FREE ALL POLITICAL PRISONERS

FREE ALL POLITICAL PRISONERS
FREE ALL POLITICAL PRISONERS

Saturday, January 19, 2013

መንግስት በአገሪቱ በቂ ምርት አለ ቢልም ህዝቡ ግን ሸቀጦች ከገበያ እየጠፉ ነው ይላል


ጥር ፲፩ (አስራ አንድ) ቀን ፳፻፭ ዓ/ም
ኢሳት ዜና:- በኢትዮጵያ ውስጥ የመሰረታዊ እቃዎች እጥረት በተለያዩ አካባቢዎች መታየቱን ተከትሎ 13 በመቶ የደረሰው ዋጋ ግሽበት ተመልሶ ያሻቅባል የሚል ስጋት ሰፍኗል። በተለይም በአገሪቱ የስንዴ፣ የዘይት እና ስኳር እጥረት በስፋት መታየቱ፣ ህዝቡን ስጋት ላይ እንዲወድቅ አድርገውታል።
ዳቦ ቤቶች በቂ የሆነ ስንዴ ለማግኘት ባለመቻላቸው በርካታ ዳቦ ቤቶች ዳቦ ማምረት ሊያቆሙ ይችላል የሚል ስጋት ፈጥሯል። መንግስት ከዚህ በፊት ባልታየ መንገድ መግለጫ የሰጠ ሲሆን፣ መግለጫውን የተከታተለው ዘጋቢያችን እንዳለው፣ መንግስት በአገሪቱ በቂ የሆነ የስንዴ ክምችት መኖሩን በመግለጽ ወሬውን የሚያስወሩት አንዳንድ ዋጋ ለመጨመር የሚያስቡ ነጋዴዎች ናቸው። ይሁን እንጅ ነጋዴዎች በአገሪቱ የሚታየው የእቃዎች አቅርቦት እጥረት በጊዜ ሂደት ገሀድ ይወጣል በማለት እንደሚገልጹ ዘገባው ያመለክታል።
መንግስት በእህል ምርቶች በኩል የሚታየውን እጥረት ለመከላከል ከውጭ አገር ስንዴ ማስገባቱን፣ በቅርቡም ወደ አገር ቤት የሚገባ ስንዴ መኖሩን ገልጿል። ስኳርና ዘይትም እንዲሁ በበቂ ሁኔታ በአገር ውስጥ እንዳለ አስታውቋል።
መንግስት የነጋዴዎችን ሚና በመውሰድ  ስኳርና ዘይት በየቀበሌው እንደሚያከፋፍል ይታወቃል።
በህብረተሰቡ ዘንድ የተፈጠረው ስጋት የምግብ እና የምግብ ነክ አቅርቦቶችን ቀድሞ ወደ ነበሩበት ቦታ ይመልሳቸዋል የሚል ስጋት ፈጥሯል። ብሄራዊ ስታትስቲክ መስሪያ ቤታ ከሁለት ሳምንት በፊት ባወጣው ሪፖርት የምግብ ሸቀጦች ካለፈው ወር ጋር ሲነጻጸር ቅናሽ ማሳየታቸውን ገልጾ ነበር። ይሁን እንጅ ምግብ ነክ ባልሆኑ ሌሎች ሸቀጦች ላይ የዋጋ ጭማሪ ታይቷል።

No comments:

Post a Comment