።
የኤሌክትሪክ መቋረጥ ማሽን እያቃጠለ ነው
በአዲስ አበባ ሰሞኑን በተደጋጋሚ ኤሌክትሪክ እየተቆራረጠ በመሆኑ ስራችንን በአግባቡ መስራት አልቻልንም ሲሉ ነዋሪዎች ቅሬታቸውን እያቀረቡ ነው። ከነዋሪዎች በተጨማሪ አንዳንድ ፋብሪካዎችና የተለያዩ ተቋማትም የሃይል መቆራረጡ ችግር እየፈጠረባቸና ማሽኖቻቸውን እያቃጠለባቸው መሆኑን በመግለጽ  የሚመለከተው አካል አፋጣኝ መፍትሄ እንዲሰጣቸው መጠየቃቸውን ከአገር ውስጥ ተዘገበ።
በኮርፖሬሽኑ የዲስትሪቢዩሽን ስራ አስፈፃሚ የሆኑት አቶ መስፍን ብርሀነ እንዳሉት፥ የግንባታ ስራዎች በሚካሄድባቸው አካባቢዎች የወሰን ማስከበር ስራ ሲሰራ በቦታው የነበሩ የኤሌክትሪክ መስመሮችን የማዛወር ስራ ስለሚሰራ ፤ በአንዳንድ አካባቢዎች በኔትዎርኮቹ ላይ የሚካሄደው ዝርፊያ እና የሚደርሰው የመኪና ግጭት ለችግሩ መንስኤ መሆናቸውን፣ ሰሞኑን እያጋጠመ ያለው ንፋስም ለችግሩ ምክንያት ሲሆን ፥ በዚህም የኤሌትሪክ መስመሮች ላይ ጉዳት ስለሚደርስና የኤሌትሪክ መስመሩን መልሶ መጠገን እስኪቻል የኤሌትሪክ ማቋረጡ ያጋጥማል ብለዋል። በዚህ ምክንያት በተለይ በኤሌክትሪክ እቃዎች ላይ ለሚፈጠረው መቃጠልና መሰል ችግሮች ፣ ኮርፖሬሽኑ አስፈላጊውን ካሳ እንደሚከፍል ሃላፊውን ገልጾ ፋና ዘግቧል። ሃላፊው ይህንን ቢሉም የችግሩ ሰለባ የሆኑ በተባለው መሰረት ካሣ እንደማያገኙ ለማወቅ ተችሏል፡፡
http://www.goolgule.com/briefs-22/

No comments:

Post a Comment