FREE ALL POLITICAL PRISONERS

FREE ALL POLITICAL PRISONERS
FREE ALL POLITICAL PRISONERS

Monday, January 28, 2013

ከእሁድ እስከ እሁድ (የሳምንቱ አጫጭር ዜናዎች)


ሻማ ማብራት ፣ ኤምባሲ መውረር
በአብዛኛው የኢትዮጵያውያን ተቃውሞ ሻማና ጧፍ ማብራት፣ በሰላማዊ ሰልፍ መጮህ፣ ፒቴሽን መፈራረም፣ በተለያዩ ማህበራዊ አውታሮችና ድሮች መሳደብና የመሳሰሉት ናቸው። ባለፈው ሳምንት የኤርትራ ተወላጆች ሎንዶን የሚገኘውን የኢሳያስ ኤምባሲ ጥሰው በመግባት የፈጸሙት የተቃውሞ ተግባር ከፍተኛ የሚዲያ ትኩረት ስቧል።
“ኤምባሲው የእኛ ነው። ከኤምባሲያችን ወደ የትም አንሄድም” ያሉት የኤርትራ ተወላጆች የሚፈሩትን ኢሳያስን ያገኙ ያህል ፎቷቸውን ከግድግዳ በማውረድ መሬት ላይ በመከስከስ ረጋግጠው ተቃውሟቸውን ሲገልጹ ራሳቸው ፕሬዚዳንት ኢሳያስና ዓለም ተመልክቷል። ይህ ታላቅ የተቃውሞ መልዕክት ለሁሉም ባለስልጣናት መልዕክት ሲሆን በተለይም ስደት ልዩ መለያው ለሆነው የኤርትራ ህዝብ ባንድነት ይነሳሳ ዘንድ የሚቀሰቅስ ተግባር ሆኖ ተገኝቷል። የእኛ አገር ተቃዋሚዎችና ደጋፊዎችስ? ሻማና ጧፍ በማብራት እንቀጥላለን ወይስ ተቃውሞውን አንድ ደረጃ እናሳድገዋለን?
መለስ አልታደሉም
ጎል ካስቆጠሩ በኋላ አቶ መለስ የተለጠፉበትን ካኒቴራ በማሳየት ደስታቸውን እንዲገልጹ የታዘዙት የብሄራዊ ቡድን ተጫዋቾች የተባሉትን ማድረግ አቅቷቸዋል። ሁኔታውን ሲከታተሉ የነበሩ አሽሟጣጮች ትዕዛዙ ጎል ስናገባ ሳይሆን ጎል ሲገባብን የመለስን ፎቶ የሚያሳየውን ቲሸርት በማሳየት ሃዘንን መግለጽ ቢሆን ኖሮ አቶ መለስ በቡርኪናፋሶ ጨዋታ ወቅት አራት ጊዜ በሃዘን የመታወስ እድል ያገኙ ነበር ሲሉ ተደምጠዋል።
እነዚሁ ተረበኞች በናይጀሪያ ጨዋታ ላይ ትዕዛዙ ላይ ማስተካከያ እንዲደረግ መክረዋል። ቡድኑ ሜዳ ሲገባ በመጀመሪያ መለስ ያሉበትን ቲሸርት እንዲለብስ፣ ጨዋታው ሊጀመር ሲል ዳኛውን በማስፈቀድ የናይጄሪያ ተጨዋቾችም ቲሸርቱን ከውስጥ እንዲለብሱ እንዲያስገድዱላቸው ጥያቄ ማቅረብ፣ ከዚያም እኛ ካላገባን እንኳ ናይጀሪያዎች ሲያገቡ የመለስን ቲሸርት በማሳየት ደስታቸውን እንዲገልጹ፣ ይህንን ካደረጉ አላሙዲ እንደሚሸልሙ አስቀድሞ ለተጨዋቾቹ ማስታወቅ የሚሉትን ሃሳቦች ያቀረቡት ሸርዳጆች ሁሉም ተደርጎ ካልተሳካ መለስን በኳስ ሜዳ የማስታወሱ ጉዳይ በቀጣዩ የአፍሪካ ዋንጫ ይተገበር ዘንድ በአምስቱ ዓመት የእድገትና የትራንስፎርሜሽን እቅድ ውስጥ እንዲያዝና ውድድሩን ኢትዮጵያ እንድታዘጋጀው በማድረግ ለስኬቱ መታገል እንደሚቻል መክረዋል። አቶ መለስ በህይወት በነበሩበት ወቅት ስለ ስታዲየም ግንባታ ተጠይቀው “እኔን የሚያሳስበን ማዳበሪያ ነው” ማለታቸው ይታወሳል።
በባንዲራ ብዛት የተሞሸረ ብሄራዊ ቡድን
የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን ደቡብ አፍሪካ ላይ ለክብሩ የቀረበለት የባንዲራ ብዛት በሪኮርድነት ተመዝግቧል። ምናልባትም ይህ የዕድሜ ልክ ሪኮርድ ሊሆን እንደሚችል ይገመታል። አሁን ያለው ባለኮከቡ ባንዲራ፣ የቀድሞው ሰንደቅ ዓለማ፣ የኦሮሚያ መለያ፣ የሞአንበሳ ባለ አንበሳው ባንዲራ፣ የኦጋዴን ነጻ አውጪ ባንዲራ፣ የኢህአዴግ አርማ …
ቡድኑን ለመደገፍ ወደ ስታዲየም የመጡት ደጋፊዎች ያሳዩት የተለያ ባንዲራ ሁሉም ኢትዮጵያን ለመደገፍ ቢሆንም የፖለቲካ መልዕክት ከማስተላለፍ አኳያ ሆን ተብሎ የተደረገ በመሆኑ አገሪቱ ውስጥ ያለውን የፖለቲካ ትኩሳት አመላካች ስለመሆኑ ጥርጥር የለውም። ለወደፊቱ ቡድኑ የሚጫወትበት መለያ የሁሉንም ባንዲራ የሚወክል እንዲሆን የኢትዮጵያ እግር ኳስ ፌዴሬሽን ሊያስብበት ይገባል። ሁሉንም ብሄሮችና የነጻነት ጥያቄ ያላቸውን ክፍሎች መለያ እንዲያካትት ተደርጎ አዲስ መለያ ከተዘጋጀ ሁሉም የየራሳቸውን ባንዲራና አርማ ከመጎተት ይልቅ አዲሱን ማሊያ በመልበስ ውክልናቸውን ያሳያሉ። በመሆኑም አዲሱ የመጫወቻ ሹራብ ክንዱ የኦነግን አርማ፣ አንገቱ የኢህአዴግን፣ ጀርባው የቀድሞውን ባንዲራ፣ ፊትለፊቱ የኦብነግን፣ ቁምጣው የብአዴንን፣ ኪሱ የስልጤ፣ የእግር ሹራቡ የህወሃትን፣ አልበቃ ካለ ኮፊያና ስካርፕ አድርገው የተለያዩ ብሄሮችን እንዲወክሉና ሜዳ እንዲገቡ ቢደረግ የተሻለ ሳይሆን ይቀራል?
ብሄራዊ ቡድን ሬኮርድ ሰበረ
የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን በደቡብ አፍሪካ ውድድር ብዙ የገባበት ቡድን በመሆን ሬኮርድ ተመዝግቦበታል። ቡድኑ ቡርኪና ፋሶ አስር ሰው ሆነው ቢጫወቱም አጋጣሚውን መጠቀም አልቻለም። በጉዳት የወጣው አዳነ ግርማ ጉዳቱ ከፍተኛ በመሆኑ ቶሎ እንደማያገግም የቡድኑ ዶክተር አስታውቀዋል።
ከሰላሳ አንድ ኣመት በኋላ አፍሪካ ዋንጫ የተቀላቀለው የኢትዮጵያ ቡድን መርሃ ግብሩን የሚያጠናቅቅበት የመጨረሻ ጨዋታውን ከናይጀሪያ ጋር ያከናውናል። ያለፈው ዓመት ባለድል ዛምቢያ ከቡርኪናፋሶ ጋር በምታደርገው ጨዋታ ከተሸነፈች ወይም እኩል ከወጣችና ኢትዮጵያ ናይጀሪያን ማሸነፍ ከቻለች ወደ ሁለተኛው ዙር ታልፋለች። አሁን ባለው የነጥብ ድምር ውጤት መሰረት ቡርኪና ፋሶ አራት፣ ዛምቢያ ሁለት፣ ናይጀሪያና ዛምቢያ ሁለት፣ ኢትዮጵያ አንድ ነጥብ አላቸው።
ሰውነት ቢሻው ተወቀሱ
“በቀጣይ ያልተጠቀምኩባቸውን አሰልፋለሁ”
በቡርኪና ፋሶ አራት ለባዶ የተሸነፈው የኢትዮጵያ ብሄራዊ ቡድን አሰልጣኝ ሰውነት ቢሻው እየተወቀሱ ነው። ሽንፈቱን አስመልከቶ የህዝብ አስተያየት ያሰባሰበው ኢቲቪ “በጨዋታው የአሰልጣኙ ደካማ ብቃት ተስተውሏል፣ እንቅስቃሴው ዝቅተኛ ነው። ምክንያቱ አልገባኝም። አሰልጣኙ አሰላለፍ ላይና አቀያየር ላይ ስህተት ሰርተዋል። አምስት ተመላላሽ ተጨዋቾችን አሰልፏል…” የሚሉ ነቀፌታዎች አሳይቷል።
አሰልጣኝ ሰውነት ቢሻውን “በድሉ” በማለት የሚጠሯቸውና በቅርብ የሚያውቋቸው ተጨዋቾች አሰልጣኙ አሁንም ችግሩ አልገባቸውም እያሉ ነው። “በራሳችን ሜዳ ኳስ በብዛት ማንከባለላችን ጎድቶናል” በማለት አቶ ሰውነት የሰጡትን አስተያየት ተከትሎ የተሰጠው አስተያየት በናይጀሪያው ጨዋታ አሰልጣኙ ረጅም ኳስ የመጫወት እቅድ እንዳላቸው አመላካች ነው። ይበልጥ እንዳንከስር እንፈራለን ብለዋል። ምን ይደረግ? ለተባሉት ኳስ ይዞ ባላጋራን በመቁረጥና አማካዩን ክፍል ኳስ ለሚችሉ ልጆች በመፍቀድ እንዲጫወቱ መደረግ እንዳለበት ተናግረዋል። የባዮሎጂ መምህር የነበሩት ሰውነት ቢሻው ወኔ በማነሳሳት እንደሚታወቁ የሚገልጹት አስተያየት ሰጪዎች በዚህም በኩል ጥንቃቄ እንዲደረግ፣ ተጨዋቾቹ ሰክነው እንዲጫወቱ መደረግ እንዳለበት ይመክራሉ።
ጥቃቅንና አነስተኛ ተቋማት ኪራይ ሰብሰቢ ተባሉ
መንግስት ከፍተኛ ትኩረት እንደሚሰጣቸው የሚነገርላቸው የጥቃቅን አነስተኛ ተቋማት በኪራይ ሰብሳቢነት ተፈረጁ። ኢንተርፕራይዞቹ የኪራይ ሰብሳቢነት አመለካከትና የተግባር ማነቆ እንዳለባቸው ይፋ ያደረገው ኮንስትራክሽን ሚኒስትር እንደሆነ የዘገበው ሪፖርተር ነው።
የተበደሩትን ገንዘብ መመለስ እንዳልቻሉ ሪፖርት የቀረበባቸው ተቋማት በበጀት ዓመቱ ግማሽ ዓመት 1.6 ቢሊዮን ብር እዳ መክፈል ሲገባቸው 575 ሚሊዮን ብር ብቻ መክፈላቸው የኪራይ ሰብሳቢነት አመለካከት የተጠናወታቸው አስብሏቸዋል።1.1 ቢሊዮን ብር መቆጠብ ሲገባቸው ተቋማቱ 540 ሚሊዮን ብር ብቻ ተቀማጭ ማድረጋቸው ሌላው ችግር እንደሆነ ሪፖርተር የጠቀሰው ዘገባ ያስረዳል።
“ትርፍም ኪሳራም የለውም”
ከአካባቢ ምርጫ ራሳቸውን ያገለሉ የተቃዋሚ ፓርቲዎች ኢህአዴግ ላይ ሊያስከትሉት የሚችሉት ጫና እንደሌለ ተሰማ። የኢህአዴግ ጽህፈት ቤት የህዝብ አደረጃጀት ሃላፊ የሆኑትን አቶ ሬድዋንን ፎቶ በማስቀደም አዲስ አድማስና ሪፖርትር እንዳስነበቡት በኢህአዴግ እምነት “ትርፍም ኪሳራም የለም”።
አቶ ሬድዋን የተቃዋሚ ፓርቲዎች በምርጫው አለመሳተፋቸው “ለኢህአዴግ ትርፍም ኪሳራም የለውም” በማለት በሰጡት መግለጫ እንደተለመደው የተቃዋሚ ፓርቲዎችን ዘልፈዋል። ለአካባቢ ምርጫ ደንታ ቢስ አድርገው ስለዋቸዋል። ኢህአዴግ ያቋቋማቸውና ተወዳዳሪ ሊሆኑ የማይችሉ ፓርቲዎች ምርጫውን በማድመቅና ኢህአዴግን በማጀብ የተለመደ ተግባራቸውን እንደሚጫወቱ በተለያዩ ሚዲያዎች መዘገቡ ይታወሳል።
source : www.goolgule.com

No comments:

Post a Comment