FREE ALL POLITICAL PRISONERS

FREE ALL POLITICAL PRISONERS
FREE ALL POLITICAL PRISONERS

Sunday, December 23, 2012

የብሔራዊ ቡድን ተጫዋቾች አድማ በመቱ ማግስት- መንግስት ለተጫዋቾቹ ጥያቄ ምላሽ እንደሚሰጥ ቃል ገባ


ኢሳት ዜና:-ከ 31 ዓመታት በሁዋላ ለአፍሪካ ዋንጫ ያለፉትና በመጪው ጥር ወር በደቡብ አፍሪካ በሚካሄደው የአፍሪካ ዋንጫ ውድድር የተሻለ ውጤት ያስመዘግባሉ ተብለው ተስፋ የተጣለባቸው የኢትዮጵያ ብሔራዊ እግር ኳስ ቡድን አባላት ከክፍያና ከአንዳንድ ጥያቄዎች ጋር በተያያዘ አድማ የመቱት ከጥቂት ቀናት በፊት ነበር።
ዋልያዎቹን  አድማ ለመምታት ያነሣሳቸው፤ ቀደም ካለ ጊዜ ጀምሮ እስካሁን ድረስ በእግር ኳስ ፌዴሬሽኑ በኩል  የተደረገላቸው ምንም ዓይነት ድጋፍ አለመኖሩ፤እንዲሁም  በሽልማት መልክ ቃል የተገባላቸውን ገንዘብ ሊያገኙ አለመቻላቸው ጭምር ነው።
"ሌላው ቀርቶ አሁን  ተቃውሞ ባደረግንበት ጊዜ እንኳ ችግራችሁ ምንድነው ?ብሎ ቀርቦ ያነጋገረን የለም"ሲሉ ተደምጠዋል-ተጨዋቾቹ።
የአፍሪካ ዋንጫ ሊጀመር ከ1 ወር ያነሰ ጊዜ በቀረው በአሁኑ ወቅት ተጫዋቾቹ አድማ መምታታቸው ያስደነገጠው  የኢትዮዽያ እግር ኳስ ፌደሬሽን አርብ ዕለት አስቸኳይ  ስብሰባ በመጥራት ከተጨዋቾቹ ጋር ተነጋግሯል።
በስብሰባው  ላይ በብሄራዊ ቡድን ተጫዋቾች ከተነሱት ጥያቄዎች መካከል፤  "ከሱዳን ጨዋታ በፊት ቃል የተገባልን የገንዘብ ሽልማት ዘገይቷል" የሚለው ቅሬታ እንደሚገኝበት የራዲዮ ፋና ዘገባ ያመለክታል።
ከዚህም በተጨማሪ፦" በሚሰጠን ገንዘብ የጋራ መኖሪያ ቤት መግዛት እንድንችል ከሚመለከተው አካል ጋር ተነጋግራችሁ ምላሽ ይሰጠን" የሚል ጥያቄ ማቅረባቸውም ተሰምቷል።
የፌዴሬሽኑ ተቀዳሚ ፕሬዚዳንት አቶ ተካ  አስፋው፤ ፌዴሬሽኑ ለሽልማቱ የዘገየው በወቅቱ በካዝናው ተቀማጭ ገንዘብ ባለመኖሩ እንደሆነ በመጥቀስ ፥ በአሁኑ ወቅት ግን ስራ አስፈጻሚ ኮሚቴው ስለወሰነና ገንዘብም ስለተገኘ ሽልማቱ እንዲሰጥ መወሰኑን አስረድተዋል ።
በዚህም መሰረት የሽልማቱ ጣሪያ 100 ሺህ ብር ሆኖ ከቤኒኑ ጨዋታ ጀምሮ ቋሚ ተሰላፊ ሆነው የቀጠሉ ተጫዋቾች ከፍተኛውን ሽልማት እንደሚያገኙ  ፥ ሌሎችም እንዳበረከቱት አስተዋጽኦ በየደረጃው የሽልማቱ ተቋዳሽ እንደሚሆኑ አመልክተዋል።
"የጋራ መኖሪያ ቤትን በተመለከተ የሚመለከተው፤ የአዲስ አበባ ከተማ አስተዳደርና በስሩ ለዚህ ጉዳይ የተቋቋሙ ተቋማት ናቸው" ፤ያሉት አቶ ተካ "ለዚህ የተጫዋቾቹ  ጥያቄ የፌዴሬሽኑ ምላሽ ፦ተቋማቱ በደንብና መመሪያቸው መሰረት ምላሽ የሚሰጡ ይሆናል  የሚል  ነው " ብለዋል።

No comments:

Post a Comment